Monday 24 August 2015

ይህ ረሃብ “ፖለቲካዊ ችጋር” ነው!!

“በቀን ሦስቴ እንመግባችኋለን”

famine


ህወሃት ለአገራችን የቀመመው የበቀልና የተላላኪነት ፖለቲካ ገና ጦሱ አልጀመረም። ግን ሊመጣ ግድ ነው። በንጉሡ ወቅት ተርበናል። በደርግ ጊዜ ተርበናል። ኢህአዴግ ከመጣ ጀምሮ የታዩት ርሃቦች ግን ለየት ያሉ ናቸው። ስለዚህ ርሃቡም ሆነ ችጋሩ ፖለቲካዊ ነው ቢባል ያስማማል። ኢሣ የግጦሽ ሳር ሲያጣ ወደ ጎረቤቶቹ ያመራ ነበር። አፋር ተመሳሳይ ችግር ሲገጥመው ከብቶቹን እየነዳ ችግርን አሳልፎ ይመለስ ነበር። መጠነኛ አለመስማማት /በግጦሽ መሬት/ ከመፈጠሩ ውጪ “እገሌ ነህ” በሚል ጎጥ ለይቶ ሲጋደል አልተሰማም።
ዛሬ ህወሃት ሌሎችን እንደራሱ ለማሳነስና ለመበጣጠስ ሲል በዘርና በጎሳ መባላትን በአዋጅ ደንግጎ፣ በህግ አጽድቆ፣ ባገር ሚዲያ ጥላቻን እየሰበከ ተፋቅረው የኖሩትን አባልቷቸዋል። እያባላም ነው። ብዙ ሳይቆይ ራሱንም ጨምሮ የሚበላውን እሳት በየቀኑ እያጋመውም ይገኛል። እናም ሰሞኑን አደባባይ የወጣው ርሃብ ሰለባ ከሆኑት መካከል “እንደቀድሞ ከብት እየነዱ ምግብ ፍለጋ መጓዝ ስለማይቻል፣ ወገኖቻችን ውሃ እያሉ አለቁ። ተደብቆ እንጂ ብዙ ህዝብ አልቋል” ሲሉ ነግረውናል። ይህ ፖለቲካው ያመጣው ጣጣ ኩራት ለሚሆንላችሁ እንኳን ደስ አላችሁ፣ ገንቡ፣ ዝረፉ፣ ልጆቻቸሁን በዶላር አስተምሩ፣ አፈናቅሉ፣ የድሃውን መሬት በሽርክና ቸብችቡ፣ ራሳችሁም ኢንቬስተር ሆናችሁ አልሙ፣ ተንበሻበሹ፣ ስከሩ፣ ዘሙቱ፣ በራባቸው ላይ አስመልሱባቸው፣ … እነ ሬድዋንን ጨምሮ።
የመለስ ሙት መሃላ
“የሚሰሩ እጆች እያሉን፣ የሚያስቡ አእምሮዎች እያሉን፣ ይህን ወጣት ኃይል ይዘን ስንዴ መለመን እናቆማለን” በማለት ድርሰት ሲደርሱልን፣ ሲተርኩልን የነበሩት አቶ መለስ “የልማት አርበኞችን” ይዘው ገጠር ገቡ። የልማት ጀግኖች ከተማ ለቀው ገጠር ከተሙ። ዕድሜ “ለኤክስቴንሽን” አገሪቱና ገበሬው ምርት ማስቀመጫ ቦታ አጡ። በአገሪቱ ታሪክ እህል ወደ ውጪ መላክ ተጀመረ በማለት ደጋግመው ሰብከውን ነበር። መለስ “ገበሬውንና አርብቶ አደሩን ማእከል አድርገን ተነስተናል። ይህ አስተሳሰብ የሚቀየረው በኢህአዴግ መቃብር ላይ ብቻ ነው” እያሉ ሲምሉ ነበር። ነገር ግን ሲማልበት የነበረ ህዝብ መሬቱን ተቀማ። በሳንቲም ለሌባ “ባለሃብቶች” ተቸበቸበ። የህዋሃት ሰዎች በልማት ስም ተቀራመቱት። የኢንቨስትመንት ኤጀንሲ መረጃ አብይ ዋቢ ነው። እዩት!! በቀን ሶስቴ መብላት ቀርቶ አንዴውም እርም ሆነ። ነፍስ ይማር?!
የፖለቲካ ድርቅ – ፈጀን – ገና ይፈጀናል!
ሰዎች በዘራቸው ተለየተው ከሚኖሩበት ተፈናቅለዋል። እየተፈናቀሉ ነው። በሁሉም ክልሎችና ጎረቤት አገራት “ተከብረው” የሚኖሩት ህወሃት “ምርጥ” የሚላቸው ዜጎቹ ብቻ ናቸው። ይህንኑ ሃቅ የህወሃት አመራሮች በይፋ የሚናገሩት እንጂ እኛ የፈጠርነው አይደለም። መፈናቀል ለችጋር ይዳርጋል፤ የፖለቲካ ድርቅ ነው። ሰለባዎቹ ፍቺው ስለሚገባቸው ይብቃ!!
ለም መሬት በቅንጣቢ ሳንቲም እየቸበቸቡ ደሃውን ማፈናቀል ሌላው የፖለቲካ ቸነፈር ነው። ለአራት ዓመት ህጻን “ከክልላችን ውጣ” ብሎ ደብዳቤ መስጠት የከፋ የፖለቲካ ጠኔ ነው። “ባሪያ፣ አገልጋይ፣ አሽቃባጭ፣ ሎሌ … ካልሆንክ ሥራ አታገኝም” ብሎ ማለት ጠባሳው የማያሽር የፖለቲካ ችጋር ነው።
ለምን ተነፈሳችሁ በሚል ወኅኒ ተጥለው የሚሰቃዩ ወገኖች ጉዳይ ጊዜ መልስ የሚሰጠው የፖለቲካ ሽባነት ነው። ይህም ትልቅ ችጋር ነው። ሴት እህቶቻችን በዘራቸው ተመርጠው እንዲመክኑ ማድረግ ይቅርታ ለማድረግ የሚቸግር የፖለቲካው ተስቦ ውጤት ነው። እንዲህ ያለው የነጠፈ ኅሊና የሚነዳው ፖለቲካ ከችጋር በምን ይለያል?
ከድሃው ጉሮሮ በመንጠቅ በተዘረፈ ሃብት ድንጋይ መቆለል፣ ቪላ ማስገንባት፣ ዘመናዊ ተሽከርካሪ መዘወር፣ ጠግቦ ድሆችን መርገጥ … የፖለቲካው በሽታ ከመሆን ምን ያግደዋል? ከወገን ይልቅ ባእድ የሚያስቀድም የአገር ገዢ የፖለቲካ ችጋር ያጠናገረው እንጂ ሌላ ምን ሊባል ይችላል? እነዚህ ኅሊናቸው የሞተባቸውና ቂም ቀብትቶ የያዛቸው ክፍሎች የሚያሽካኩበት ህዝብ የፖለቲካው ችጋር አልመታውም? ቸነፈሩ ስንቱን ዘረረ?! የስንቱን ደጅ ዘጋ … እንዲህ እየኖርን ዛሬ ላይ ደረስን።
ዛሬም ተርበናል። ችጋር ይዞናል። ድርቅ እንስሶችን፣ ወገኖቻችንን እየቀጠፋቸው ነው። የቁጥር ጸብ ከሌለ በስተቀር ችጋሩም፣ ረሃቡም፣ ድርቁም ካቅም በላይ ሆኖ ህጻናትን፣ አረጋዊያንን፣ እንስሦችን እንደፈጀና እየፈጃቸው ስለመሆኑ መከራከሪያም ሆነ ማደናበሪያ ማቅረብ የሚቻለው የለም። ሊኖርም አይችልም።
በተመሳሳይ ጥጋብ ያሰከራቸውና በዝርፊያ ላይ ተጠምደው “ልማት ላይ ነን” የሚሉ አሉ። ሁሉም የዚያች መከረኛ አገር “እኩል ዜጎች” ተብለው ይቆጠራሉ፤ ይጠራሉ። የዚህን መጨረሻ ስናስብ እናፍራለን፣ እናዝናለን፣ አንደነግጣለን። ስጋት ያርደናል። በዚህ መልኩ አይቀጥልምና!! የቀን እንጂ የሰው ጀግና የለውም እንደሚባለው!!
“ድርቅና ችጋር ያሉ፣ የነበሩና የሚኖሩ ናቸው። አሜሪካም ሆነ አውስትራሊያ ድርቅ አለ፤ ለምን እንዲህ በመረረ መልኩ አያችሁት? ድርቅ ብርቅ ነው እንዴ?” በሚል ጥያቄ የሚያቀርቡ “የልማት መሪዎችና አርበኞች” መልሳችን “ቀን ይፍረድ” ብቻ ነው።
ረሃቡ የቆየ መሆኑ
እንደሚታወቀው የዘንድሮ ምርት ዘመን ገና መንገድ ላይ ነው። ክረምቱ አላበቃም። ስለዚህ አሁን ይፋ የሆነው ችጋር ካለፈው አመት ተንከባሎ የመጣ በመሆኑ አሁን ተከሰተ የተባለው “የዝናብ እጥረት” ምክንያት ሊሆን አይችልም። ለቪኦኤ አማርኛው ክፍል መግለጫ የሰጡት የሚቲዎሮሎጂ ባለስልጣን የዝናብ እጥረት እንደሚከሰት ለሚመለከታቸው ሁሉ አስቀድመው ማሳወቃቸውን ተናግረዋል። “የአየር ንብረት ድርቅ ገብቷል” ሲሉ አዙረውም ቢሆን ችግሩን አምነዋል። ግብርና ሚኒስቴርም ድርቅ ስለመከሰቱ ተጠየቆ አላስተባበለም። በዚህ መነሻ 14 ሚሊዮን ሕዝብ በችጋር እስኪገረፍ ድረስ፣ 24 ሚሊዮን ህዝብ ለችጋር እስኪጋለጥ “ልማታዊ ነኝ” የሚለው ህወሃትና አጫፋሪዎቹ የት ነበሩ? “ልማታዊ ነን፣ ስራ ላይ ነን” የምትሉት እናንተ “የህወሃት ምርጥ ዜጎችና አገልጋዮች” ምን መልስ ልትሰጡ ትችላላችሁ? “በቀን ሶስት ጊዜ ትበላላችሁ” በማለት በድሆች ላይ ሲሳፈጥ የነበረውን “ሌጋሲ” አምላኪዎችና የሙት መንፈስ ድቤ ደላቂዎች ራዕዩና “ከሦስት ዓመት በኋላ መልሳችሁ ምንድነው? “ከ … ጋር መጪው ጊዜ ብሩህ ነው”?!
ከፖለቲካ ችጋር ነጻ ካልወጣን ሁሌም ችጋር ነው!! መልከ ብዙ ችጋር!! (ፎቶ: ለማሳያ የቀረበ)

Thursday 20 August 2015

ለእውነት እንዳንታገል አዚም የሆነብን ምንድር ነው?

