Wednesday 22 June 2016

አንድአርጋቸው ፅጌ

ሰኔ 16 2006 የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ታጋይ ቆራጡና ጀግናው አንድአርጋቸው ፅጌ በብዙ ሚሊዮን ዶላር በሕገ-ወጥ መንገድ በየመን ትብብር በፋሽስታዊው ወያኔ እጅ ስር የገባበት ሰኔ 16 2008 የዛሬው ቀን ሁለተኛ ዓመቱን አስቆጠረን ᎓᎓ አንድአርጋቸው የጀመረው የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ትግል እና መስዋትነት ብዙ ሚሊዮኖችን ኢትዮጵያውያን ወደ ትግል አለም እንዲቀላቀሉ አድርጎአል᎓᎓
__________________________________________________
ዶ/ር ወንድሙ (ለንደን) ስለ አንድአርጋቸው ፅጌ ከትዝታዎቼ አንዱ በማለት እንዲህ ብለው ነበር᎓᎓
" አንድ የወያኔ ወዳጅ የብርቲሽ የፓርላማ አባልና የመንግስት ባለስልጣን ወያኔን ለመርዳት በፈረንጆቹ አቆጣጠር 2005 ዓ᎐ም ላይ "ለኢንቨስተሮች "እዚያው ፓርላማ ውስጥ የምሽት ስብሰባ በሚስጥር አዘጋጀ᎓᎓ አንድ ወንድም ሚስጥራቸውን ማወቅ ብቻ ሳይሆን የግብዣ ወረቀትም መግኘት ቻለ ᎓᎓ ያንን የግብዣ ወረቀት " ከእኔ ይልቅ አንተ ብትገባበት ይሻላል" ብሎ ድምፄን አጥፍቼ እንድገባ መክሮ ሰጠኝ᎓᎓ እንዳለው ተሽሎኩልኬ ስገባ ፣ አንድአርጋቸውና ዶ/ር ብሪም በዚያው መንገድ ገብተው አገኘኋቸው᎓᎓ ተመሰጣጥረን ተቀመጥን᎓᎓ አልተመካከርንም ᎓᎓ ዕድሉን እናግኝ እንጂ፣ ሶስታችንም የአገራችንን ጉዳይ ለመናገር ብቁ እውቀት ነበረን᎓᎓
ያ ባለስልጣን ለነዚያ "ኢንቨስተሮች " ና በወረንጦ ተለቅመው ለታጋበዙ ታዳሚዎች ፣ወያኔ የሚያስተዳድራት ኢትዮጵያ ንዋያቸውን ለማፍሰስ ለሚፈልጉ ባላሃብቶች ገነት እንደሆነች ፣ ዲሞክራሲ በአገሪቱ እንዳበበ ፣ ልማት በየቦታው እንደተተከለ ፣ርሀብ ኢትዮጵያ ውስጥ ጨርሶ ጠፍቶ ለታሪክ ምዝገባ ብቻ እንደበቃ ᎐᎐᎐ የወያኔን አስቀያሚ ገፅ "በሜክአፕ" ቀባብቶ ያለምንም ሀፍረት አቀረበው ᎓᎓ በንግግሩ መጨረሻ ላይ ለጥያቄ መድረክ ተከፈተ ᎓᎓ ኢንቬስተር ሁሉ በጉጉት ጥያቄውን አዥጎደጎደ᎓᎓ መልስ ተሰጠ᎓᎓ እኔ እጄን ባወጣ፣ባወጣ ሰርጎ- ገብ ኢትዮጵያዊ መሆኔ ሳይነቃ አልቀረምና ተዘጋሁ᎓᎓ዶ/ር