ይበልጣል ከኖርዌይ

truth1
ስለ እውነት በተግባር እንጂ በቃል ደረጃ ብዙ ማለት ከባድ ቢሆንም ብዙዎች ብዙ ጽፈዋል ተናግረዋል።እውነት ማለት ያዩትን፣ የሰሙትን፣ የሚያውቁትን፣ የተረዱትን፣ የሆኑትን እና የሚያምኑበትን ነገርሳይጨምሩ ሳይቀንሱ በግልም ሆነ በአደባባይ በይፋመናገርና መመስከር መቻል እንደሆነ የዘርፉ ሙህራን ያስረዳሉ።  በሌላ መልኩ ደግሞያላዩትን፣የማያውቁትን፣ ያልሰሙትን፣ ያልሆነን ነገር ሳያረጋግጡ እና የማያምኑበትን ጉዳይ አለመናገር ማለትእንደሆነም አክለው ያስረዳሉ፡፡ በአጭሩ እውነት የሀሰት ተቃራኒ ነው። እውነት ለመናገር፣ ስለ እውነት ለመመስከር በመጀመርያ ሀሰትን መቃወም ይኖርብናል። ስለ እውነት ለመናገር ያልቆሸሸ ንጹህ ሕሊና ሊኖረን ይገባል። ንጹህ ሕሊና እውነተኛ ዳኛ ነውና። ያልተበረዘ፣ያልቆሸሸ እና ንጽህ ሕሊና ሀሰትን የማስተናገድ ባህሪ የለውም።
ሀቀኝነት፣ ታማኝነት፣ እርግጠኛነት፣ ትክክለኛነት፣ ተጠያቂነትን መቀበል እና ሀላፊነትን መወጣት የእውነት መገለጫ ባህሪያት ናቸው። በሌላ አነጋገር እውነት ማለት ጽድቅን ማድረግ፣ መልካም ሥነ ምግባርን መላበስ እና ለነጻነት፣ ፍትህና ዲሞክራሲ ግንባታ መታገል ማለት ነው። እውነት ማለት ሀገር፣ ታሪክ፣ ባህል እና ማንነት ነው። እውነት አድሎ የማይታይበት፣ ርህራሄና ቸርነት በተሞላበት ለሰው ልጅ ሁሉ መልካም ነገር እንዲያገኝ መመኘትና በጎ ተግባራትን ማከናወን ነው። እውነት የሰው ልጅ ዘላቂ ሰላም እና የተረጋጋ ህይወት እንዲያገኝ ከፍተኛ አስትዋጾ ያደርጋል።
ቀደምት አባቶቻችን  ስለእውነት ሲሉ ውድ ህይወታቸውን በሰማዕትነት አሳልፈው ሰጠዋል፤ ብዙ መከራና ስቃይ ተቀብለዋል። ለእውነት ሲሉ ከጊዜያዊ ጥቅም ታቅበዋል። ዛሬም ለእውነት ሲሉ ዋጋ እየከፈሉ የሚገኙ እውነተኛ የእውነት ምስክሮች በብዙ ስቃይና መከራ ውስጥ ይገኛሉ። በብዙ ውጣ ውረድ እውነትን መናገር እጅግ መልካምና ልብን የሚያስደስት ቢሆንም እውነትን የሚወዷትን ያህል የሚፈሯትና ከቻሉም በሀሰት ለውጠው ለማጥፋት የሚመኙ ብዙዎች ናቸው፡፡ በተለይ ጥቅምና ስልጣን ፈላጊዎች እንዲሁም አምባገነን መሪዎች በዋናነት ለእውነት መጥፋት ዋነኛ ተዋናኞች ናቸው፡፡
አምባገነን መሪዎች እውነትን መከተልም ሆነ መስማት አይፈልጉም። መነሻቸውና ግብራቸው ሀሰት ስለሆነ እውነትን ፈጽመው አያውቋትም። እርግጥ ነው እውነት ለእነሱ ጠላት ናት፤ ታጠፋቸዋለች። እነርሱ የሀገር መጥፋት፣ የታሪክ መዛባት፣ የህዝብ ሰላምና ደህንነት አያስጨንቃቸውም። ለሥልጣን ማራዘሚያ ሀገር ይሸጣሉ፣ ህዝብን ይጨቁናሉ፣ ይገድላሉም።
በዚህ በ21ኛው ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያ ውስጥ ስለ ነጻነት፣ ፍትህና ዲሞክራሲ ማውራትና መስበክ ወንጀል ከሆነ ዘመናትን አስቆጥሯል። በዚህ ዙርያም ለምን እና እንዴት ብለው የሚጠይቁ ዜጎች እጣ ፈንታቸው እስር፣ እንግልትና ሞት ሆኗል።በኢትዮጵያም ያለው ይህ እውነትን የሚፈራ እና ከእውነት ፈጽሞ የተጣላ የህወሓት አገዛዝ ለሀቅ፣ ለእውነት የቆሙትንና ሕዝብ እውነትን ያውቅ ዘንድ ያለመታከት እየሰሩ የሚገኙ ጋዜጠኞችን፣ ጦማርያንን፣ የፖለቲካ መሪዎችን እና ንጹሃን ዜጎችን ማሳደድናማሰር ቀጥሎበታል፡፡ በአጠቃላይ ለነጻነት፣ፍትህና ዲሞክራሲ የሚታገሉ ውድ ኢትዮጵያውያንን  ወያኔ ማንኛውንም ዋጋ ከፍሎ ወደ ግዞት እንዲወረወሩ ማድረግ፣ መግደልና ማሰቃየት የሥርዓቱ ተቀዳሚ ተግባር አድርጎታል። ወያኔዎች ሰባዊነት የሚባል በውስጣቸው ቅንጣት ስለሌላቸው በነጻነት ታጋይ ኢትዮጵያውያን ላይ የአካልና የሥነ ልቦና አሰቃቂ እና ኢ_ሰባዊ ድርጊት ካለ ምንም ርህራሄ ይፈጽማሉ፤ ዛሬም በመፈጸም ላይ ይገኛሉ።
የወያኔ ፈላጭ ቆራጭ፣ ዘረኛና አምባገነን አገዛዝ በህብረተሰቡ ላይ የሚያደርሰው ግፍና ሰቆቃ ከመብዛቱ የተነሳ ለእውነት እንዳንቆም እንቅፋት ሆኖብናል። ብዙዎች እውነት መናገር ቢፈልጉም እንዳይናገሩ የተለያዩ አመክንዮ ይሰጣሉ። ከፊሎችም በወያኔ አምባገነን አገዛዝ ተጠልፈው የሥርዓቱ ከዳሚና ደንገጡር በመሆን ከእውነትና ከእራሳቸው ጋር ተጣልተው የሕሊና እስረኞች ሆነው መኖር ጀምረዋል። አብዛኛው ህዝብ ደግሞ  ከእውነት ጋር ለመቆም፣ ለእውነት ለመታገል ጊዜና ወቅት በመጣባበቅ ላይ ይገኛል። ብዙ ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን የወያኔን የውንብድና አገዛዝ ተቋቁመው ለእውነት ሲሉ ሰማዕትነትን እየተቀበሉ ይገኛሉ። እውነት ዘላለማዊ ሰላም የምታጎናጽፍ ከመሆኗም በላይ ድልን የምታቀናጅ አሸናፊ ናትና።
በዋናነት ለእውነት እንዳንታገል አዚምና እንቅፋት የሆነብን ወሮበላው የወያኔ ቡድን አምባገነናዊ አገዛዝ መሆኑ ግልጽ ቢሆንም በተለያዩ ዘርፈ ብዙ ምክንያቶች ለእውነት እንዳንታገል ሆነናል። እውነትን በቃል ከመግለጽ ባሻገር በተግባር መኖር እንዳንችል ምክንያቶችን በመደርደር ከእውነት ታቅበናል። ለእውነት እንዳንታገል አዚም ከሆኑብን ምክንያቶች መካከል የተወሰኑትን ማንሳት እንችላለን።
  • ፍርሃት
ፍርሃት በአካል እና በሥነ ልቦና እንዲሁም በእለታዊ ኑሮያችን ላይ እንቅፋት ሊፈጥርብን/ሊደርስብን ይችላል ብሎ በማሰብ ከማነኛውም ድርጊት ወይም ማድረግ ካለብን ነገር መቆጠብ/መከልከል ማለት ነው። ፍርሃት ከነጻነትና ፍትህ እጦት የሚመጣ በሽታ ነው። ፍርሃት ቅጣትን ወይም ብቀላን በመፍራት ማድረግ ከምንፈልገው ሁሉ መታቀብ ማለት ነው። ፍርሃት በቡድንም ሆነ በግለሰብ ሊከሰት ይችላል፤ በሀገርና ህዝብ ላይ ግን ሊከሰት አይችልም። ፍርሃት በግለሰብና በቡድን ደረጃ ብቻም ሳይሆን በአምባገነን መንግሥታት ላይም ይከሰታል።  ስልጣንና ገንዘብ በእጅጉ ስለሚፈልጉ ይህንን ሊያሳጣ የሚችል ማንኛውንም ኃይል ይፈራሉ። ስለዚህም ህዝብን በማሰቃየት፣ በማሰርና በመግደል ስልጣናቸውን ያራዝማሉ። ግለሰቦች ይህን መከራና ስቃይ ስለሚፈሩ ለእውነት ከመታገል ወደ ኋላ ይሸሻሉ። ፍርሃት እንደ ህወሓት አምባገነን ገዥዎችን በህዝብ ላይ ስቃይና መከራን የበለጠ እንዲያጸኑ ያደርጋቸዋል፤ ብዕር ይዘው ስለ እውነት የሚታገሉትን፣ ለነጻነት ስርዓቱን የሚቃወሙ የፖለቲካ መሪዎችን፣ ጦማርያንን እና ወጣቱን ትውልድ በአሸባሪነት ተከሰው ግዞት እንዲወርዱ አድርጓቸዋል። የሃይማኖት መሪዎች ሳይቀሩ እውነት ከመናገር ይልቅ ተቋሜ ችግር ሊገጥመው ይችላል በማለት በፍርሃት ተውጠው አምልኮታቸውን እንኳ በስርዓት ማካሄድ እንዳይችሉ አድርጓቸዋል። ስለዚህ ፍርሃት በሁሉም በኩል ለእውነት እንዳንታገል ትልቅ እንቅፋት ሆኖብናል።
  • አድርባይነት/ጊዜያዊ ጥቅም መሻት
ለእውነት እንዳንታገል ከሚያደርጉ ምክንያቶች መካከል አድርባይነት አንዱ ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተዘግቦ እንደምናገኘው ኤሳው ለሆዱ ብሎ በምስር ወጥ ብኩርናውን አሳልፎ ለወንድሙ ለያዕቆብ እንደሸጠው ሁሉ ዛሬም በዚህ ዘመን ለጊዜያዊ ጥቅም ተብሎ ማንነትንና ሕሊናን በመሸጥ ለእውነት ከመቆም ይልቅ አድርባይነትን ተቀብለው ከእውነት ጋር የተጣሉ በርካቶች ናቸው። አድርባይነት ዛሬ የጀመረ ብቻም ሳይሆን በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ አሉታዊ ተጽኖ ከፈጠሩ ጉዳዮች መካከል ትልቁን ስፍራ ይዞ እናገኘዋለን። በአድርባይነት ታውረው በጣሊያን ወረራ ዘመን መንገድ እየመሩ ወደ መሀል ሀገር ከማስገባት በተጨማሪም የንጉሠ ነገሥቱ የቅርብ ባልሙዋል ከነበሩ መኩዋንንቶች እና መሳፍንቶች መካከል ሳይቀሩ ለጣሊያን ያደሩ ሰዎችን እንደምሳሌ ማንሳት ይቻላል። እነዚህ በአድርባይነት የተጠቁ ወገኖች ወይም ሹማምንቶች ህዝቡ ተቃውሞውን በማቆም መሰሪዋ ጣሊያን ይዛው የመጣችውን የይምሰል እውቀት እና ስልጣኔ በመቅሰም ሀገሩን ያለማ ዘንድ በሀሰት ለመሸንገል ሞክረዋል። መረጃ በመስጠት በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ደማቸው በግፍ እንዲፈስ ያደረጉት አድርባዮች/ጥቅመኞች ናቸው። ዛሬም አድርባኞችና ጥቅመኞች ጊዜያዊ ሥልጣንን እና የወያኔን ትርፍራፊ በመልቀም የሀሰት “ልማታዊ መንግስት” የሚል ስም ለጥፈው ሀገርን በመሸጥ፣ ታሪክን በመበረዝ፣ ህዝብን በመበደል፣ በማሰርና በመግደል ዋነኛ ተባባሪዎች እነርሱ ናቸው። ስለዚህ ከአድርባይነት ተላቀን ማንነትንና ሕሊናን በጥቅም ሳንሸጥ እንደ ዜጋ ለሀገር በማሰብ ለነጻነት፣ ፍትህና ዲሞክራሲ በጽኑ መታገል ይኖርብናል።
  • ምን አገባኝነት
እኔ ከሞትኩ ሰርዶ/ግጦሽ አይብቀል እንዳለች አህያ እኔ ከበላሁ፣ ከጠጣሁ፣ ኑሮዬ ከተሟላልኝ ለሌላውና ለሚቀጥለው ትውልድ አይመለከተኝም በማለት ለነጻነት ከሚደረገው እውነተኛ ትግል የሚርቁት ጥቂቶች አይደሉም። የራሳቸው በር እስካልተንኳኳ ድረስ የሌሎች ስቃይ፣ በደል፣ ሰቆቃ፣ እንግልትና ስደት አይመለከተንም በማለት ከሰባዊነት ወጥተው ከዳር የቆሙ በርካቶች ናቸው። ምን አገባኝነት የማንነት፣ ሀገራዊና የነጻነት ጥያቄ እንዳናነሳ እና ሆድ አምላኪዎች በማድረግ ለእውነት እንዳንታገል ያደርጋል።
  • የእውቀት ማነስ
በእውቀት የበለጸገ ትውልድ ሀገርን የመለወጥ አቅም ይኖረዋል። እውቀት ሙሉ ሰው በማድረግ ሀገርን ከማነኛውም አሉታዊ ተጽኖ  በመታደግ ወርቃማ ታሪክ መስራት ይችላል። አባቶቻችን በዚህ ተክህነውበት ነበር፤ ተፈጥሯዊና በልምድ የቀሰሙትን እውቀት ለሀገር ጥቅም በማዋል በተግባር አሳይተዋል። የሀገርን ታሪክ፣ ባህልና ቋንቋ እንዲሁም የህዝብን ምንነት መረዳትና ጠንቅቆ ማወቅ ሀገራዊ ፍቅር እንዲኖረን ያደርጋል። የበለጸጉ ሀገራት ታሪክንና ብሄራዊ ስሜትን በማስረጽ እያንዳንዱ ትውልድ ለሀገሩ ፖሊስ (እንደ ኢትዮጵያ ፖሊስ ማለቴ አይደለም) እንዲሆን አድርገዋል። ወያኔ ግን ትውልዱ እውቀት አልባ፣ ታሪክ የለሽ ለማድረግ በጎጥና በመንደር ከፋፍሎ ሀገራዊ ስሜት እንዳይኖረው በከፍተኛ ደረጃ እየሰራ ይገኛል። ይህ የእውቀት ማነስ ትውልዱ ሀገራዊ ፍቅር ተላብሶ ለእውነት እንዳንታገል አድርጎናል። ወያኔዎች “በጣሊያን ቅኝ ግዛት በተገዛን ኑሮ” የሚል ትውልድ በማፍራት ሥልጣናቸውን ለማስረዘም እየጣሩ ነው። እውቀታችንን በማዳበር እንደ አባቶቻችን ታሪክ መስራት እንኳ ቢያቅተን ታሪካችንን አስጠብቀን ለተተኪው ትውልድ ማስተላለፍ ሀገራዊ ኃላፊነት አለብን የሚል እምነት አለኝ።
  • ተስፋ መቁረጥ
የህግ የበላይነት ባልሰፈነበት፣ አምባገነን መንግሥት በሰለጠነበት፣ ድህነት በተንሰራፋበት ሀገር እውነት መናገርም ሆነ ለነጻነት መታገል ውጤት አይኖርም በሚል ተስፋ የቆረጠ የህብረተሰብ ክፍል በግልጽ ይታያል። ይህ ችግር በተለይ ወጣቱን ትውልድ ለእውነት ከመታገል ይልቅ ስደትን አማራጭ መፍትሄ አድርጎ እንዲጓዝ አድርጎታል። በኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ዘረኝነት፣ ማን አለብኝነት፣ ሙስና እና ብልሹ አሰራር በእጅጉ ገዝፎ በመታየቱ ብዙዎችን በቀላሉ የማይቀረፍ ስለሚመስላቸው ተስፋ መቁረጥ ይታይባቸዋል። ተስፋ መቁረት መፍትሄ እንዳልሆነ ቢያውቁትም ለጊዜ ጭቆናን በጸጋ ተቀብለው ሰማያዊ ኃይል በመጠባበቅ ላይ የሚገኙ ብዙዎች ይመስሉኛል። ለውጥ ለማምጣት፣ ተስፍ ለመሰነቅ፣ እውነትን ለማንገስ፣ ነጻነት፣ ፍትህና ዲሞክራስን ለማስፈን ችግሮቻችንን ተቋቁሞ ወደፊት መጓዝ ይኖርብናል እንጂ ተስፋ በመቁረጥ ለስደት እና ለባርነት መጋለጥ የለብንም።
በአጭሩ ከላይ የዘረዘርናቸው ምክንያቶች/ችግር ለወሮበላውና ማፍያ ቡድን ወያኔ አሳልፎ በመስጠት ስቃይና መከራ፣ እንግልትና ሰቆቃ፣ እስራትና ግርፋት፣ ሞትና ስቅላት እንድንቀበል አድርጎናል። ብዙኃኑ ህዝብም ይበላው ይጠጣው አጥቶ፣ ነጻነቱን ተገፎ በድህነት ይሰቃያል፤ ለእውነት እንዳንታገል ትልቅ እንቅፋት ሆኖብናል። ታሪክ እንደሚያስረዳን አባቶቻችን ለእውነት ሲሉ ህይወታቸውን አሳልፈው ሰጠዋል። ዛሬም ብዙዎች መከራን እየተቀበሉ ይገኛሉ። እኛም የእነሱን ዓርያ ለመከተል እና ሀገርን ነጻ ለማውጣት የበኩላችንን ድርሻ መወጣት ይኖርብናል። ለእውነትኛ ትግል እንደ መፍትሄ ሊደረጉ ከሚገባቸው ተግባራት መካከል የሚከተሉትን መጥቀስ ይቻላል።
v  እራስን መሆን/ ለሕሊና መኖር
ማንኛውንም ተግባር ለመፈጸም ቀዳሚው ነገር እራስን መሆን ነው። እራሳችንን በሚገባ ሳናውቅና ሳንረዳ የምናከናውናቸው ነገሮች ዘላቂነት ላይኖራቸው ይችላል። በይምሰልና በሌላ አካል ተጽኖ የምንፈጽማቸው ጉዳዮችም  እንዲሁ ውጤታቸው አያምርም። ስልጣን፣ ገንዘብ፣ ጥቅም ዜያቸውን ጠብቀው ይጠፋሉ። እራስን ለመሆን ሕሊናን ማዳመጥ ይኖርብናል። ሕሊና በእድሜ ዘመናችን ሁሉ እውነተኛ ዳኛ በመሆኑ ትክክለኛ ፍርድ ይሰጣናል፤ ሕሊና ዘላለማዊ ሰላም አልያም ደግሞ ዘላለማዊ ጸጸት ያጎናጽፈናል።  እራችንን መሆን ከቻልን ለእራሳችን፣ ለእውነት፣ ለነጻነት፣ ለፍትህ፣ ለሀገር እና ለወገን መታገል እንችላለን።  እውነተኛ ትግልን ከእራስ እንጀምር፤ ያኔ ለውጥ ማምጣ እንችላለንና።
v  ታሪክን በሚገባ መረዳት
ኢትዮጵያ አኩሪ ታሪክ፣ ባህል እና ኩሩ ህዝብ ያላት ሀገር ናት። የህዝቧ ጀግንነት፣ አይበገሪነት፣ ዳር ድንበር ጠባቂነት እና የጥቁር አፍሪካውያን ተምሳሌነት  በዓለም የተመሰከረላት ብርቅዬ ሀገር ናት። ሀገራችን የመለያየት፣ የሙስና፣ የዘረኝነት እና ተስፋ ያጣ ትውልድ መፍለቂያ አልነበረችም፤ እንደ ሀገር ዛሬም አይደለችም። ይኸን ታሪኳን ብዙ መዛግብት ይመሰክራሉና ማስተባበል አይቻልም። ቀደምት አባቶቻችን የከፈሉት ዋጋ እንዲሁ በታሪክ ሲወሳ ህያው ሆኖ ይኖራል። ታሪካችንን በሚገባ ተገንዝበን እንደ ዜጋ መክፈል የሚገባንን ዋጋ በመክፈል ለእውነት/ለሀገር መቆም አለብን። ታሪክ ሰርተን እንጂ ታሪክ በርዘን ወይም አጥፍተን ለልጆቻችን ማስተላለፍ የለብንም።
v  በእውቀት እራስን ማነጽ
ከላይ እንዳየነው የእውቀት ማነስ ሀገርን ወደኋላ ያስቀራል፤ ማንነትን ያሳጣል፤ ደካማና ፈሪ ያደርጋል። በእውቀት ከታነጽን ግን ለምን፣ እንዴት እና መቼ እንደምንታገል በደንብ ተረድተን ከዓላማችን እንደርሳለን። እውቀት በዓላማና በስልት እንድንታገል ይረዳናል። ነጻነት፣ፍትህ፣ ዲሞክራሲ እና ልማት ምን ማለት እንደሆነ እንረዳለን። እውቀት ቅድሚያ ሊሰጣቸው የሚገቡ ጉዳዮችን ለይቶ ያወጣል። እውቀት ወያኔ እንደሚያወራው ህንጻ መገንባት፣ መንገድ መስራት፣ ግድብ መገደብ፣ የሀገሪቱን ለም መሬት ለውጭ ባለሃብቶች ማቀራመት፣ ህዝብ ሃብት ንብረት አፍርቶ ከሚኖርበት ማፍለስ እና ወዘተ የዘላቂ ልማት መገለጫ እንዳልሆነ እንድንረዳ ያደርጋል። እውቀት ከምንም በላይ ለሰባዊ መብት፣ ለነጻነት፣ ለፍትህና ለዲሞክራሲ እንድንቆም እና በጽኑ እንድንታገል ከፍተኛ አስተዋጾ አለው። ስለዚህ በእውቀት መታነጽ ያስፈልጋል።
v  አንድነትን መፍጠር
ስለ አንድነት ብዙ መተንተን አስፈላጊ መስሎ አልታየኝም፤ በተግባር እንጂ በቃላት የሚገለጽ አይደለም። አባቶቻችን በተግባር አሳይተውናልና። በእውነት ወያኔን ከህዝብ ጫንቃ ላይ አሶግዶ ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ ለመገንባት ከሆነ የማስመሰል ሳይሆን እውነተኛ ህብረት/አንድነት ይኑረን። በዘር፣ በቋንቋ፣ በሃይማኖት ተለያይተን ለውጥ ማምጣት በፍጹ የማይታሰብ ነው። “ድር ቢያብር አንበሳ ያስር” እንደሚባለው ተባብረን በአንድ ላይ ከቆምን እንኳን ወያኔን ጣሊያንን ድባቅ የመቱ ኢትዮጵያውያን አርበኞች ልጆች ነንና ጊዜ ሳይፈጅብን ሀገራችንን ነጻ ማውጣት እንችላለን።  ስለዚህ አንድነት ይኑረንና ከዘረኛው ወያኔ እራሳችንና ሀገራችንን ነጻ እናውጣ!
በአጠቃላይ ለእውነት እንዳንታገል አዚም የሆነብንን ነገር አሶግደን ከእኛ የሚጠበቀውንና ጊዜው የሚጠይቀውን ማንኛውንም ዋጋ በመክፈል ለእውነት ከቆሙ እና ከነጻነትና ፍትህ ታጋዮች ጋር በመቀላቀል በይፋ እውነትን መስበክ ሀገራዊ ግዴታ አድርገን እንነሳ። እኛ በውጭም በውስጥም የምንኖር ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያን የወያኔ ተራ የሃሰት ወሬና ማስፈራሪያ ሳይገድበን ለነጻነትና ፍትህ በጽናት እንታገል። ለእውነት፣ ለሀገር፣ ለነጻነትና ፍትህ ብለው ስቃይና መከራ፣ እስራትና ግርፋት እንዲሁም ሞት የተፈረደባቸውን እውነተኛ ታጋዮችን በማሰብ  የእነርሱን ራዕይ እና ሀገራዊ ተልእኮ ከግብ ለማድረስ እኛ ለእውነትና ለእውነት ብቻ በመታገል ሀገርራችንን ከወያኔ ዘረኛና አምባገንን አገዛዝ እንታደግ።

ለእውነትና ለእውነት ብቻ እንታገል! አዚም የሆነብንን ወያኔን በነገር ሁሉ እንቃወም!!!

በፍትህ እንዲህ የተቀለደበት ዘመን ይኖር ይሆን?

ከፋሲል የኔአለም

ወንድሞቼ ዳንኤል፣ አብርሃም፣ የሽዋስና ሃብታሙ ይፈታሉ በመባሉ በጣም ደስ ብሎኛል። በመፈታታቸው ደስ እየተሰኝን የአገዛዙን ፖለቲካዊ ጨዋታ ማየቱም አይከፋም። ከዚህ ቀድም እንዳልኩት ነው፤ አገዛዙ እድሜውን የሚያራዝመው በሰላማዊ ትግል እና በትጥቅ ትግል መካከል ያለውን የሃሳብ ልዩነት በማራገብ ነው። ሰላማዊ ትግልን የሚያቀነቅኑ ሃይሎች እየጠነከሩ ሲመጡ፣ የትግሉን መሪዎች ያስርና ህዝቡ "ሰላማዊ ትግል አያዋጣንም" ብሎ ወደ ትጥቅ ትግል ፊቱን እንዲያዞር አድርጎ አደጋውን ይቀንሰዋል። የህዝቡ ትኩረት ወደ ትጥቅ ትግል ሲዞር ደግሞ፣ የታሰሩ ሰላማዊ ታጋዮችን ይፈታና የፖለቲካ ምህዳሩንም ትንሽ ከፈት አድርጎ " አዲስ የተስፋ ዳቦ" ይሰቅላል ። ህዝቡም እንደገና በሰላማዊ ትግል ተስፋ ያደርግና ትጥቅ ትግሉን ለመቀላቀል ልቡ ያመነታል- የታጋዩን ልብ እየከፋፈሉ የመግዛት ፖለቲካ ። የእነ አብርሃን መፈታት "ሃሳብን ከፋፍሎ በመግዛት የፖለቲካ ስልት " ካየነው ስሜት ይሰጣል።
የተፈቱትም ሆነ ለወደፊቱ የሚፈቱት ታጋዮች ቆራጥ የሰላማዊ ትግል አቀንቃኞች ናቸው፤ ከመጀመሪያውም የታሰሩት ሰላማዊ ትግሉ በምርጫው ላይ ተጽኖ እንደሚፈጥር ስለታወቀ ነው። ከምርጫው በሁዋላ፣ በተለይም ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ጓዙን ጠቅልሎ የትጥቅ ትግል ወደሚደረግበት በረሃ ሲወርድ፣ ህዝባዊ ንቅናቄው በከፍተኛ ደረጃ አድጓል። ይህን ህዝባዊ ንቅናቄ ለመቀልበስ አገዛዙ ፣ ሰላማዊ ታጋዮችን በመፍታትና የፖለቲካ ምህዳሩን ትንሽ ገርበብ በማድረግ የህዝቡን ልብ ለመከፋፈል የተለመደ ስልቱን ተግባራዊ ለማድረግ አቅዷል። ይህ ስትራቴጂ የተበላ እቁብ በመሆኑ ከእንግዲህ ውጤት ያመጣል ብሎ መጠበቅ የዋህነት ነው። አንደኛው የትግል አማራጭ ( የትጥቅ ትግሉ) ጉልምስና እድሜ ላይ ደርሷል፤ አገራችን በውጭ ስትወረር ካልሆነ በስተቀር ህዝቡ በዚህ ደረጃ ተነቃንቆ ትጥቅ ትግሉን ለመቀላቀል ፍላጎት ሲያሳይ ስመለከት ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። " ትግሉን መቀላቀል እንፈልጋለን" እየተባለ ከአገር ቤት በየቀኑ የሚደወለው ስልክ አስገራሚ ነው፤ እንዲያውም ስልክ የምታነሳው ባልደረባዬ " የኢትዮጵያ ህዝብ በመሉ ጫካ ከገባ ነጻ አውጪዎች ነጻ የሚያወጡት ማንን ነው? በማለት በጣም ተገርማ ጠይቃኛለች ። ከአገር ቤት ስለሚደወሉ ስልኮች ደግሞ አገዛዙ በቂ መረጃ አለው፤ የህዝቡንም ስሜት ያውቀዋል። ይህን የተባለበትን ቁማር እንደገና ለመቆመር የተነሳውም ለዚህ ነው። እኔ ሁለቱም የትግል ስልቶች በስልት ከተካሄዱ ተደጋጋፊ ናቸው ብዬ አምናለሁ። ስርዓቱን በውስጥም በውጭም በመወጠር፣ ልክ እሱ የታጋዮችን የትኩረት አቅጣጫ በመከፋፈል የነጻነት ትግሉን ለማዳከም እንደሚሞክረው ሁሉ፣ ታጋዮችም በተመሳሳይ ስልት የእሱን የትኩረት አቅጠጫ በማሳት ሊያዳክሙት ይችላሉ። የእነ ዳንኤል መፈታት ትግሉን ወደፊት ይገፋዋል እንጅ አያዳክመውም።

እግረ-መንገዴን ስለሚያብከነክነኝ አንድ ነገር ትንሽ ልበል። ሃሳቡን ዮና ብር የተባለ ጎበዝ ጸሃፊ አንስቶት አይቻለሁ ። እንደሚታወቀው በዘፈቀደ እየታፈሱ የሚታሰሩና የሚፈቱ የአገሬ ብርቅዬ ልጆች ይቅርታም ካሳም ተከፍሏቸው አያውቅም። ዘመዶቻቸው እነሱን ለመጠየቅ ሲመላለሱ የገንዘብ ፣ የጊዜና የጉልበት ኪሳራ አጋጥሟቸዋል። ልጆቻቸው የወላጆቻቸውን ፍቅር እንዳያገኙ በመከልከላቸው በአእምሮ እድገታቸው እና በወደፊቱ ህይወታቸውም ላይ ከፍተኛ አሉታዊ ተጽኖ ይፈጠርባቸዋል። ስራ መስራት ባለመቻላቸው የኑሮ ቀውስ ያጋጥማቸዋል። ሽብርተኛ በመባላቸውም የሞራል ኪሳራ ይደርስባቸዋል። የግል ህይወቴን የተመለከቱ ጉዳዮችን ማንሳት ባልፈልግም፣ ለዚህ ውይይት ስለሚጠቅም ለዛሬ አንድ ነገር አነሳለሁ። ከ5 ዓመታት በፊት፣ ወደ ሆላንድ ከመጣሁ በሁለተኛው አመት፣ የገጠመኝ አንድ ትልቅ ችግር ነበር። ኢሳት እንደተቋቋመ፣ እንደዛሬው በቂ የሰው ሃይል ሳይኖርና በየአገሩ ስቱዲዮዎች ሳይመሰረቱ፣ የሆኑ ሃይሎች "ኢሳትን ማስቆም አለብን" ብለው ተነሱና በእኔ ላይ ክስ መሰረቱ። እነዚህ እኩይ ሰዎች፣ " ህገወጥ የገንዘብ ዝውውር ይሰራል፤ ህገወጥ ገንዘብ ያገኛል፣ ሰዎችን በህገወጥ መንገድ ወደ አውሮፓ ያስገባል ወዘተ" የሚል ደብዳቤ ጽፈው ለፖሊስ አስገቡ። የተጠቀሱት ወንጀሎች በጣም አደገኛና ከአገር የሚያስባርሩ ወይም የሚያሳስሩ ናቸው። ያው ጥቆማ ቀርቧልና ፖሊስም ምርመራ ጀመረ። ሁለት ጊዜ ተጠርቼ ተጠየኩ፤ መርማሪዎች ቤታችን ድረስ መጥተው አኗኗራችንን አዩት። የባንክ አካውንቴ ተመረመረ፣ ስለኢሳት አጀማመርና የገንዘብ ምንጭ ሳይቀር ተጠየቀኩ፣ የሁዋላ ታሪኬ ሁሉ ተመረመረ። የመንግስት ክፍያም ለሁለት ወራት በግማሽ ቀነሰ። ሰዎች መከሩኝና በነጻ ጠበቃ ወደሚያቆም ድርጅት ሄድኩ። በሳምንቱ፣ ከጠበቃዬ ጋር ፍርድ ቤት ቀረብኩ። ፍርድ ቤቱ ፋይሉን አገላብጦ እንደቆምኩ ውሳኔ ሰጠ። "በአጉል ጥርጣሬ ለተደረገው ምርምራ የይቅርታ ደብዳቤ ይጻፍ፣ ለቃለምልልስ በሚል ሁለት ቀናት ስራ በመፍታቴ ክፍያ ይከፈለው፣ የታገደው የሁለት ወር ክፍያ ይለቀቅለት እንዲሁም በእሱና በቤተሰቡ ላይ ለደረሰው የሞራል ካሳ መዘጋጃው በመስፈርቱ መሰረት ይክፈለው" አለ። አጠቃላይ የገንዘብ መጠኑ ተስልቶ እንደሚነገረኝ፤ በክፍያው ላይ ቅሬታ ካለኝመ ይግባኝ እንድል፣ ስራዬን እንደሚያደንቁ አበረታተው አሰናበቱኝ። በፍጹም ማመን አልቻልኩም። ከቀናት በሁዋላ የይቅርታ እና የገንዘብ ዝርዝር የያዘ ወፍራም ደብዳቤ ደረሰኝ። ጠበቃው " ገንዘብ አንሶኛል የምትል ከሆነ ይግባኝ እጠይቃለሁ" አለኝ። (እሱም ራሱ ለአንድ ቀን ፍርድ ቤት ስለቀረበ ብቻ ጠቀም ያለ ክፍያ አግኝቷል። ) አይሆንም አልኩት። 

የ97ቱን ምርጫ ተከትሎ ከሌሎች ጋደኞቼ ጋር ለአንድ አመት ከስምንት ወር ያክል ጊዜ ታስሬ በነጻ ተለቅቄያለሁ። በታሰርኩባቸው ወራት ስራ ብሰራ ኖሮ ላገኝ የምችለውን ገንዘብ እንርሳውና በተለያዩ ምክንያቶች ከፍተኛ የሆነ የገንዘብ ኪሳራ ደርሶብኛል። ባለንብረት የነበርኩ ሰው ንብረት አልባ ሆኜ ተፈትቻለሁ፤ ለዚህ ሁሉ ግን ካሳ ሊከፈለኝ ቀርቶ የተወሰደብኝ ኮምፒዩተር እንኳ አልተመለሰልኝም፤ ስጠይቃቸው " ገና መቼ ተነካህና ነው" ብለው አሰናብተውኛል። በሰው አገር ለሁለት ቀናት ተጠርቼ በመጠየቄ ብቻ ጠቀም ያለ የሞራል ካሳ ክፍያ ሲከፈለኝ፣ በአገሬ ለረጅም ጊዜ ታስሬ ስፈታ፣ የሞራል ካሳ ሊከፈለኝ ቀርቶ የተወሰደብኝ ንብረት እንኳ በወጉ አልተመለሰልኝም። ልብ በሉ! ለአንድ ቀን ታስሬ ብፈታ ኖሮ የሚሰጠኝ የሞራል ካሳ በዚያው ልክ ይጨምር ነበር። እነርዕዮት፣ የሽዋስ፣ ሃብታሙና ሌባለመሆኑ እንጽናናለን እንጅ፣ የደረሰው ጉዳትስ ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም።ሎችም በግፍ የታሰሩት ወገኖቻችን ሁሉ ፍትህ የሚያገኙበት ቀን እሩቅ አይደለም᎓᎓

Friday 7 August 2015

የፕሬዚዳንት ኦባማ የአፍሪካ ኅብረት ንግግርና እንደምታው

August 7, 2015



የዩ ኤስ አሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ሐምሌ 21 ቀን 2007 ዓም አዲስ አበባ ውስጥ በአፍሪካ ኅብረት ጽ/ቤት ያደረጉት ንግግር በርካታ ቁምነገሮችን የያዘ በመሆኑ አንጽዖት ሊሰጠው እንደሚገባ አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ ያምናል።

ፕሬዚዳንቱ በዚህ ንግግራቸው የአፍሪቃን በተለይም ደግሞ የአገራችንን ችግሮች ነቅሰው አሳይተዋል። ሰብዓዊ መብቶች ሰው በመሆናችን ያገኘናቸው በመሆኑ በቆዳችን ቀለም፣ በተወለድንበት አካባቢ፣ በምንናገረው ቋንቋ ወይም በሌላ ማናቸውም ምክንያቶች ሊሸራረፉ የማይገቡ መሆኑን በመግለጽ “ሁላችንም እኩል ተወልደናል” በማለት ዘረኞችን አፍ የሚያዘጋ ኃይለቃል ተናግረዋል። “ሁላችንም ከአንድ ግንድ የበቀልን ነን፤ ሁላችንም አንድ ቤተሰብ ነን፤ ሁላችንም አንድ ጎሳ ነን” ካሉ በኋላ በዓለም ያለው አብዛኛው ችግር ይህንን መረዳት አለመቻላችን፤ ራሳችንን በእያንዳንዳችን ውስጥ ማየት አለመቻላችን ነው ብለዋል።
ይሁን እንጂ በብዙ የአፍሪቃ አገሮች፣ ዜጎች ነፃነታቸው የተገፈፈ መሆኑን፤ ምርጫ መኖሩ ብቻ ዲሞክራሲ ሰፈነ ማለት አለመሆኑ አብራርተዋል። ጋዜጠኞች፣ የተቃውሞ ፓለቲካ መሪዎችና ግንባር ቀደም ተሳታፊዎች፣ የሲቪክ እንቅስቃሴዎች መሪዎችን በእስር ቤት እያጎሩ ወይም በነፃነት እንዳይቀሳቀሱ እያደረጉ ዲሞክራሲያዊ ምርጫ አደረግን የሚሉ አገሮች መኖራቸው ለመግለጽ ኢትዮጵያን በዋቢነት ጠርተዋል።
ፕሬዚዳንት ኦባማ የሰላምና የደህንነት ጉዳይ ምን ያህል አሳሳቢ መሆኑን በሰፊው ከገለጹ በኋላ ለሰላም ሲባል ነፃነትን መንፈግ ሁለቱንም ሊያሳጣ የሚችል መሆኑም አስገንዝበዋል።
እድገትን በማፋጠን ዜጎችን ከድህነት ለማውጣት አዲስ አስተሳብ ያሻል፤ ለአዲስ አስተሳሰብ ደግሞ በነፃነት ማሰብ፤ ድምፃቸው የሚሰማ ዜጎች መኖር እና የሰብዓዊ መብቶች መከበር ቁልፍ ጉዳዮች መሆናቸው አጽንኦት ሰጥተውበታል። የአፍሪቃ መሪዎች ሥልጣን ላለመልቀቅ የሚሄዱትን ርቀት በማንሳት ተሳልቀውበታል፤ ሙስናም የልማትና የመልካም አስተዳደር ፀር መሆኑን አስምረውበታል።
አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ ፕሬዚዳንት ኦባማ ይኸ ቀራቸው በማይባል ሁኔታ በአህጉራችን በአፍሪቃ በተለይ በኢትዮጵያ የሰፈነው ክፉ አገዛዝ መተቸታቸው፤ ይህንን እዚያው የአፍሪቃ መዲና በሆነችሁ አዲስ አበባ ተገኝተው መናገራቸው በበጎ ይመለከተዋል። እሳቸው ያነሷቸውን ቁም ነገሮችን አድምጠው ማስተካከያዎችን የሚያደርጉ ገዢዎች ኑረውን ቢሆን ኖሮ የኛ ትግል ባላስፈለገ ነበር። ችግሩ መስማት እንጂ ማዳመጥና መተግበር የማያውቁ ገዢዎች የሰፈኑብን መሆኑን ነው።
ስለሆነም፣ አርበኞች ግንቦት 7: ፕሬዚዳንት ኦባማ በአፍሪቃ ኅብረት ንግግራቸው ሀቁን አብጠርጥረው በመናገራቸው የተሰማውን አድናቆት ይገልፃል፤ በዚሁ አጋጣሚ ደግሞ በንግግራቸው ያነሷቸው ቁምነገሮችን መደመጣቸውና በተግባር መተረጎማቸውን እንዲከታተሉ አበክሮ ይጠይቃል።
የፕሬዚዳንት ኦባማ ንግግር በሀቅ ላይ የተመረኮዘ በመሆኑ የህወሓት ሽማምንት የተከፉ ቢሆንም የኢትዮጵያን ፓለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ እውነታ የመቀየር ኃላፊነት የእኛው የኢትዮጵያዊያን ኃላፊነት መሆኑን በመረዳት፤ ለፍትህ፣ ለነፃነት፣ ለዲሞክራሲና ለአገር አንድነት ግድ ያለን ኢትዮጵያዊያን ሁሉ ተባብረን አገራችን ከዘረኛውና ፋሽስታዊ ህወሓት አገዛዝ ነፃ የማውጣት ተጋድሎዓችን አጠናክረን እንድንቀጥል አርበኞች ግንቦት 7 ያሳስባል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

Wednesday 5 August 2015

በአርበኞች ግንቦት 7 ሕዝባዊ ትግል ላይ ከየአቅጣጫው እየተሰነዘሩ ያሉ ፈተናዎችና ማርከሻ መድኃኒታቸው !