ብሪ በጣም ቀላ ስለሚል የዓረብ ቱጃር መስሏቸው ነው መሰለኝ ዕድል ሲሰጡት ፣ በሚያስገርም ሁኔታ ሰውየው የካበውን ሁሉ በመረጃ በተደገፈ አስተያየት ደርምሶት አረፈው᎓᎓ ያንን ውርጅብኝ መካድ ስለማይቻል " የራስህን ሃሳብ የመግለጽ መብት አለህ" ተብሎ ሊታለፍ ተሞከረ ᎓᎓ አንድአርጋቸው ለመጀመሪያ ግዜ እጁን አወጣ ᎓᎓ አንድአርጋቸው ሲመቸው በኢትዮጵያን ካልሆነ በስተቀር በእይታ የትውልድ ሃገሩን ለመለየት አስቸጋሪ ነው ᎓᎓ ናይጄራዊ ቱጃር ሳይመስለው አልቀረም ᎓᎓ ዕድሉን ሰጠው ! በቀጥታ እንግሊዞቹ ላይ ነበር አንድአርጋቸው ያነጣጠረው᎓᎓ "እናንተ ብርቲሾች ስትባሉ፣ሁለት አይነት ዲሞክራሲ ነው ያላችሁ᎓᎓አንዱ ለዜጎቻችሁ ያለገደብ የሚሰጥ ነው᎓᎓ ሌላው በማንኪያ እየተጨለፈ ለታዳጊ አገሮች የሚሰጥ !እንደ ኢሕአዴግ ያለ አሻንጉሊታችሁንማ ፣ ነፍስ-ገዳዮች መሆናቸውን እያወቃችሁ፣ ዜጎቻቸው ላይ የሚያደርሱት ግፍ፣ጭፍጨፋ፣ በደልና ፍጅት፣ በተባዮች ላይ የሚፈፅሙት እንጂ በሰው ላይ የሚደርስ ስቃይ መስሎ አይታያችሁም ᎓᎓ እኛም ኢትዮጵያን እኮ እንደ ብርቲሽ ዜጎች ዲሞክራሲ ይርበናል ፣ ፍትህ ይጠማናል ፣እኩልነት ይናፍቀናል ᎓᎓ ገዳዩን፣ወንጀለኛውን፣አገር አጥፊውን ጉልበተኟ ገዢ እንዲህ አሰማምረው ሲያቀርቡት ትንሽ እንኳን አይሰቀጥጦትም?" ሲል ቤቱ ተረበሸ! ሰብሳቢውም ባለስልጣን ዕቅዱ ሁሉ እንደተኮላሸበት ሲረዳ ፣"ሌላ ስብሰባ አለኝ" ብሎ ተሰብሳቢውን ጥሎ ውልቅ አለ᎓᎓ ሶስታችን ክፍሉን ተቆጣርን ᎓᎓ ተሰብሳቢው እውነተኛ የበለጠ ዕውነተኛ ማስረጃ ለማግኘት ሶስታችንን ከበበን ᎓᎓የሚያስፈልገውን ማስረጃ ሁሉ ሰጥተን አድራሻ ተቀያይረን እየሳቅን ወጣን ᎓᎓ ከዚያችን ዕለት ጀምሮ ነፍሴ ከአንድአርጋቸው ጋር ተቆራኘች !ከዚያ በኋላ የትግል ጓዶች ሆንን᎓᎓ አብረን ብዙ ብዙ ቁምነገሮችን ሰርተናል᎓᎓ እሱ ቅንጅቶችን ለመርዳት ወደ ኢትዮጵያ ተመልሶ ከቅንጅት ባላስልጣኖች ጋር ሲታሰር በለንደን የተቃውሞ ረሀብ-አድማ ከመቱት መሃል አንዱ ነኝ ᎓᎓ ዛሬም ወንድሜ ጠላቶቹ ሕገ-ወጥ መንገድ እጃቸው ሲያስገቡት፣ ከእጃቸው ፈልቅቀን እስከምናወጣ ድረስ ከሚታገሉት መሀል አንዱ በመሆኔ ታድያለሁ᎓᎓እኔም አንድአርጋቸው ፅጌ ነኝ᎓᎓"
ምንጭ"አሻራ" መፅሄት ገፅ 20