   August 5, 2015                                                                         


እግዚአብሔር ይመስገንና አሁን የነገዋን ነጻይቱን ኢትዮጵያ ለማየት መንገዱ ላይ ቆመን መራመድ የቻልንበት ሰዓት ላይ ደርሰናል፡፡ ይሄ ትልቅ ትልቅ እመርታ ነው፡፡ አሁን ባለንበት ሁኔታ ራሱ ወያኔ ተሸንፎ እንደወደቀ መቁጠር ይቻላል፡፡ የቀረው የባለሥልጣኑ የጊዜ ጉዳይ ነው፡፡ ነገ የሚሆነው ነገ እንጅ ዛሬ ስለማይሆን ብቻ ነው፡፡ ነገ ግን ዛሬ መሆኑ አይቀርምና ነገ የምንጨብጠውን ዛሬ እንደጨበጥነው መቁጠር ይቻላል፡፡
PG7 front 2
ይህ ታላቅ እመርታ እንዳይመዘገብ ወያኔ የሀገር ክህደት በመፈጸም ለጎረቤት ሀገራት ሉዓላዊ የሀገሪቱን መሬት እየቆራረሰ ከመስጠት ጀምሮ በተለያየ ጥቅም በመያዝ መሸሻ መሸፈቻ መደራጃ መንቀሳቀሻ መንደርደሪያ እሱ ሱዳንን ይጠቀምባት እንደነበረውና ከሱዳን ያገኝ የነበረውን ድጋፍና ምቹ ሁኔታዎች የሚሰጠን ጎረቤት ሀገር እንዳይኖርና እንዳናገኝ ለማድረግ ያላደረገው ነገር ያላስቀመጠው መሰናክል ያልቆፈረው ጉድጓድ አልነበረም፡፡ ይሄንን ዕድል ልናገኝ የምንችልበት አንድ ቦታ ከተገኘ የኢትዮጵያ ሕዝብ ብሶተኛ ከመሆኑና ይሄንን አጋጣሚ የሚጠባበቅ ከመሆኑ የተነሣ አርፎ ተቀምጦ የነበረውም አማራጭ ስላጣ ብቻ እንደሆነ ይሄንን ዕድሉን ባገኘ ጊዜ ግን ወያኔ ዕድሜ እንደማይኖረው በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚያልቅለት ጠንቅቆ ያውቀዋልና፡፡ መሸሻ መሸፈቻ ለማሳጣት ይሄንን ያህል ርቀት የተጓዘው ወያኔ ይህ አሁን ከባሕረ ምድር (ኤርትራ) ላይ ያገኘነውንም ለማሳጣት ለማበላሸት ይሄም አልሆን ሲለው ሐሰተኛ የፈጠራ ወሬና ሴራ በመጠንሰስ እንድንሸሽና እንዳንጠቀምበት ለማድረግ በከፍተኛ ደረጃ ሲጥር ነበር እየጣረም ይገኛል፡፡ እውነቱን መለየት ማወቅ መረዳት እስኪያቅተን ድረስ ባሕረ ምድር የመሸጉትን የነጻነት ታጋዮችን ትግል ሊያደናቅፍ ሊያሰናክል ሊያጨናግፍ የሚችሉ የሆኑና ያልሆኑ ነገሮችን መሠረት ያደረጉ ስሞታዎችን ስም ማጥፋቶችን ድምዳሜዎችን የያዙ መጣጥፎች አሁን ማንነታቸው ይበልጥ ግልጽ እየሆኑ እየታወቁ በመጡ ግለሰቦች ቀደም ሲል ግን በጣም ተአማኒነት በነበራቸው ግለሰቦችና ቡድኖች ድረ ገጾች ላይ እየተለቀቁ እየቀረቡ ትግሉን እንድንጠራጠር እንዳናምን እንድንሸሽ ከዚያም አልፎ በጠላትነት እንድንፈርጅ ለማድረግ ከባድ ከባድ ጥረቶች ሲደረጉ ቆይተዋል፡፡
ከዚህ በኋላም ወያኔ እስካለ ድረስና የዕጣ ፈንታው የመጨረሻ መጨረሻ ሰዓት የደረሰ መስሎ እስከታየው ድረስ አያደርገውም የሚባል ነገር ሳይኖረው ሊያደርገው የማይችለው ምንም ዓይነት ነገር ሳይኖር እስከ የመጨረሻ ህቅታው ድረስ የጣረሞቱን በመንፈራገጥ አቅሙን አሟጦ በመጠቀም የተቻለውን ሁሉንም ዓይነት ጥረቶች በማድረግ ይቀጥላል እንጅ ይቆማል ብላቹህ አታስቡ፡፡ አሁን አሁን ከእነዚያ ስም ማጥፋቶች የተጋነኑ ስሞታዎችና የፈጠራ ውንጀላዎች ትክክለኛ የተፈጸሙ ከሆኑትም ጀርባ የወያኔ እጅ እንዳለ ግልጽ እየሆነ መጥቷል፡፡ እኔ በእርግጥ ጥርጣሬው የነበረኝ ቢሆንም አብዛኞቻችን ይሄንን አለመገመታችን አለመጠርጠራችን ምን ያህል የዋሆች ብንሆን ነው እያሰኘኝም ነው፡፡
እነኝህን ጽሑፎች ይጽፉና በድረ ገጻቸው ይለጥፉ የነበሩ ግለሰቦችና ድረ ገጾች አንዳንዶቹ አስቀድሞ በነበረው ማንነታቸው በወያኔነት የምንጠረጥራቸው አልነበሩም፡፡ አንዳንዶቹ ግን ወያኔ በስውር ለዚሁ ዓላማው አስቀድመው ተአማኒነትን አግኝተው እንዲቆዩ አድርጎ ያዘጋጃቸው ናቸው፡፡ ቀደም ሲል በወያኔነት የማንጠረጥራቸው ወይም ወያኔ ያልነበሩትም ቢሆኑ ትናንት አልነበሩም ማለት ዛሬ አይሆኑም ማለት አይደለም፡፡ ወያኔ የመጨረሻው መጨረሻ የደረሰ መስሎ ከታየው እራሱን ለማዳን የሚቆጥበውና የሚሰስተው ምንም ነገር የለም፡፡ እንዳልኳቹህ የሀገርን ካዝና አራቁቶም ቢሆን ገንዘብ ይረጫል፣ ፍላጎታቸው ገንዘብ ሳይሆን ጉዳዮች እንዲፈጸምላቸው ለፈለጉት ጉዳዮቻቸውን ይፈጽምላቸዋል፣ ፍላጎታቸው እነዚህ ሁቱም ያልሆነና ሥልጣን ለሚፈልጉትም ከሚንስትርነት እስከ ዲፕሎማትነት (አቅናኤ ግንኙነት) ድረስ ሥልጣን እየሰጠ ይደልላል፡፡ ሌላው ቀርቶ አያገኝም እንጅ እንዲህ አድርገሀል እንዲህ ብሎ ለፍርድ ላቅርብህ ሳይለው ከሀገር ክህደት እስከ የዘር ማጥፋት ለፈጸመው ወንጀል ላይጠይቀው አስተማማኝ ዋስትና የሚሰጠው አካል ቢያገኝ የመንግሥት ሥልጣንን ሁሉ አሳልፎ በመስጠት እራሱን ለማዳን ዝግጁ ነው፡፡
አሁን በዚህ ዘመን በእነዚህ ወያኔ ያንዣበበበትን አደጋ ለማስቀረት ሳይሰስት በሚያቀርባቸው መደለያወች የማይለወጥ የማይደለል ሰው ማግኘት በጣም ከባድ እየሆነ ከመምጣቱ የተነሣ ብዙዎች ያውም በቀላል በቀላል ነገር እየተደለሉ ሕዝብን እንደካዱ ስናይ ቆይተናል፡፡ አብሶ ደግሞ ሀገርና ሕዝብ ነጻ ሆነው ማየት ቁርጠኛ ዓላማ ይዞ ሳይሆን ከግል ጥቅሙ ከዝናና እውቅና ፍለጋ አኳያ እንዲሁም ወያኔ ተወግዶ እሱም ሥልጣን ይዞ በተራው ባለ ሥልጣን ለመባል፣ ለመኮፈስ፣ ሕዝብን ከጫማው ስር ለመርገጥ፣ በግል ጉዳዩ ለገጠመው ችግር የተጣላውን ለመበቀል፣ ለማዘዝ ለመናዘዝ ወይም ደግሞ ለመብላት ምኞትና ፍላጎት ይዞ በተለያዩ የሕዝባዊ ትግል ዘርፎች ተሰማርቶ ወያኔን እየተገዳደረ እየተሯሯጠ ያለ ሰው ከሆነ እንዲህ ዓይነቱን ሰው የያዘውን ሕዝባዊ ትግል በማስካድ ወያኔ የሚፈልገውን ነገር አቅርቦለት አድርጎለት ደልሎ መጠቀሚያው አገልጋዩ እንዲሆን ለማድረግ አይቸግረውም፡፡ አሁን እያስቸገሩ ያሉ ግለሰቦች የተደለሉበት ገንዘብ ወይም ሌላ የመደለያ ነገር መጠንና ዓይነት ይለያይ እንደሆነ ነው እንጅ ከላይ የጠቀስኩትን ዓይነት ፍላጎቶች ይዘው በተለያየ መስክ ሕዝባዊ ትግል ያደርጉ የነበሩ ግለሰቦች እንደነበሩ አሁን ላይ እርግጠኛ መሆን ይቻላል፡፡
በዚህ ጽሑፍ ላይ እኛ ሳናውቃቸው ቀርተን እራሳቸውን ሰውረው ወያኔ ደልሎ ለራሱ ጥቅም እንዲያድሩ ያደረጋቸው ግለሰቦች አሳቢ መስለው የተለያየ ነገር በማውራት የትጥቅ ትግሉ እንዳይታመን እንዳይጠነክር ከግብ እንዳይደርስ ለማድረግ ይጠቀሙባቸው በነበሩ ሐሳቦች ላይ አተኩረን ዕናያለን፡፡ ወደ መሀሉም ወያኔ ገዝቷቸው ካልሆነ በስተቀር ሌላ አሳማኝ ምክንያት ስላላቸው እየተደረገ ያለውን ሕዝባዊ ትግል የሸሹ እንዳልሆኑና ምንም ዓይነት አሳማኝ ምክንያት አቅርበው ሊሸሹ ሊቃወሙ የማይችሉበትን አመክንዮም ዕናያለን፡፡
የትጥቅ ትግሉን የሚቃወሙ ወገኖች የትጥቅ ትግሉን ተአማኒነት ለማሳጣት የሚያነሡዋቸው ነጥቦች ምን ምን ናቸው? የሚለውን ቀድመን ዕንይ በአምስት ዋና ዋና ሐሳቦች ይጠቀለላሉ፡-
  1. ሸአቢያ ራሱ ስላልቻለ አቅም ስለሌለው በእኛ ተጠቅሞ ወያኔን ለመበቀል ለማስወገድ ነው እንጅ በፍጹም በፍጹም ሸአቢያ ለኢትዮጵያ በማሰብ ይሄንን ድጋፍ ሊያደርግ አይችልም፡፡ ሸአቢያ በዚህ ዓላማው ምክንያት በሚያደርግልን ድጋፍ ውጤት ቢመጣ እሱ እንጅ ኢትዮጵያ ተጠቃሚ አትሆንም፡፡
  2. የወያኔና የሸአቢያ ፀብ የውሸት እንጅ እውነተኛ አይደለም እዛ ብንሔድ መልሶ ነው አሳልፎ ለወያኔ የሚሰጠን ወይም የሚፈጀን፣ ፀባቸው የእውነት ቢሆንም ወያኔና ሸአቢያ ቀደም ሲል ከነበራቸው ጥምረት ቁርኝትና ዝምድና አንጻር ለሸአቢያ ከወያኔ ይልቅ እኛ ቀርበነው ይሄንን ያህል ውለታ ሊውልልን አይችልም፣ ሊታመንልን አይችልም፣ ሸአቢያ ለኢትዮጵያ ከወያኔ የባሰ ሸረኛ ጠንቀኛ ጠላት ነው ብሎ ከመጠራጠር፡፡
  3. የታጠቀ ኃይል የምንፈልገውን ዓይነት ለውጥ ሊያመጣ አይችልም፣ በአፈሙዝ የሚገኝ ዲሞክራሲ (መስፍነ ሕዝብ) የለም፣ የታጠቀ ኃይል የራሱን እንጅ የሕዝብን ፍላጎት አያሟላም፡፡ ከሚል ዓለም አቀፋዊውን ነባራዊ ሁኔታ ካልተገነዘበ አስተሳሰብ፡፡
  4. በዘመነ ደርግ ወያኔና ሸአቢያ ደርግን ሲታገሉ በነበረበት ወቅት የስንቅና ትጥቅ (logistics) ሌላም ድጋፍ ያደርጉላቸው እንደነበሩ ሀገራትና አንዳንድ አካላት በዚህ ዘመን ለእኛ ሊያደርግልን የሚችል ባለመኖሩ በቂ ስንቅና ትጥቅ ሊገኝ ስለማይችል ከንቱ ድካምና ከንቱ መሥዋዕትነት ነው ከሚል፡፡
  5. ሸአቢያ እኛን ይዞ ወያኔን ለማስፈራራትና ከወያኔ የሚፈልገውን ለማግኘት እንጅ የምናደርገው ትግል ፍሬ እንዲያፈራ ለስኬት እንዲበቃም በፍጹም አይፈልግም፡፡ የሚሉ ምክንያቶችን ያቀርባሉ፡፡
እነኝህ ሥጋቶች ጥርጣሬዎችና ስሞታዎች ተጨባጭና ትክክለኛ ስለመሆናቸው መፈተሽ ይኖርብናልና እንደ ቅደም ተከተላቸው እንፈትሻቸው፡-
  1. “ሸአቢያ ራሱ ስላልቻለ አቅም ስለሌለው በእኛ ተጠቅሞ ወያኔን ለመበቀል ለማስወገድ ነው እንጅ በፍጹም በፍጹም ሸአቢያ ለኢትዮጵያ በማሰብ ይሄንን ድጋፍ ሊያደርግ አይችልም፡፡ ሸአቢያ በዚህ ዓላማው ምክንያት በሚያደርግልን ድጋፍ ውጤት ቢመጣ እሱ እንጅ ኢትዮጵያ ተጠቃሚ አትሆንም” የሚባለው ነገር ሸአቢያ እንዲህ ዓይነት ሐሳብ ሊኖረው ቢችልም እንኳን የእኛ ጠላት የሆነው ለሸአቢያም ጠላት መሆኑ ጥሩ ዕድል መፍጠሩን በመረዳት የጋራ ጠላትን አንድ ግንባር ፈጥሮ ወይም ተረዳድቶ ማጥቃቱ ማጥፋቱ ስልታዊ አኪያሔድ እንጅ ጉዳቱ ምኑ ላይ ነው? ይሄንን ሥጋት የሚያነሡ ወገኖች ይሄንን ያላቸውን ሥጋት በደፈናው ከመናገር በስተቀር ወያኔ በዚህ ጥምረትና መረዳዳት ቢጠፋ ኢትዮጵያ ተጠቃሚ የማትሆንበትን ምክንያት በግልጽ እንዲህ እንዲህ ነው በማለት አያስረዱም፡፡ በደፈናው ከመጠራጠር በስተቀር የሚሉት ነገር የላቸውም፡፡ ስገምት ግን የእነሡ ሥጋት “ወያኔ ሲወድቅ በወያኔ ቦታ ሸአቢያ ይቀመጥና ውጤቱ ጉልቻ መለዋወጥ ነው የሚሆነው” የሚሉ ይመስላል፡፡ ይሄም ቢሆን ግን ሥጋቱ ተጨባጭ አይደለም፡፡ ከኢትዮጵያ ተገንጥላለች የተባለችው ባሕረ ምድር (ኤርትራ) ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ እንደ አንድ ሀገር አውቄሻለሁ ብሏታል ከተባለ በኋላ ሸአቢያ አዲስ አበባ ገብቶ ሥልጣን ሊይዝ የሚችልበት ምንም ዓይነት ሁኔታ አጋጣሚ አሠራር የሌለና ሊታሰብም የሚችል ባለመሆኑ ተደርጎ ቢገኝም በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሕግ መሠረት “ወረራ” ተብሎ የሚወገዝና ወረራው በአባል ሀገራት የትብብር ጥቃት እንዲቀለበስ የሚደረግ በመሆኑ ሥጋቱ ተጨባጭ ያልሆነና ሊገመትም የሚገባ አይደለም፡፡
2-“የወያኔና የሸአቢያ ፀብ የውሸት እንጅ እውነተኛ አይደለም እዛ ብንሔድ መልሶ ነው አሳልፎ ለወያኔ የሚሰጠን ወይም የሚፈጀን፣ ፀባቸው የእውነት ቢሆንም ወያኔና ሸአቢያ ቀደም ሲል ከነበራቸው ጥምረት ቁርኝትና ዝምድና አንጻር ለሸአቢያ ከወያኔ ይልቅ እኛ ቀርበነው ይሄንን ያህል ውለታ ሊውልልን አይችልም፣ ሊታመንልን አይችልም፣ ሸአቢያ ለኢትዮጵያ ከወያኔ የባሰ ሸረኛ ጠንቀኛ ጠላት ነው ብሎ ከመጠራጠር” ይሄ ደግሞ በጣም አስቂኝ ነው፡፡ ሰው አይጠርጥር አይጠንቀቅ አይባልም በተለይ በእኛ ሁኔታ መጠራጠርና መጠንቀቅ ተገቢና አስፈላጊም ነው፡፡ ነገር ግን የጠረጠርነውን ነገር ሊያስወግዱ ሊቀርፉ የሚችሉ ያሉና የሚታዩ ተጨባጭ ኩነቶች ባሉበት ሁኔታ አንድ ሰው በዚህ ደረጃ ተጠራጥሮ የማይመስል ነገርን ሲያስብ ብታገኙት ይሄ ሰው በጤነኛና ትክክለኛ የአእምሮ ጤና ውስጥ እንዳልሆነ እርግጠኛ ልትሆኑ ትችላላቹህ፡፡ ለእንደዚህ ዓይነት መስመር የሳተ አስተሳሰብ የሚዳረጉ ሰዎች እንዲህ ሊሆኑ የሚችሉበት ምክንያት ሲመረመር እንዲህ ብለው በሚጠረጥሯቸው በሚያስቧቸው አካላት ከባድ የሥነልቡና ጫና መታወክና መረበሽ የደረሰባቸው ሆነው ይገኛሉ፡፡ ከዚህም የተነሣ እነዚያን የሚጠረጥሯቸውን አካላት በተመለከተ ሊያደርጉትና ላያደርጉት ሊችሉትና ላይችሉት ሊሠሩትና ላይሠሩት ይችላሉ ብለው የሚያስቡት የሚገምቱት ሲመረመር ከሞላ ጎደል ትክክለኛ ሆኖ አይገኝም፡፡ ሥጋቶቻቸውና ጥርጣሬዎቻቸው ከታወከ ሥነልቡናቸው የሚመነጩና ከገሀዱ ዓለም ተጨባጭ እውነታዎች የራቁ ሆነው ይገኛሉ፡፡ ያሉ ነገሮችንም በተጨባጭ ካሉ ከተፈጸሙ መሬት ላይ ከሚታዩ ነገሮች አንጻር መመዘን መለካት የሚፈልጉ አይደሉም፡፡
ይሁንና ምናልባት ያሉበትን ተጨባጭ ያልሆነ ምናባዊ አስተሳሰብ ማሰብ ማገናዘብ መረዳት ያስችላቸው እንደሆነ ከሚል እንዲህ ለሚሉ ሰዎች ላነሣቸው የምፈልጋቸው ጥያቄዎች አሉኝ፡- ሀ. የሸአቢያና የወያኔ ጸብ የውሸት ከሆነ የዚህ የውሸት ጸባቸው ምክንያት ዓላማና ግብ ምንድን ነው? ለ. ጸባቸው የውሸት ከሆነ ወያኔና ሸአቢያ ለ17 እና ለ30 ዓመታት ደርግን ሲታገሉ ከእያንዳንዳቸው ወገን ካለቀባቸው ሠራዊት በላይ በዚያች በአጭር ጊዜ ጦርነት ባደረጉት ጦርነት ብቻ ከእያንዳንዳቸው ወገን ሰባ ሰባ ሽህ የሚገመት ሠራዊት ላለቀበት አስከፊ ጦርነትስ እንዴት ሊዳረጉ ቻሉ? ሐ. ከዚያ አሰቃቂ ጦርነት በኋላስ ባሕረ ምድር (ኤርትራ) ከዓለም ዓቀፉ ማኅበረሰብ ተነጥላ በማዕቀብ ስር ሆና ሕዝቧም ለአስቸጋሪ የድህነት ኑሮ ተዳርጎ እስከ አሁንም ድረስ በከባድ ችግር ለማለፍ እንዴት ልትገደድ ቻለች? የሚሉ ጥያቄዎችን ለራሳቸው ለመመለስ ቢሞክሩ ጭንቅላታቸውን ወደ ትክክለኛውና ጤነኛው አስተሳሰብ ለመመለስ ይረዳቸው ይሆናል ብየ አስባለሁ፡፡ አንዱ እንዲህ ዓይነት ችግር ያለበት “ጋዜጠኛ” እማ ጭራሽ ምን አለ? “ጸባቸው የውሸት ነው” ካለ በኋላ “የውሸት መሆኑንም የሚያረጋግጠው ኢትዮጵያ ለኤርትራ በየዓመቱ 250 ሚሊዮን (አእላፋት) ዶላር ትረዳለች” በማለት ያለበትን የሥነልቡናና የሥነ አእምሮ የጤና መታወክ ደረጃ ቁልጭ አድርጎ ሊያሳየን ቻለ፡፡ ወይም ደግሞ የትጥቅ ጥግሉን ለማክሸፍ ለስውር ተልእኮ ወያኔ ከቀጠራቸው ቅጥረኞች አንዱ መሆኑን እንዲህ በል ተብሎ ሊሆንም ይችላል፡፡ ምክንያቱም ይህ ያለው ነገር የፈጠራ መሆኑን የሚያረጋግጠው አስቀድመን ከጠቀስናቸው የሸአቢያና የወያኔ ፀብ የውሸት አለመሆኑን ከሚያረጋግጡት ነጥቦች አኳያ የማይመስል ነገር መሆኑና ለወሬው መረጃውን ወይም ምንጩን መጥቀስ ያልቻለ መሆኑ ነው፡፡
ሌላው “ሸአቢያ ታማኝ አይደለም ሸአቢያ ለኢትዮጵያ ከወያኔ የባሰ ሴረኛ ሸረኛ ጠንቀኛ ጠላት ነው” ለሚለውን የዋሀን ወገኖቻችንም ይሄንን አጥብቀው ያነሣሉ፡፡ ለነገሩ እነሱን ጨምሮ የወያኔ ካድሬዎችም ጭምር ሸአቢያ ከወያኔ የባሰ ጠላት ለመሆኑ የሚጠቃቅሷቸው ነገሮች አሉ፡፡ በሸአቢያ በኩል ደግሞ እነኝህ የሚጠቀሱ ነገሮች ሐሜቶችና የወያኔ የፈጠራ ወሬዎች መሆናቸውንና እሱ ግን ከድሮ ጀምሮ ለኢትዮጵያ በማሰብ ቀና ቀና ነገሮችን ሲያደርግ እንደቆየ ቢናገርም እንዲያው አንዳችም የፈጸመብን ክፉ ተግባር የለም ማለት የሚቻል አይመስለኝም፡፡ ምንስ ቢሆን ሲዋጋ የኖረው ከእኛ ጋር መሆኑ ቀረ እንዴ! ጠላቱ አድርጎ የሚያስበንን ለመጉዳት ለማጥቃት ለማዳከም የማይመኘን የማይጥርብን ምን ያህል ታጋሽ አርቆ አሳቢ በሳል ይቅር ባይ ቢሆን ነው? እንኳንና የሚጠቀሱ ነገሮች እያሉ የቱንም ያህል ደግ አሳቢ ቅኖች የነበሩ ቢሆኑም እንኳ የዚህን ያህል ሊያመጻድቅ የሚችል ሥራ ሊኖራቸው እንደማይችል መገመት የሚቻል ይመስለኛል፡፡
ነገር ግን ይህ የሸአቢያ መልካም ሥራ እውነት መሆኑን ማጣቀሻዎችን እያነሡ የመሰከሩ የአንዳንድ ወገኖች ምስክርነትንም ሰምተናል፡፡ እንደኔ እንደኔ ሠራው የተባለው ክፋት እውነት ቢሆንም እንኳን ሊያስደንቀን የሚገባ አይደለም፡፡ በጠላትነት ተፈራርጀን ስንተላለቅ የኖርን ሰዎች ሆነን እያለ አንዳችም ክፉ ነገር እንዲያደርግብን መጠበቅ የኛን የዋህነት ሊያስይ ቢችል እንጅ ሊሆን የባይገባው ነገር መደረጉን የሚያሳይ አይመስለኝም፡፡ ምን ነካቹህ? በቀንደኛ ጠላትነት ተፈራርጀን ለ30 ዓመታት እኮ ነው ጦርነት ስናደርግ የኖርነው! እኛ እነሱን ልናጠፋ እነሱም እኛን ሊያጠፉ፡፡ ዛሬ ላይ ግን ያ ትግላቸው ለስኬት አብቅቷቸው የትግላቸውን ፍሬ እየለቀሙ ያሉበት ደረጃ ላይ በመሆናቸውና ትግላቸው “ያተረፉበት ወይስ የከሰሩበት? መሆን መደረግ የነበረበት ወይስ ያልነበረበት?” የሚል ጥያቄን ለራሳቸው እንዲያነሡ የተገደዱበት ወቅት ላይ ያሉ በመሆኑና ለትግል ያስወጣቸው ችግሮች የነበሩ ከሆነም እንኳን እነዚያን ችግሮች በሌላ መንገድ መፍታት ይቻል የነበረበትን አማራጭ መፈለግ የተሻለ እንደነበር የተረዱበት ወቅት ላይ ያሉ በመሆናቸው እድሜ የማያስተምረው የማያበስለውም የለምና ከዕድሜና ከተሞክሮም በመማራቸው ከዚህ አንጻር በዚያ ወቅት በኢትዮጵያ ላይ የሠሩት የፈጸሙት ሸር ሴራ ወንጀል ተንኮል ክፋት ቢኖርም እንኳን የሚጸጸቱበት እንጅ የሚኮሩበት ባለመሆኑ እንደቀድሟቸው ሁሉ አሁንም እንደዚያው ያደርጋሉ ያስባሉ በማለት ፍጹም አትጠራጠሩ ባልልም ድምዳሜ ላይ መድረሱ ግን የሚገባ ነው ብየ አላስብም፡፡
የወያኔ ካድሬዎች ተቀጣሪዎችና የዋሀን ወገኖች የፈለጉትን ሲያወሩ ለሸአቢያ የነበረን ሥዕል ከድሮው መጥፎ መሆኑ ስለ ሸአቢያ መጥፎነት ምንም ነገር ቢባል በቀላሉ እንድናምን እያደረገን ወደ እውነቱ እንዳንደርስ የተጫነን መስሎ ይሰማኛል፡፡ እኔ እንዲያውም አሁን አሁን እየተረዳሁት የመጣሁት ነገር ቢኖር በሸረኝነት በክፋተኝነት በጠንቀኝነት በሴረኝነት በጠላትነት ወያኔ ሸአቢያን እጥፍ አስከንድቶ የሚበልጠው መሆኑን እንጅ የሚያንሰው አለመሆኑን ነው፡፡ በግልጽ አማርኛ ከመጀመሪያውም ጀምሮ ከሸአቢያ ይልቅ ወያኔ እጅግ በጣም የከፋ ሸረኛ ሴረኛ ክፉ ጠላት ነው፡፡
ይሄንን ልታረጋግጡ የምትችሉበትን አንድ ሁለት ነገሮችን ላንሣላቹህ፡፡ ከ1990ዓ.ም. የወያኔ ሸአቢያ ጦርነት በኋላ እነ አቶ ኢሳይያስ ከዓለሙ ማኅበረሰብ የተነጠሉ መሆናቸውን ታውቃላቹህ፡፡ ለምዕራባዊያን ከኢትዮጵያ ይልቅ ባሕረ ምድር (ኤርትራ) ስልታዊ (strategic) ጠቀሜታ ያላት ነች፡፡ የወያኔ ሸረኝነት ሴረኝነትና ዋሽቶ የማሳመን ችሎታ ከሸአቢያ እጅግ የላቀ መሆኑ ባሕረ ምድር እንዲህ ዓይነት ስልታዊ ጠቀሜታ ያላት መሆኗ በቀላሉ ምዕራባዊያንን ከጎኗ ማሰለፍ የሚያስችላት ሆኖ ሳለ በጠቀስነው ችሎታ ወያኔን ስላልቻሉትና በዲፕሎማሲው (በአቅንኦተ ግንኙነቱ) ላይ የበላይነቱን በመያዙ ከጨዋታ ውጪ እንዳደረጋቸው ዓይተናል፡፡ ይሄው እስከዛሬም በአሳዛኝ ተሸናፊነት ተገልለው እንዲቀሩ አድርጓቸው ቀርቷል፡፡ ከሸአቢያ ያየነው ብቃት ቢኖር የዘመኑን የፖለቲካ ጨዋታ ባለመረዳት ከሁኔታዎች ጋር እንደወያኔ እየተጣጠፈ በብልጠት ጥቅሙን ማስከበር ሳይችል በግትርነት በድርቅና መጽናቱን ብቻ ነው፡፡
ይሄ ሽንፈት በድንበር ዳኝነቱ (ኮሚሽኑ) ውሳኔ ጊዜም ተደግሟል የዳኝነቱ ውሳኔ ትክክል ባይሆንም የድንበር ኮሚሽኑ (ዳኝነቱ) ይግባኝ በሌለው ውሳኔ ባድመን ለባሕረ ምድር የወሰነ ሆኖ እያለ ከሸአቢያ ችሎታ ማነስና ደካማነት ከወያኔ መሠሪነት ሸረኝነት የተነሣ ውሳኔው ተፈጻሚ መሆን እንዳይችል አድርጎታል፡፡ እንግዲህ ሸአቢያ ሊጠቀምባቸው መብቴ ነው የሚለውን ሊያስጠብቅበት የሚያስችለው ዕድሎችና አንዳንድ ነገሮች ቢኖሩትም ከደካማነቱ የተነሣ ጥቅሙን ማስጠበቅ ያልቻለ አካል ነው፡፡ ከእነዚህ ሁለት ሁኔታዎች የምንረዳው የወያኔንና የሸአቢያን በጣም የተራራቀና የማይመጣጠን የብቃትና የችሎታን አቅም ነው፡፡ እንደምናስበውና ከየዋሀን ወገኖቻችን ከወያኔ ቅጥረኞችና ካድሬዎች በሰፊው እንደሚወራልን ሸአቢያ ከወያኔ የላቀ የበለጠ መሠሪ ሸረኛ ብቃትና ችሎታ ያለው ቢሆን ኖሮ አይደለም ከወያኔ በበለጠ በተሸለ በምዕራባዊያኑ ተመራጭ ተፈላጊ ሊያደርገው የሚችሉ ነገሮች እያሉት ቀርቶ ባይኖረውም እንኳ የበላይነቱን ይዞ ልናየው በቻልን ነበር፡፡ የሆነው ግን የተገላቢጦሹ ነው ስልታዊ ጠቀሜታ እንደሌለውና በድንበር ኮሚሽኑ እንደተሸነፈ ሆኖ ከዓለም ዓቀፉም ኅብረተሰብ ተነጥሎ ተገልሎ ይሄ ሳያንሰው ማዕቀብ ተጥሎበት በማዕቀብ እየታሸ ለመኖር የተገደደ መሆኑ ነው፡፡
እዚህ ላይ አንዳንድ ሰዎች ምናልባት ሸአቢያ ምዕራባዊያኑን ከጎኑ ሊያሰልፍ የሚችልበት ጥቅም እያለው ምዕራባዊያኑ ከሸአቢያ ጎን ሊቆሙ ያልቻሉበትና ከወያኔ ጎን ሊቆሙ የቻሉበት ምክንያት “ወያኔ አልሸባብን አጥፍቶ ሱማሌን የተረጋጋችና መንግሥት ያላት ሀገር እንዲያደርግላቸው ስለሚፈልጉ እዚያ ላላቸው ጥቅም ወያኔን ስለሚፈልጉት ነው” የሚሉ ሊኖሩ ይችሉ ይሆናል፡፡ ነገር ግን እውነት እንነጋገር ከተባለ የምዕራባዊያኑ ፍላጎትና ጥቅም እውን ሶማሊያ የተረጋጋች ሀገር እንድትሆን ነው ወይ? እንዳልሆነ ሊቢያ ላይ ምን ብለው ምን አድርገዋቸው እንደቀሩ የታየውና የምናውቀው ነው፡፡ አፈራርሰዋት የአሸባሪዎች መፈንጫ አድርገዋት ቀሩ እንጅ ቃል የገቡትን የመልሶ ማቋቋሚያ ገንዘብ ሰጥተው መስፍነ ሕዝባዊ (ዲሞክራሲያዊ) መንግሥት እንዲመሠርቱ ሲረዷቸው ፈጽሞ አልታዩም፡፡ በመሆኑም የምእራባዊያኑ ጥቅምና ፍላጎት ሶማልያን ማረጋጋትና ባለመንግሥት ማድረግ ሆኖ ባሕረ ምድር ካላት ስልታዊ ጠቀሜታነት አንጻር ከሷ ሊያገኙት የሚችሉት ጥቅም ወያኔ ሱማሌ ላይ ከሚሰጣቸው ጥቅም በልጦባቸው አይደለም ከሸአቢያ ይልቅ ወያኔ በልጦባቸው ከወያኔ ጋር ሊቆሙ የቻሉት፡፡
እናም አትጠራጠሩ የከፋው የባሰው የላቀው መሠሪ ሸረኛና ሴረኛ ወያኔ እንጅ ሸአቢያ አይደለም፡፡ ሸአቢያ እንኳንና ፈጥሮ ፈልስፎ አሲሮ ጥቅሙን ሊያስጠብቅ ይቅርና በያዘው ጥቅሙን ሊያስጠብቅ የሚያስችሉትን ዕድሎች በመጠቀም ሌላው ቀርቶ ያንተ ነው የተባለለትን ውሳኔ ጥቅሙን ማስጠበቅ ያልቻለ ምስኪን ተሸናፊ ነው፡፡ ይህ ነገር ስለ ሸአቢያ መጥፎነት የመሠሪነት ብቃትና ችሎታ ሲወሩ ሲነገሩን የነበሩ ነገሮች ሁሉ እውነትነታቸውን እንደገና መለስ ብለን እንድናይ እንድንፈትሽ የሚያስገድደን ይመስለኛል ይገባልም፡፡ ቢያንስ የተባለው ሁሉ እውነት እንዳልሆነ የሚያረጋግጥ ይመስለኛል፡፡ ጥቂቱ እንኳ እውነት ሊሆን ቢችል አስቀድሜ እንደገለጽኩት ለምን እንዴት ብሎ መጠየቅ ድርጊቱንም ማውገዝ ተገቢ ቢሆንም ከነበሩ የጦርነት ነባራዊ ሁኔታዎች አንጻር በምንም ተአምር መፈጸም አልነበረበትም ማለቱና በዚህም ላይ ተመሥርቶ የመጨረሻ ድምዳሜ ላይ መድረሱ ግን እጅግ እጅግ የዋህነትና እጅግም አለመብሰል ነው፡፡ በቤተሰብ መሀከል በጥቅም ምክንያት ወንድም በወንድሙ እኅት በእኅቷ ወንድም በእኅቱ ልጆች በወላጆቻቸው ወላጅ በልጆቹ ክህደት እየፈጸመ በሚባላበት ዘመን ጠላት ተደራርገው አንዱ ሌላውን ለማጥፋት በሚታገል በታጠቀ ሠራዊት መሀከል አንዳንድ ነገሮች መፈጸማቸው አይቀርምና ይሄና ያ እንዴት ለምን ማለትና ምንም ነገር እንዲፈጸም አለመጠበቅ ያንን የተፈጸመውን ጉዳይም የነገሮች መጨረሻ አድርጎ መቁጠር አሁንም እላቹሀለሁ እጅግ የዋህነትና አለመብሰል ነው፡፡ ምን ነካቹህ እቃቃ ስናጫወት እኮ አይደለም የኖርነው በጦርነት እሳት ስንለባለብ እንጅ፡፡ በፖለቲካ ጨዋታ ውስጥ የሚታየው ዛሬ እንጅ ትላንት አይደለም በዓለማችን ትላንት ሲባሉ ሲቧጨቁ ሲጠፋፉ የነበሩ ዛሬ ላይ ግን እፍ ያለ ፍቅር ውስጥ የገቡ በርካታ ሀገራትንና ቡድኖችን መጥቀስ ይቻላል፡፡
የሆነ ሆኖ ይሄንን ሁሉ እንዳለ ተውትና ያልገባቸው ወገኖችም ሆኑ ወያኔ የገዛቸው ቅጥረኞች የሚናገሩት ክስ አንድም ሳይቀር ሁሉም እውነት እንደሆነ እንቁጠረውና ለወያኔ ከተገዙትና ከወያኔ ካድሬዎች በስተቀር የኢትዮጵያ ሕዝብ ለወያኔ የተገዙና የወያኔ ካድሬዎች የሚያወሩትን ሳይሰማ ትግሉን ተቀላቅሎ ለድል የሚበቃበትን መንገድ ስናገር የሚከተለውን ይመስላል፡- የነጻነት ትግል ማለት ምንም ዓይነት መሰናክልና የፈተና ዓይነት እንቅፋት የሚያግደው የሚያደናቅፈው የሚገታው እንዲያግደው እንዲገታው እንዲያደናቅፈውም የማይፈቅድ ሁልጊዜም በተመቻቸ ሁኔታ ውስጥ ሳይሆን ባልተመቻቸና እንቅፋት መሰናክሎች ፈተናዎች በበዙበት ሁኔታ የሚደረግ የማይመቹ ሁኔታዎች ስላሉ በፍጹም ከመደረግ የማይቆም የማይቀር፤ ያለው ዕድል ከጠጉር የቀጠነ ዕድልም እንኳ ቢሆን በከፍተኛ ጽናት ትዕግሥትና ብልጠት እሱን ተጠቅሞ ዓላማውን ለማሳካት ከፍተኛ ትግልና ትንቅንቅ የሚደረግበት ሌላው ቀርቶ ምንም ዓይነት ዕድልም እንኳ ባይኖር ራሱን ዕድሉን ፈጥሮ ግቡን ለማሳካት የሚደረግ መራራ ትግል እንጅ እንደ ሽርሽር ምቹ ሁኔታዎች የሚጠበቁበት የትግል ዓይነት አይደለም፡፡
እናም አኔ የምላቹህ የወያኔ ቅጥረኞችና ካድሬዎች እንደሚያወሩት ሸአቢያ ከወያኔ የከፋና የኢትዮጵያ ቀንደኛ ጠላት ቢሆንም እንኳ ትግላችን የነጻነት ትግል በመሆኑና በምንም የሚመለስ ሊመለስም የሚገባ ባለመሆኑ እንኳንና ይሄንን ያህል ዕድል ተፈጥሮ ቀርቶ ምንም ዓይነት ዕድል ባይኖርም ራሱ ዋሽተን ወስልተን ቀጥፈን ሌሎች የብልጠት መንገዶችን ተጠቅመንም ቢሆን ዕድሉን ፈጥረን ግባችንን የማሳካት ግዴታ ያለብን በመሆኑ ሸአቢያ እንዳሉት ቢሆንም እንኳ ባለፈው ጊዜ እንዳልኳቹህ የልባችንን በልብ አድርገን መዋሸት ካለብን እየዋሸን “ቃል ግቡልኝ ፈርሙልኝ ማሉልኝ እንዲህ እንዲህ ታደርጉላኛላቹህ” ቢልም በፍጹም እንደማታደርጉት ልባቹህ እያወቀም አንኳ “እሽ ምን ችግር አለው! የፈለከውን እናደርጋለን! እኛ ሎሌህ ደጋፊዎችህ አጋሮችን ነን! ላንተ የማንሆነው የማናደርገው ነገር የለም!” እያልን ግጥም አድርገን በዐሥር ጣታችን በመፈረም እርኩስ ክፉ መሠሪ መሆኑን ብናውቅም “ደግ ቅንና ቅዱስ ነህ!” እያልን “ሸአቢያ ሽህ ዓመት ይንገሥ በሉ!” ቢል “ለምን ሽህ ዓመት ብቻ ለዘለዓለም ኑርልን!” እያልን ሥራችንን በመሥራት ይሄንን ክፉ ቀናችንን ዛሬን ተሻግረን ግባችንን አሳክተን ከነጻነቱ ቀን ነገ ላይ መድረስ ግድ ይለናል፡፡ ዕድል ባይኖርም ዕድል መፍጠር ይሉሀል ይሄ ነው፡፡ እንዲህ የምናደርገው ለምንድን ነው? እውነት ከሆነ ሸአቢያ የማይወደውን አቋም በመያዛችን በሸአቢያ እንዲጠፉ ተደርገዋል እንደተባሉት ወገኖች ከመጠቃት ለመዳን ነው፡፡ በዚህ የትግል ዘመን እውነት ብቻ ተናግረን ፈተናዎቻችንን ማለፍ መሻገር በፍጹም በፍጹም አንችልም፡፡ የልብን በልብ አድርገን ማስመሰልን መዋሸትን መቅጠፍን በሚገባ ልንካንበት ይገባናል ለምን ሲባል? ለዚህች ውድ ሀገራችንና ለውዱ ሕዝባችን ህልውናና ነጻነት ስንል፡፡ ተስፋ አደርጋለሁ አሁን ነገሩ የሚገባቹህ የሚገለጥላቹህ ይመስለኛል፡፡ በመሆኑም ወያኔ ወይም የወያኔ ቅጥረኛ ካልሆንን በስተቀር ሀገራችንን የምንወድ የሀገራችንንና የሕዝባችንን ነጻነት ፈላጊ ሆነን ከዚህ ሕዝባዊ ትግል ልንሸሽ ጭራሽም ትግሉት ልንቃወም የምንችልበት ምንም ዓይነት ምክንያት እንደሌለ በሚገባ በመረዳት እያንዳንዳችን እንደየችሎታችን ትግሉን በመደገፍ የትግሉ አካል መሆን አማራጭ የሌለው መሆኑን አውቀን መንቀሳቀስ ይኖርብናል፡፡
  1. “በዘመነ ደርግ ወያኔና ሸአቢያ ደርግን ሲታገሉ በነበረበት ወቅት የስንቅና ትጥቅ (logistics) ሌላም ድጋፍ ያደርጉላቸው እንደነበሩ ሀገራትና አንዳንድ አካላት በዚህ ዘመን ለእኛ ሊያደርግልን የሚችል ባለመኖሩ በቂ ስንቅና ትጥቅ ሊገኝ ስለማይችል ከንቱ ድካምና ከንቱ መሥዋዕትነት ነው” ለሚለው፡- እርግጥ ነው በዚያን ዘመን ወያኔና ሸአቢያ ሲያገኙት የነበረውን ዓይነት ድጋፍ ከእነኛው ሀገራት ማግኘት አንችል ይሆናል፡፡ ይሁንና በዚህ በኩል ያለውን ክፍተት ሸአቢያ ጦርነቱ የእኛ ብቻ ሳይሆን የራሱም መሆኑን በሚገባ ስለሚያውቅ ከምንም በላይ የኢትዮጵያን ሕዝብ ከወያኔ ነጥለው አርቀው ብቻውን ማስቀረት የሚችሉና የኢትዮጵያን ሕዝብ ድጋፍ ማግኘት ከጎናቸው ማሰለፍ የሚችሉ እንዲህ ዓይነት አጋዥ ኃይል ማግኘቱን ቢሳልም የማያገኘው ወርቃማ ዕድል መሆኑን ጠንቅቆ ስለሚያውቅ በስንቅና ትጥቅ በኩል ያለውን ክፍተት ሸአቢያ ለእኛ ብሎ ሳይሆን ለራሱ ብሎ የሚያደርገው የሚያቀርበው በመሆኑ ይሄ የሚያሳስብ ጉዳይ አይደለም፡፡ እነ አቶ ኢሳይያስ በግልጽ እንዳስታወቁት “ላደረኩላቹህና ለማደርግላቹህ ድጋፍ ምንም ዓይነት ምላሽ አልፈልግም የተረጋጋች የበለጸገች እኩልነትና ፍትሕ የሰፈነባት ሰላማዊት ኢትዮጵያን ብሎብ የተረጋጋና ሰላማዊ የቀጠናው ሀገራት እንዲኖሩ ካለኝ ጽኑ ዓላማ ያደረኩትና የማደርገውም በመሆኑ” በማለት ያስታወቁና ለመካስም ካላቸው በጎና ቁርጠኛ አቋም በመነሣት የተዋሐደችና ጠንካራ ምሥራቅ አፍሪካን ለመፍጠር ካላቸው የተቀደሰና ታላቅ ርእይ አንጻር ይሄንን ለማሳካት ያስችል ዘንድ መሠራት ያለባቸውን ሥራዎች እየሠሩ እንደሆነ አምነው ታሪክ ሠርቶ ለማለፍ እየተንቀሳቀሱ እንደሆነ ዓላማቸውን ከረጅም ጊዜና ከአጭር ጊዜ አቅድ አኳያ ግልጽ ያደረጉ በመሆኑ “እነ አቶ ኢሳይያስ ለዚህ ሁሉ ውለታ ምላሽ ሳይፈልጉ ይሄንን ሁሉ ነገር ሊያደርጉልን አይችሉም ላደረጉትና ለሚያደርጉት ምን ልንመልስ ምን ልንከፍል ነው?” የሚያስብልና የሚያሳስብ ጉዳይ አይደለም፡፡ ሁላችንም መወጣት ያለብንን ግዴታና ኃላፊነት የሚጠበቅብንንና ማድረግ ያለብንን ሥራ ነው እየሠራን ያለነው፡፡
ይሁን እንጅ ለሀገራችንና ለሕዝባችን በማሰብ ታጋይ ወገኖቻችን የማይሆን ውለታ (commitment) ውስጥ እንዳይገቡ የምንሠጋና እንዲገቡም የማንፈልግ ከሆነ ለእኛ ነጻነትና ጥቅም ሲሉ ሁለንተናቸውን አሳልፈው የሰጡ እነሱ እንኳን እንዳሉ በማሰብ እያንዳንዳችን ከተረፈን ሳይሆን ምቾታችንን ቆጠብ በማድረግ “ለእኛ ይቅርብን! እኛን ይቸግረን!” ብለንም ቢሆን ትርጉም ያለው ድጋፍ ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡ በወሬና ከንፈር በመምጠጥ ወይም በማጨብጨብ ብቻ የሚገነባ የሚሠራ ምንም ነገር የለም፡፡ ተግባር ያስፈልጋል ሀገርን መውደድ በተግባር ከምናደርገው አንዳች ነገር ውጭ በምንም ሊገለጽ አይችልም፡፡ ይሄንን ማድረግ ሳይችል ወሬ ብቻ የሚያወራ ካለን ሊያመጣው የሚችለው ለውጥ ካለመኖሩም በላይ ለወያኔ ዕድሜ መርዘም የራሱን እገዛ በማበርከቱ በሀገር ላይ የሚደርሰው ጉዳትና ኪሳራ ከወያኔ በማይተናነስ መልኩ በታሪክ ተጠያቂ እንደሆንን ልንገነዘብ ይገባል፡፡
በተለይ በተለይ ሀገር ብዙ ወጪ አውጥታባቹህ ሳይማር አስተምሮ ተቸግሮ አሳድጎ ነገር ግን በተለያዩ ገፊ ምክንያቶች (push factors) ከሀገራቹህ ተሰዳቹህ እናንተ እዚህ እንድትደርሱ ሽራፊ ሳንቲም ያላወጣባቹህን የባዕድ ሕዝብና የባዕድ ሀገር በማገልገላቹህ ሀገራቹህን ሕዝባቹህን ባለማገልገላቹህ ውለታውን ለመክፈል ባለመቻላቹህ ቁጭት የሚያንገበግባቹህ የሚቆጫቹህ የሚከነክናቹህ ዕረፍት የነሳቹህ ወገኖች ካላቹህ በተለያየ ምክንያት በረሀ ወርዳቹህ ትግሉን በአካል መቀላቀን ባትችሉም ለዚህ ሕዝባዊ ትግል ትርጉም ያለው ድጋፍ በማድረግ ሀገርራቹህን ልታገለግሉ ባለመቻላቹህ የተሰማቹህን ቁጭት ጸጸት በዚህ መወጣትና ሀገር ወገናቹህን መካስ እንደምትችሉ እንዲሁም ደግሞ  ጉልበታቹህን ዕውቀታቹህን ችሎታቹህን በባዕድ ሀገራት በማፍሰስ ዕድሜያቹህን የፈጃቹህና በዕድሜ መግፋት ምክንያት ከዚህ በኋላ በዕውቀታቹህ በጉልበታቹህ በችሎታቹህ ሀገራቹህንና ሕዝባቹህን ማገልገል የማትችሉ ጡረተኛ ወገኖች ሁሉ ካፈራቹህት ካላቹህ ገንዘብና ንብረት ቁጭታቹህን ጸጸታቹህን ሊያስወግድላቹህ ሊያስወጣላቹህ የሚችል መጠን ያለውን ገንዘብ ለትግሉ በማበርከት መንፈሳዊ እርካታን እንድታገኙ ይንን አጋጣሚ እንድትጠቀሙበት ላመለክታቹህ እወዳለሁ፡፡
የሞቀ ቤታቸውን ቅንጡ ኑሯቸውን ከፍ ያለ ደረጃቸውን ሁለነገራቸውን ጥለው ለእኔና ለእናንተ ለሚወዷት ሀገራቸው ሲሉ ነፍሳቸውን እስከመስጠት ታምነውና ቆርጠው በረሀ የገቡ ፕሮፌሰር ዶክተር ኢንጂኒየር… ወገኖቻችን ግንባር በግንባር ተፋጠው ዕላያቸው ላይ የሚወርድባቸውን ዝናብና ፀሐይ ሳይማረሩ ከሞት ጋር ተፋጠው ለማሸለብ ፋታ አጥተው ያገኟትን ተቃምሰው በረሀብ እየተፈተኑ እነኝህንና ሌሎችንም ሁሉ ዋጋ እየከፈሉ ያሉ መሆናቸውን እያወቃቹህ ከሞቀ ቤታቹህ ሆናቹህ ይህንን ማድረግ ይከብዳቹሀል ለማለት እጅግ ይከብደኛል፡፡
  1. “ሸአቢያ እኛን ይዞ ወያኔን ለማስፈራራትና ከወያኔ የሚፈልገውን ለማግኘት እንጅ የምናደርገው ትግል ፍሬ እንዲያፈራ ለስኬት እንዲበቃም በፍጹም አይፈልግም” ይሄንን የሚሉ ሰዎች ምን ይጠቅሳሉ ለምሳሌ ይሉና “የአርበኞች ግንባር ትግል ከጀመረ 16 ዓመታት ሆኖታል፡፡ ይሄንን ሁሉ ዓመታት ሲቆይ አንድም የሚጠቀስ ተግባር ለመፈጸም አልቻለም እንዲዋጋ አልተፈቀደለትም ዝም ብለው ነው እንዲቀመጡ ያደረጋቸው” ይላሉ፡፡ ይመስለኛል እንዲህ እንዲሉ ያደረጋቸው ስለትግል ስለጦርነት በቂ ግንዛቤ አለመያዛቸው ነው፡፡ ምክንያቱም አሁን ባለው ሁኔታ ውጤት ያለው ጦርነትም ሆነ ሽምቅ ውጊያ በቂ ኃይል ሳይያዝ፣ በቅጡ ሳይደራጁ፣ ሕዝባዊ ዕውቅናና ድጋፍ በበቂ ደረጃ ሳይገኝ ማድረግ ታይቶ ለመጥፋት ካሆነ በስተቀር ዘለቄታ ያለው እንቅስቃሴ ለማድረግ አይቻልም፡፡ ይሄንን ቅሬታ እንደሚያነሡ ሰዎች አስተሳሰብ ቢሆን ኖሮ የአርበኞች ግንባር ባለው አነስተኛ ኃይል እንደተመሠረተ ተንቀሳቅሶ ቢሆን ኖሮ ገና ድሮ ጠፍቶ ነበር፡፡ እንደሚመስለኝ ሸአቢያም ይሄንን እንዳያደርጉ የከለከለበት ምክንያት የተጠናከረ ኃይል እስኪኖራቸው እስኪይዙ መኖራቸው መደራጀታቸው በኢትዮጵያ ሕዝብ ዘንድ በቂ ግንዛቤ እስኪያዝበት ድረስ መጠበቅ አስፈላጊ ስለሆነ ነው፡፡ በመሆኑም ይሄንን ቅሬታ የሚያቀርቡ የትግሉ አካል የነበሩ አሁን ላይ በዚህ ቅሬታቸው ምክንያት ከዓመታት በፊት ትግሉን ጥለው የወጡ ግለሰቦች በወቅቱ ሸአቢያ ይሄንን ባለመፍቀዱ ያነሡበት ቅሬታ ተገቢ አይመስለኝም፡፡ ሸአቢያን በጣም በጥርጣሬ ዓይን ስለምናይ ብቻ እያንዳንዷን ነገር በክፋት እየተረጎምን ለተሳሳተ ድምዳሜዎች እየተዳረግን እንደሆነ ልብ ብንል መልካም ነው፡፡ ይህ ችግር በሥራችን ላይ የራሱ የሆነ እንቅፋት ሊፈጥር ይችላልና በማስተዋል ብንራመድ መልካም ነው፡፡
አሳቢ የመሰሉ ወገኖች የሚሰጡትን ምክር ሐሳብና ተቃውሞ አሳቢ ሆነው ሳይሆን ወያኔ ገዝቷቸው ቅጥረኞች ስለሆኑ እንደሆነ በምን ልናውቅ እንችላለን?
ይሄን ለመለየት በተለይ በአሁኑ ጊዜ ብዙም የሚያስቸግር አይመስለኝም ለማንኛውም እነኝህ ነጥቦች ይጠቅማሉ ብየ አስባለሁ፡-
  1. የሚናገሩትና የሚጽፉት ነገር ከረጅም ጊዜና ከአጭር ጊዜ አኳያ በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ሀገርንና ሕዝብን ሳይሆን ወያኔን የሚጠቅም ከሆነ፡፡
  2. የሚናገሩትና የሚጽፉት ነገር ትግሉን ወደኋላ ለመሳብ ለማሰናከል የሚያሴር ከሆነ፡፡
  3. አሳቢ መስለው እኩይ ሥራቸው የሚከውኑት ወሳኝና አንገብጋቢ ወቅትን (timing) እያዩ ከሆነ ማለትም ወያኔ ሥጋት በተጋረጠበት ሰዓትና አጋጣሚዎች ላይ ከሆነ፡፡ ለምሳሌ ባለፈው አርበኞችና ግንቦት ሰባት ውሕደት በፈጸሙ ወቅት፣ ሰሞኑን ማጥቃት በመጀመሩ ትግሉን ሊያጠናክሩ የሚችሉ ወሳኝ ወሳኝ ምእራፎች በሚመዘገብበት ወቅቶች ላይ ማለት ነው እነኝህ ቅጥረኞችም ይሄንን እመርታ ሊቀለብስ የሚችል ሥራን በመሥራት እራሳቸውን ጠምደው ታይተዋል፡፡
  4. እነዚህ አሳቢ መስለው የቀርቡ ግለሰቦች ሕዝባችን ነጻ እንዲወጣ የሚያቀርቡት ተጨባጭና ጠቃሚ አማራጭ የሌለ መሆኑና “ዝም ብለን አርፈን በወያኔ መገዛት ነው የሚሻለን” የሚል ዓይነት ከሆነ፡፡
እነዚህ እነዚህ ነጥቦች ቅጥረኞችን ለመለየት ይጠቅማሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡ እነዚህ ኅሊናቸውን ብቻ ሳይሆን ሁለንተናቸውን ለሆዳቸው የሸጡ ምንደኛ ግለሰቦች ለወያኔ ያደሩ ሳይመስሉ መርዘኛ ሐሳቦቻቸውን ሳይፈሩና ሳያፍሩ በነጻነት ለመናገር ለመጻፍ የሚጠቀሙበት አንድ ሽፋን አለ “ሐሳብን በነጻነት የመግለጽን መብት ከመጠቀምና ተግባራዊ ከማድረግ አኳያ” በሚል ሽፋን ነው፡፡ እንዳሉትም በትክክል ሐሳብን በነጻነት ከመግለጽና ይሄንን ዲሞክራሲያዊ መብት ለመጠበቅና ለማስጠበቅ ከሚል አንጻር ያደረጉት ከሆነ ሚዛናዊነትን ሲጠብቁ ከሁለቱም አቅጣጫዎች ጠንካራ ጠንካራ ሐሳቦችን ሲያስተናግዱ ታገኟቸዋላቹህ፡፡ ነገር ግን ከሁለቱም አቅጣጫዎች ያሉ ጠንካራ ጠንካራ የመከራከሪያ ሐሳቦችንና ተሟጋቾችን የማያስተናግዱና ሚዛናዊነትንም የማይጠብቁ ወያኔን ተጠቃሚ ወደሚያደርግ ወገን የማድላት ዝንባሌ የሚታይባቸው ከሆነ ይሄንን “ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን ተግባራዊ ከማድረግ” የሚለውን መብት ሥውር ተልእኮዋቸውን ለማሳካት ለሽፋን እየተጠቀሙበት ነውና ቅጥረኞች መሆናቸውን ልታረጋግጡ ትችላላቹህ፡፡
ለምሳሌ የቪኦኤው “ጋዜጠኛ” ሔኖክ ሰማእግዜር አቶ ኃይለማርያም ከተማሩበት ዩኒቨርስቲ ሊያገኙት ስለነበረውና በተቃውሞ ምክንያት እንዳያገኙ የተደረገውን ሽልማትና እውቅና ዘገባ በሠራበት ጊዜ ዘገባውን የሠራበት መንገድ ግልጽ በመሆኑ ማንነቱን ለመለየት አስቸጋሪ አልነበረም፡፡ ምክንያቱም ሆን ብሎ የጋዜጠኝነትን መርሖዎች ግልጽነትንና ሚዛናዊነትን ባለመጠበቅ ወያኔን ለመጥቀም በማሰብ ትክክለኛ መረጃወች እንዳይካተቱ በማድረግ ዕውነትን ያዛባ ዘገባ ሠርቷል፡፡
ይህ ሰው ይሄንን ዐይን ያወጣ ስሕተት ረዳት አብራሪ ኃይለመድኅን አበራ ቦይንግ 767 የመንገደኞች አውሮፕላንን (በረርትን) በመጥለፍ አውሮፓ ጥገኝነት የጠየቀበትን ዘገባም በተከታታይ በሠራበት ወቅት ወያኔ “አብራሪው ለረጅም ጊዜ የአእምሮ ጭንቀት ላይ ነበረ ይሄንን ያደረገው ሕመሙ ተባብሶበት ከዚህ ችግሩ የተነሣ ነው” ብሎ የደረሰበትን የፖለቲካ ኪሳራ ለመሸፋፈን ጥረት በማድረግ የሰጠውን ሐሰተኛ ስም አጥፊ መግለጫ እውነት ወይም ትክክለኛ ለማስመሰል በማሰብ አሁንም ሚዛናዊነትን ያልጠበቀና የወያኔን ጥቅም ለማስጠበቅ የጣሩ ዝግጅቶችን አቅርቦ ነበር፡፡ እናም ማንም ጋዜጠኞችም ሆኑ የብዙኃን መገናኛዎች ግልጽ የሆኑ የሞያዊ አሠራር ግድፈቶችን ሲፈጽሙ ስታዩ ያ ሰው ወያም ያ አካል ለሚከላከልለት ሀቁን ለደበቀለት (ለወያኔ) ያደረ የተገዛ የሱን ጥቅም ለማስጠበቅ የሚጥር እንደሆነ ልታረጋግጡ ትችላላቹህ፡፡ እንዲህ መሆኑ በግልጽ የታወቀ ሰው በዚያ የጥፋት ዲርጊቱ ቢገለልና ቢወገዝ ተወገዝኩ ተገለልኩ ጥቃት ደረሰብኝ ብሎ ሊከስ ሊያማርር ሊወቅስ አይችልም መብትም የለውም፡፡
ምክንያቱም ጉዳይ ከሞያዊ ግድፈት አልፎ ሞያውን በማርከስ ኃላፊነትና ግዴታውንም ለግል ዓላማውና ጉዳዩ በመተላለፍ ሞያው የጣለበትን ኃላፊነት አላግባብ ሕገ ወጥ በሆነ መንገድ በመጠቀም ማለትም ወያኔ ወይም የወያኔ አባል በመሆኑ ሆን ብሎ የወያኔን ጥቅም ለማስጠበቅ በመሞከር ጉዳዩን ወደ የመደብ ትግል ፍትጊያ አሻግሮታልና ወይም እንዲለወጥ ያደረገ በመሆኑና የኢትዮጵያ ሕዝብ ደግሞ በወያኔ ላይ ተስፋ ቆርጦ ትጥቅ ያነሣበት ሁኔታ ላይ ያለ በመሆኑ ይህ ሰው ከመወገዝም አልፎ ቦታና ሁኔታዎች ቢፈቅዱና እርምጃ ቢወሰድበትም እንኳ ድርጊቱ ሕገ ወጥ ሊሆን የሚችልበት ሁኔታ የለም፡፡ ምክንያቱም በጋዜጠኝነቱ ያለውን ከለላ በሠራው ወንጀል አጥቶታልና፤ እራሱን ከጋዜጠኝነት አውጥቶ እንደ አንድ የወያኔ ታጋይ ሁሉ የወያኔ ጥቅም አስከባሪ አድርጓልና፡፡
ይህ እርምጃ ቢወሰድበት “ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ይከበር! እያሉ እነሱ ራሳቸው ይሄንን የሚያደርግን ሰው ያጠቃሉ” ተብሎ ሊገለጽ በፍጹም በፍጹም አይደባም፡፡ ይሄ ብየና አለመብሰልና አለማገናዘብም ነው፡፡ ምክንያቱም የሰውየው ሥራ ሆን ብሎ ከሞያዊ ሥነምግባሩ ውጭ በፈጸመው ስሕተት ምክንያት ሐሳብን በነጻ ከመግለጽ ጋራ ምንም የሚያገናኘው ነገር የሌለ በመሆኑና ይህ የፈጸመው ስሕተትም እራሱን እንደ አንድ የወያኔ ወታደር አድርጎ ስላቆመ ያለውን የጋዜጠኝነትም ሆነ የሌላ መብት ከለላውን ስለሚያሳጣው፡፡ ይህ ሰው ሚዛናዊነትንና ከሁለቱም ወገኖች ጠንካራ የሆኑትን ሐሳቦች ለማስተናገድ የፈቀደ ባለመሆኑ ይልቁንም ትክክለኛ መረጃዎችን ሆን ብሎ የሰወረ በመሆኑ ሐሳብን በነጻ የመግልጽ መብትን ለቅጥፈቱ ሽፋን ሊያደርግ ስለማይችል፡፡
ይሄ “ጋዜጠኛ” ሆነ ሌላ ማንነቱ የታወቀ ሰው ኢትዮጵያዊያን በሚያደርጉት ማንኛውም ኩነት ተገኝቶ ልዘግብ ቢልና ሕዝብ የሚያውቀው በወያኔነቱ በመሆኑ ከወያኔ ጋርም ልዩነታችንን በውይይትና በሌሎች ዲሞክራሲያዊ (መስፍነ ሕዝባዊ) መንገዶች ልንፈታ የምንችልበት መንደግ ዕድል ተጠርቆሞ የተዘጋ በመሆኑና በቀረልን ብቸኛ አማራጭ በኃይል እርምጃ ለመፍታት መብታችንን ለማስከበር የተገደድንበት ሁኔታ ውስጥ ያለን በመሆኑ እንዲህ ዓይነቱን ሰው ሕዝቡ በራሱ ዝግጅቶች እንዳይገኝ የመከልከል የማስወገድ መብት አለው፡፡
“እነዚህ የሚከለከሉ (ከዚህ ዞር በሉልን አንያቹህ!) የተባሉ ጋዜጠኛም ሆኑ ሌሎች ግለሰቦች የወያኔ ደጋፊ ወይም ወያኔ እንኳን ቢሆኑ በመነጋገር ነው እንጅ ልዩነቱ መፈታት ያለበት ለምን በኃይል ይሆናል?” ከተባለ በመነጋገር ልዩነትን ለመፍታት 24 ዓመታት ለምነን ተማጽነን አይሆንም አይቻልም ተብለን መብታችንን ተነጥቀን ተነጋግሮ ልዩነትን የመፍቻው ዘመን አልፎ ሳንወድ በግድ ተገፍተን ወደ ሌላኛው የተተወልን ብቸኛ አማራጭ ማለትም በትጥቅ ትግል የኢትዮጵያን ሕዝብ ነጻነትና መብት የማስከበር አማራጭ የገባንበት ወቅት ውስጥ በመሆናችን እንደዚህ ዓይነት ሰዎችን ካጠገባችን እንዳይደርሱ መከልከል ማራቅ እንችላለን መብታችንም ነው፡፡ ሌላ እርምጃ በእነሱ ላይ ለመውሰድ ያሉበት ሀገር ሕግና ሁኔታዎች አይፈቅዱም እንጅ እንደጠላትነታቸው ሁሉ ሁሉንም ዓይነት እርምጃ በእነሱ ላይ ለመውሰድ የያዝነውና የገባንበት ሕዝባዊ ትግል ያስገድደናል፡፡
ሌሎችም ድረ ገጾችና የብዙኃን መገናኛዎችም ቢሆኑ የመጻፍ፣ የመናገር፣ ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት ሲባል የሕዝብን የጋራ ጥቅም የሀገር ደኅንነትንና ህልውናን ለመጠበቅ ለመንከባከብ የተለየ ሐሳብ ካለ እሱን ለማስተናገድ የተሰጠ መብት እንጅ ሀገርንና ወገንን የሚጎዳ ወይም ሀገርንና ወገንን የሚጎዳን አካል ጥቅም ለመጠበቅ የሚነገር የሚጻፍ ሐሳብን ለማስተናገድ የተሰጠ መብት አይደለም፡፡ በግልጽ አማርኛ ወያኔ የዚህች ሀገርና የሕዝቧ ቀንደኛ ጠላት እንደመሆኑ ማንም ሰው የወያኔ ቅጥረኛ ሆኖ የወያኔን ጥቅም ለማስጠበቅ ማለትም ከድሮ ጀምሮ የራሱን ቡድናዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ሲል የሀገርን ሕልውናንና የሕዝብን ደኅንነትና ጥቅሞች ለመጉዳት ለማጥቃት ለአደጋ ለመዳረግ የሚያሴረውን የወያኔን ጥቅሞች ለማስጠበቅ የተሰጠ መብት አይደለምና በዚህ ሽፋን ይሄንን ሊያደርጉ እንደማይችሉ ጠንቅቀው ሊያውቁት ይገባል፡፡ የትም ሀገር ቢሆን ያለው አሠራር ይህ ነው፡፡ አሜሪካም ብትሆን ዜጋዋ የሀገሪቱን ብሔራዊ ጥቅም የሚጎዳ ሥራ ሠርቶ “ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት ነው” ቢል አትሰማውም “ብሔራዊ ጥቅሜን ለአደጋ ዳርጓል የሀገርንና የሕዝብት ደኅንነት ለአደጋ አጋልጧል ወይም ለጠላት ተቀጥሮ በመሥራት” ወንጂላ እንደ ስኖውደን ታሳድደዋለች እንጅ ሐሳብን የመግለጽ ነጻነት ነው ብላ አትምረውም፡፡
እነኝህ አካላት ሞያዊ ሥነምግባራቸውን በመጣስ የሀገራችንን ጠላት የወያኔን ጥቅም ለማስጠበቅ ከወያኔ ጋር በማበር የወያኔ ቅጥረኛ በመሆን መረጃን በማዛባት እንደሚንቀሳቀሱ ባወቅን ጊዜ ይሄንን መብት አጥተዋልና ይሄንን መብት ለሽፋን መጠቀም አይችሉም፡፡ አሜሪካ ጥቅሟን የሚጎዳባትን ሰውና ዘገባ የሀገርና የሕዝብ ጠላት አድርጋ እንደፈረጀችና እንደምታሳድድ ሁሉ እኛ ኢትዮጵያዊያንም የሀገራችንንና የሕዝባችንን ብሔራዊ ጥቅሞች የሕልውናችንና የደኅንነታችን ጠላት የሆነው ወያኔን ያገለገለ ወይም የደገፈ ጋዜጠኛንም ሆነ ማንኛውንም ሌላ አካል ሁሉ የሀገራችንና የሕዝባችን ጠላት እንፈርጃለን እናሳድዳለንም፡፡ በግልጽ አማርኛ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሁሉም ዕድሎች ተዘግተውበት መብቶቹን ለማስከበር ተገዶ የትጥቅ ትግል ውስጥ የገባበት ሁኔታ ውስጥ ያለ በመሆኑ ማንኛውም ሰው ወዶና ፈቅዶ የወያኔ አባልና ደጋፊ የሆነ ካለ ይህ ሰው ሊሸሸግበትና ሊታደገው የሚችል ምንም ዓይነት ዋስትና እንደሌለው ጠንቅቆ ሊያውቅ ይገባል፡፡
ይመስለኛል በሌላም በኩል ወይ ድፍረት ቁርጠኝነት አጥተው ይሁን ወይ ደግሞ ቅድሚያ የሚሰጡት ቤተሰባዊም ሆነ ሌላ ጉዳይ ኖሮባቸው ብቻ በአንድም በሌላም ምክንያት በትጥቅ ትግሉ መሳተፍ የማይችሉ ከመሆናቸውና የትግሉ አካል ካለመሆናቸው የተነሣም “የሚመጣው ለውጥ በግል እኔን አያካትተኝም በተዋናይነት ቦታ ሰጥቶ አያሳትፈኝም” ከሚል ሥጋትና “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” ከሚል ለራሳቸውም ለወለዷቸው ልጆችም ለሀገር ለወገንም ፈጽሞ የማይጠቅም የደነቆረና በሽተኛ የሆነ የራስወዳድነትና የምቀኝነት ጠንቀኛ አስተሳሰብ ወያኔ ወይም የወያኔ ደጋፊም ሳይሆኑ እየተደረገ ያለውን የትጥቅ ትግል የሚቃወሙ ወይም የማይደግፉ ያሉ ይመስለኛል፡፡ እንዲህ የሚያስቡ ግለሰቦች የማሰብና የማገናዘብ ችሎታ በጣም የወረደ ነው፡፡ ከተቆጣጠራቸው ክፉ የምቀኝነት መንፈስ የተነሣ እንደ ዜጋ እራሳቸውን ጨምሮ ተጠቃሚ የሚያደርጋቸው አስመስጋኝና አስከባሪ ሥራ በሌሎች ሲደረግ ሲያዩ ዐይናቸው ደም ይለብሳል፡፡ ዜጋ እንደመሆናቸው የዜግነት ግዴታ እንዳለባቸው ተረድተው እንደ ዜጋ ለሀገሬ ምን ማበርከት ይጠበቅብኛል? ሀገሬ ወገኔ ከኔ ምን ይጠብቃሉ? ብለው ራሳቸውን በመጠየቅ የዜግነት ግዴታቸውን ለመወጣት አስበው በቅንነት ተንቀሳቅሰው የሚያውቁ አይደሉም፡፡ ከተንቀሳቀሱም ለዝና ወይም ድብቅ የሆነ ሌላ የግል ጥቅማቸውን ለማስከበር ለማግኘት እንጅ ለሀገርና ለወገን በማሰብ አንዳች ነገር አድርገው አያውቁም፡፡
እነኝህ ግለሰቦች በሚቃወሙበት ጊዜ ለመቃወማቸው ምክንያት ሲጠየቁ ብዙ ጊዜ ሊያቀርቡት የሚችሉት ምንም ዐይነት ምክንያት የላቸውም፡፡ ካቀረቡም የረባ አይሆንም፡፡ ወይ እራሳቸው አይሠሩትም ወይ ደግሞ ሌላው እንዲሠራው አይፈልጉም አይፈቅዱም፡፡ ሌላው ሠርቶት ሲደነቅ ሲከበር ሲያዩ በሰይጣናዊ የቅናትና የምቀኝነት መንፈስ ቆሽታቸው ይደብናል፡፡ እንኳንና ለልጆቻቸው፣ ለሀገር፣ ለወገን ለራሳቸውም እንኳን ቢሆን ምን ቢሆን እንደሚበጅ በቅጡ የሚያውቁ ሰዎች አይደሉም፡፡ የሚገርመው ለምን እንዲህ እንደሚሆኑ ራሳቸውም እንኳን አያውቁትም፡፡ የሚያደርጉት ነገር ከግል ሕይዎታቸው ጀምሮ እስከ ሀገር ድረስ እንደሚጎዳ እንደማይጠቅም እንኳንና እራሳቸው ሊያስቡት ተነግሯቸውም እንኳ አይገባቸውም እንዲገባቸውም አይፈልጉም፡፡ በጣም የሚገርመው እንዲህ ዓይነት ክፉ የቅናትና የምቀኝነት መንፈስ ተማሩ በሚባሉት የሚብስ መሆኑ ነው፡፡ ችግሩ ግን የተማረ ከሚባለው ጀምሮ መሀይም እስከሚባለው ዜጋ ድረስ በየቦታው አለ፡፡ ሥራ እንዳይሠራ ብዙ ያውካሉ፡፡ በተለይ የተማሩ የተባሉቱ ተቃውሟቸውን የትም ሲያቀርቡ ተቃውሟቸው በቂና አሳማኝ ምክንያት ይኖረው ይሆናል በሚል ግምት ብዙ ጊዜ ሕዝብ ይሰናከልና ድጋፍ መስጠት ላለበት አካል ድጋፍ ይነፍጋል፡፡ በእንደዚህ ዓይነት ችግር ምክንያት የተቀደሰ ዓላማ ተይዞ ስንት ሊሠሩ የሚሞከሩ በርካታ ሥራዎች ከንቱ ሆነው ይቀራሉ፡፡ የእነዚህን ችግር ያለባቸው ግለሰቦች ፈተና ተቋቁሞ ሥራ መሥራት የተቀደሰን ዓላማ ከግብ ማድረስ እንደ ዕድል አልፎ አልፎ የሚገኝ እንጅ በብዛት የሚታይ አይደለም፡፡ እናም ከዚህ ችግራቸው የተነሣ ሕዝባዊ ትግሉን የሚቃወሙ ወገኖች ሊኖሩ እንደሚችሉ እገምታለሁ፡፡ የሆነ ሆኖ የሚያቀርቡት ተቃውሞ ከወያኔነት አንጻር ባይሆንም ቅሉ በሕዝባዊ ትግሉ ላይ የሚያደርሱት ጉዳት ከቅጥረኞች የማይተናነስ እንዲያውም የባሰ በመሆኑ እነሱንም እንደ ወያኔ ሁሉ የሀገርና የሕዝብ ጠላት አድርጎ መቁጠርና የሚፈጽሙትንም ጥቃት መከላከል ግዴታ መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡
የተያያዝነው ትግል የሞት ሽረት ትግል ነው፡፡ ጨዋታ አይደለም የተያዘው ሀገርንና ሕዝብን ከጠባብ ጨካኝ ደንቆሮ አንባገነን አገዛዝ መዳፍ ፈልቅቀን ነጻ ለማውጣት ነው እየታገልን ያለነው፡፡ የግድ የሚወሰዱ ቆራጥ አቋሞች ይኖራሉ፡፡ የመረጥነውን የማውረድ መብቱ እያለን የመረጥነውን መንግሥት በኃይል ለማውረድ መሥዋዕትነት የምንከፍልበት ምንም ምክንያት የለንም መርጠን ያስቀመጥነውን መንግሥት ማንም በኃይል እንዲያስወግደው አንፈልግም አንፈቅድምም፡፡ አገዛዙ ያልመረጥነው በመሆኑና በኃይል የተጫነን ይህንን አገዛዝ በምርጫ ልናወርደው ልናስወግደው የሚያስችለን ሥርዓት በፍጹም የሌለ ስለሆነ እንጅ፡፡ ከተረባረብን በእርግጠኝነት ተሳክቶልን በቅርብ ጊዜ ሀገርንና ሕዝብን ነጻ እናወጣለን፡፡ ባለመብሰላችን እየሆነና ሊሆን ያለውን በማስተዋል አቅቶን አርቀንና ግራ ቀኝ መመልከት ተስኖን እያንዳንዳችን መወጣት ያለብንን ግዴታና ኃላፊነት መወጣት ቸግሮን መረባረብ መተባበር ካልቻልን ደግሞ ወያኔ እንደሚለው ለ60 ዓመታት ብቻ አይደለም ለዘለዓለሙ ባልመረጥከውና በኃይል ጫንቃህ ላይ ተጭኖ በነፍስ በሥጋህ እየተጫወተብህ ባለው አገዛዝ በወያኔ የጭቆና ቀንበር ስር ተጠፍንገህ ሰብዓዊ ክብርህን አተህ እየተዋረድክ የባርነት ኑሮህን እየኖርክ ይንንም የውርደት ኑሮ ለልጅህ እያወረስክ ፍዳህን ትቆጥራታለህ! በእርግጠኝነት ይህ እንዲሆን የሚወድና የሚደቅድ ኢትዮጵያዊ አይኖርምና ያለን ብቸኛ አማራጭ መረባረብ ነው እንረባረብ ወገን!!!
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!
ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው

የሀይማኖት መብታችን የሚከበረው በነፃነት ትግል ነው! ከሰማያዊ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ


ከሰማያዊ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ

ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘበት ጊዜ ጀምሮ ለስልጣን ለሚያሰጋው ድርጅትና ተቋም ለራሱ ስልጣን የሚበጀውን ሌላ ድርጅትና ተቋም በመፍጠር እንዲሁም ኢትዮጵያውያንን በቋንቋ ልዩነት ከፋፍሎ ሲገዛ ቆይቷል፡፡ ለመምህራን ማህበር ለመምህራን ሳይሆን ለእሱ የሚመች ማህበር፣ ለፖለቲካ ድርጅቶች ለህዝብ የሚቆም ሳይሆን ለአገዛዙ መሳሪያ የሚሆን ድርጅት፣ ለሰብአዊ መብት ድርጅቶችም እንዲሁ ለኢትዮጵያውያን የሚቆሙ ሳይሆን ከእሱ ጋር የሚወግኑ ድርጅቶችን በማቋቋም እውነትና ከእውነተኞችን ሲታገል ኖሯል፡፡ ከዚህም አልፎ አሁን በሀይማኖት ውስጥ ለእሱ የሚመች ሌላ ሀይማኖት በመቋቋም ላይ ነው፡፡
የቆየው የአገዛዙ እኩይ ባህሪ ስልጣን ላይ ለመቆየት በቂ ሆኖ ባለመገኘቱ በሀይማኖት ተቋማትም ጭምር ጣልቃ በመግባት እሱ የሚፈልገውን እምነት በመደገፍ፣ ሌላው ላይ ቅጣት በመጣል ላይ ይገኛል፡፡ ለዚህም አገዛዙ ባለፉት ሶስት አመታት በሙስሊሙ ማህበረሰብ ዘንድ እያደረሰ ያለውን የሰብአዊ መብት ጥሰት መመልከት በቂ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ኢህአዴግ ጣልቃ ከመግባት እንዲቆጠብ ንቅናቄ ማድረግ በጀመሩበት ወቅት ስርዓቱ ለመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴው እውቅና ሰጥቶ ሲደራደር እንደነበር ይታወቃል፡፡ ይሁንና በሚፈልገው መንገድ አልሄድለት ሲል የመፍትሄ አፈላላጊ ኮሜቴ አባላትን አስሯል፡፡ ‹‹አሸባሪ›› ብሎ ከሷል፡፡ ሀምሌ 27/2007 ዓ.ም እውቅና ሰጥቶ ሲደራደራቸው የነበሩትን የሙስሊሙ ማህበረሰብ አመራሮች ከ7 እስከ 22 አመት እስራት ፈርዶባቸዋል፡፡ ይህ የሚያሳየው ‹‹ሽብር›› የሚባለው ክስ ስርዓቱ ያልፈለገውን የሚያስርበት መሆኑን ነው፡፡ በዚህ ክስ ሰላማዊ ታጋዮችን ጥፋተኛ የሚለው ፍርድ ቤትና ህግም የአገዛዙ ዋነኛ መሳሪያ ሆነው ቀጥለዋል፡፡ 
ሰማያዊ ፓርቲ የሙስሊሙ ማህበረሰብ ጥያቄ የፖለቲካ ሰነድ ከሆነው ህገ መንግስት ላይ በቅዳሚነት ከሚሰፍሩት መብቶች መካከል አንዱ የሆነው የሀይማኖት (የሰብአዊ መብት) ጥያቄ እንደሆነ ያምናል፡፡ ይህም በመሆኑ ስርዓቱ ለሙስሊሙ ማህበረሰብ ይህን እመን፣ ይህን አትመን በሚል እምነት ወደመወሰን ጣልቃ ገብነት ከገባበት ጊዜ ጀምሮ ትክክል እንዳልሆነ ለማስገንዘብ ጥሯል፡፡ ሆኖም ለሀገርና ለህዝብ ከሚጠቅመው ሀሳብ ይልቅ የስልጣኑ ጉዳይ ብቻ የሚያሳስበው ኢህአዴግ የሚሰማ ሆኖ አልተገኘም፡፡ ኢህአዴግ ሰላማዊ ታጋዮችን በፈጠራ ሽብር ወንጀል ከሶ ሲያስር፣ ለፖለቲካ ድርጅቶችና ለተቋማት ለእሱ የሚመቹትን በመፍጠር አባዜው ሀገራችንን አደጋ ውስጥ እየጣላት ይገኛል፡፡ ይህ አልበቃ ብሎት በሀይማኖት ጉዳይ ጣልቃ በመግባት ሌላ አደጋ ውስጥ እንድንገባ እያደረገም ነው፡፡ 
ከአሁን ቀደም ካሉት በርካታ ተሞክሮዎች ለመረዳት እንደሚቻለው አገዛዙ ምክርና ትችት አዳምጦ ማስተካከያ ከማድረግ ይልቅ በእልህና በማን አለብኝነት እያባባሰ መቀጠሉ የማይቀር ነው፡፡ አሁንም በሙስሊሙ ማህበረሰብ ላይ የፈፀመው በደል ተተችቶ የሚያስተካክለው ነው ብሎ ለመገመት ይከብዳል፡፡ ይልቁንም ሀገራችንን አደጋ ላይ ለመጣል በየ ጊዜው የፈፀማቸውና ወደፊትም ለመፈፀም ወደኋላ የማይላቸውን ችግሮች ለመቅረፍ ብቸኛው አማራጭ በጋራ መታገል ነው፡፡ የችግሮች ሁሉ ምንጭ ስርዓቱ እንደመሆኑ ለየብቻችን የምናስመልሳቸው መብቶች አይኖሩም፡፡ የሰብአዊም ሆነ ዴሞክራሲያዊ መብቶቻችን ልናስከብር የምንችለው ዋነኛው የችግሮቹ ምንጭ የሆነውን ስርዓት ታግለን ለኢትዮጵያችን የሚበጅ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ስንገነባ መሆኑን ተገንዝበን ሰላማዊ የነፃነት ትግሉን መቀላቀል ይኖርብናል፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ የሙስሊሙ ማህበረሰብ አገዛዙ እየፈፀመበት ያለውን በደል በመቃወም ሲያደርግ የቆየውን ሰላማዊ ትግል ያደንቃል፡፡ በኮሚቴው ላይ የተወሰደው እርምጃ የሙስሊሙ ማህበረሰብ ይበልጡን ትግሉን አጠናክሮ፣ ከሌሎች ወገኖቹ ጋር ተባብሮ አምባገነንነትን ከምንጩ ከማድረቅ ውጭ ሌላ አማራጭ እንደሌለው ትልቅ መልዕክት የሚያስተላልፍ ነው፡፡ በመሆኑን ሰላማዊ ትግሉን በመቀላቀል በሰብአዊነታችን፣ በዜግነታችን ከዚህም አለፍ ሲል በሀገራችን ላይ እየፀመው ያለውን አደጋ በመገናዘብ፣ የፖለቲካ ትግሉን እንዲቀላቀል ጥሪውን ያቀርባል፡፡

ኑ! ራሳችን ነፃ በማውጣት የሀገራችንን እጣ ፋንታ እንወስን!
ሀምሌ 29/2007 ዓ.ም
አዲስ አበባ


Tuesday 4 August 2015

አፈትልኮ የወጣ እዉነት!! አንዳርጋቸዉ ጽጌ ተናገረ!!


ማን ይሆን ብዬ ተደናገጥኩ!! ነገር ግን በእጅ ምልክት ድብቅ እዉልብልቢት የጠራኝን ሰዉ ተከትዬ ወደ መጸዳጃ ቤት ዘለቅኩኝ ሴት መሆኔን የዘነጋዉ መለሰኝ ሰዉዬዉ በቀጥታ ወደ ወንዶች ሽንት ቤት አመራ እኔ ግን ወደዛ መግባት ስለፈራዉ ባለሁበት ቆምኩ ከጥቂት ቆይታ ሰከንዶች በኋላ ተመልሶ ወጣ መካከለኛ ቁመትና ደንዳና ሰዉነት አለዉ ከላይ ጥቁር ጃኬት ደርቦ ጥቁር የጨርቅ ሱሪ ታጥቋል በስሱ ተመልክቶኝ በንገቱ ወደ መጸዳጃ ቤት አመላከተኝና ዘመመ አሁን ፈራሁ በርግጠኝነት የሆነ ነገር መጸዳጃ ቤት ጥሎ እንደሄደ ጥርጥር ብጤ ገባኝ ቢሆንም የሰዉዬዉ ሁኔታ አስፈራኝ ልክ እንደ ሌባ ወይም የሆነ ነገር እንደሚደበቅ ሰዉ ነበር ሁኔታዉ። እንደምንም እራሴን አበራትቼ ወደ ወንዶቹ ሽንት ቤት ዘለቅኩ ታዲያ ይህ ሰዉ አንዳች ነገር ጥሎ እንደሚሄድ በመጠራጠሬ አይኖቼን ዙሪያ አማተርኩ በትክክል ልክ ነበርኩ አንድ የተጤቀለለ ወረቅት በገፋሁት በር ሲንፏቀቀ ተመለከትኩ በቀጥታ ወረቀቱን አንስቼ ስወጣ ያዉ ወረቀቱን የወረወረዉ ግለሰብ እና ሌላ ሰዉ ሽንት ቤቱ በር ላይ ቆመዉ ተመለከትኩ እናም ” እህት አንዴ ቆይ! ” ተባልኩ እኔም ባለሁበት ቆምኩ ያዉ እራሱ ግለሰብ ወደኔ ጠጋ አለና ” ይህ የወንዶች ሽንት ቤት ነዉ ምን ታደርጊያለሽ ” አለኝ ” አረ እኔ! ተሳስቼ ነዉ። ደግሞ ሽንቴን ወጥሮኝ.. ስለነበር ” ብዬ ዝም አልኩ ” እሺ እዚህ አካባቢ ምን ታደርጊያለሽ ” አለኝ ” ማን! እኔ ” አልኩት ” አዎ! አንቺ ” ” እኔ የብሄራዊ መረጃ ደህንነት አባል ነኝ!! እገሊት እባላለዉ ” አልኩት ” በጣም ጥሩ መታወቂያ ልታሳይኝ ትችያለሽ ” አለኝ አዎ! አልኩትና ሰጠሁት መታወቂያዬን እንዳየዉ ድንጋጤ ይነበብበት ጀመር እጁ እየተንቀጠቀጠ መልሶ ሰጠኝ ነገሩ ስለገባኝ ፈገግ ብዬ “” አታስብ አይዞን “” ብዬዉ ወደ መደበኛ ስራዬ አመራሁ።

ለግዜዉ ስሜ ይቆያችሁና ከሽንት ቤት የተገኘዉን ደብዳቤ ግን ለናንተ እንዲደርስ እንዲህ አሰብኩኝ
“” ይህን እዉነት ለሚያገኘዉ ሁሉ እዉነት በተወለደችበት እለት የእዉነት ጠላቶች እዉነት ነዉ ብለዉ የሚያምኑበትን የእኛን እዉነት የእነርሱን ዉሸት እንድንቀበል በሚደረግ ግብ ግብ መሐከል ስለሚንገላታ አንድ ግለሰብ እንዲያስብ ይሁንለት “” እኔ በምኖርበት ዘመን የተፈጠረዉ ትዉልዴ ልጅ ነኝ፣ አንዲት የምታሳዝን ሐገር ልጅ፣ አንዲት በጥቂቶች እጅ ወድቃ የምትንገላታ እናት ልጅ፣ አንዲት የልጅ ያለህ እያለች ለምትጣራ ደርባባ እናት የቃተትኩ ልጅ፣ ሽማግሌ ልጅ፣ አዛዉንት ልጅ፣ የእናቴ ልጅ ሆኜ ደግሞ ሌላ ልጅ ወደዚህ ምድር ያመጣሁ ስለነጻነትም ልጄን በበረሐ ላይ የወለድኩ ያሳደግኩ ፣ ለእርሷ ለእናቴ እዳ ሆኜ እንዳልቀር ለትዉልዴ ልስራ ያልኩኝ ነጻነት ተጠምቼ በነጻነት ምክንያት ተላልፌ የተሰጠዉ ልጅ እና የልጅ አባት’፤ አዛዉንት የነጻነት ጥመኛ የትዉልድ እረሃብተኛ።
እኔን ለማጥፋት ያልተቆፈረ አልነበረም እነ ይሁዳ አሳልፈዉ ሰጡኝ። ነገር ግን እኔ ብኖርም ባልኖርም የነጻነት ብርሐን አንድ ቀን ቦግ እንደሚል አዉቃለዉ!!! እጄ በእጃቸዉ ላይ ከወደቀበት እለት አንስቶ እኔ የምባል ሰዉ መሞቴን እወቁ!! በዚህ አለ!! እንዲህ ሆነ!! ይህን አደረገ!! ይህን ተናገረ!! ቢሏችሁ ሁሉ እኔ መሞቴን እወቁ!! የሞተን የተገደለን ሰዉ የተገደደን ሰዉ አትከተሉ እንዳሻቸዉ ሊያደርጉና ሊያደርጉብኝ ዛሬ በእነርሱ እጅ ላይ ነኝና እኔኝ እርሱኝ !! ለእናንተ በትግል ነጻ ለመዉጣት ለምትተባበሩ ሁሉ አደራዬን አስተላልፋለዉ ኢትዮጵያዬን አደራ! ህዝቤን አደራ! ነጻነትን አደራ! ከንግዲህ እያንዳንዳችሁ እስከሞት ድረስ የታመናችሁ ሁኑ በመሰዋትነት የሚገኝን ክብርና ሰላም ለሌሎች ስጡ! እነዚህን ግን ነቀርሳዎች ሳትነቅሉ እኝዳትተኙ እንዳታንቀላፉ ።
ደህና ሁኑ ድል ለመላዉ ህዝቤ !

በሙስሊም እንቅስቃሴ መሪዎች ላይ የተሰጠውን ፍርደገምድል ፍርድን እናወግዛለን!

August 4, 2015
def-thumb
የህወሓት አገዛዝ የሚዘውረው የይስሙላ ፍርድ ቤት ዛሬ ሀምሌ 27 ቀን 2007 ዓ.ም. በሙስሊም ወገኖቻችን መሪዎች ላይ ፍርደገምድል ውሳኔ ሰጥቷል። በዚህ ውሳኔ መሠረትም የእምነት መብቶቻቸው እንዲከበሩላቸው በሰላማዊ በሆነ መንገድ የጠየቁ ወገኖቻችን መሪዎች እስከ 22 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት እንዲቀጡ ወስኗል።

ሙስሊም ወገኖቻችን ጥያቄዎቻቸው ሰላማዊ በሆነ መንገድ ሲያቀርቡ ቆይተዋል። ሥርዓቱ ያደረገውን ተደጋጋሚ ትንኮሳዎችን ተቋቁመው “ድምፃችን ይሰማ!” የሚል አቤቱታ ከማቅረብ የዘለለ አንዳችም የኃይል እርምጃ ወስደው አያውቁም። ሆኖም “በደል ደርሶብኛልና ልሰማ” ብሎ አቤቱታ ያቀረበ ሕዝብ መሪዎችን እስከ ሃያ ሁለት ዓመታት በእስር መቅጣት የአገዛዙ እብሪትና ማናለብኝነት አጉልቶ የሚያሳይ ተግባር ነው።
አርበኞች ግንቦት 7:የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ ይህን ፍርደገምድል ውሳኔ አጥብቆ ያወግዛል።ይህ ፍርደገምድል ውሳኔ የተሰጠው ፕሬዚዳንት ኦባማ በአገራችን መዲና ተገኝተው “ለሰላም ሲባል ነፃነትን ማፈን ሁለቱንም ያሳጣል” ባሉ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ መሆኑ አገዛዙ የሚሰማ ጆሮ የሌለው መሆኑ የሚያረጋግጥ ሆኗል።
የሙስሊም መሪዎች በእስር ላይ በነበሩት ጊዜ በምርመራ ስም ተደብድበዋል፤ ክብራቸው ተደፍሯል፤ የተለያዩ ዘግናኝ ሰቆቃዎች ተፈጽሞባቸዋል፤ የሀሰት ዶክመንታሪ ፊልሞች እንዲሰራጩ ተደርገው ስማቸውን ለማጥፋት ሙከራ ተደርጓል።
በሙስሊም ወገኖቻችን ላይ የደረሰው በደል ሃይማኖት ሳይለይ በሁሉም ኢትዮጵያዊያን ላይ የደረሰ በደል ነው፤ መፍትሄ የምናገኘውም በጋራ በምናደርገው ትግል ህወሓትን አስወግደን በምትኩ ፍትህ፣ ነፃነት፣ ዲሞክራሲና የአገር አንድነት የሚጠብቅ የመንግሥት ሥርዓት ስናቆም ነው። ከዚህ በመለስ የሚገኝ መፍትሄ የለም። የእምነት መብቶች የሚከበሩት ሰብዓዊ መብቶች ሁሉ ሲከበሩ እንደሆኑ “በድምፃችን ይሰማ” ሥር የተሰባሰቡ ወገኖቻችን ይረዳሉ ብለን እናምናለን።
አርበኞች ግንቦት 7 ሙስሊም ወገኖቻችን ለዓመታት ያለመታከት ያካሄዱትን ትግል ያደንቃል። ከእንግዲህ ደግሞ እጅ ለእጅ ተያይዘን፤ ተደጋግፈን በመታገል ህወሓትን አስወግደን በምትኩ ለሁላችንም የምትመች አገር እንድንገነባ ጥሪ ያደርጋል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!
አርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ

Sunday 2 August 2015

How the “War on Terror” Stole Democracy in Ethiopia

August 1, 2015

How the “War on Terror” Stole Democracy in Ethiopia: Dispelling the myth of the US claim as a “guardian of liberty and freedom” in the world

by Alem Mamo
“It would be unjust and deplorable for foreign powers to intervene and frustrate the Salvadorian people, to repress them and keep them from deciding autonomously the economic and political course that our nation should follow.”
—Archbishop Oscar Romero, 1980
“The greatest weapon in the hands of an oppressor is never his guns and armies, but the mind of the oppressed.”
—Steven Biko
“It is counterproductive to hold Ethiopia up as a model of good governance when the current government has created one of the most oppressive regimes in Africa and has largely shut down civil society and the independent media. It is questionable, however, whether progress on economic indicators can be sustained as long as a repressive one-party government, largely representing a minority group, continues to exercise power by force” —The Irish Times
Once upon a time, not too far in the distant past, countering the expansion and influence of the USSR was the most important driving force of US foreign policy. It is in this context that the Cold War “friendly state” list included the most brutal and corrupt authoritarian regimes who committed heinous acts of genocide, mass murder, and crimes
Ethiopia's “War on Terror” Stole Democracy
 against humanity. The list of such brutal regimes include Suharto of Indonesia, Mobutu Se Se Seko of Zaire (now the Democratic Republic of Congo), General Augusto Pinochet of Chile, and during the Vietnam War, the US administration supported and collaborated with Vice-President General Nguyen Cao Ky of South Vietnam, who idolized Adolf Hitler as his hero. Even, the most degrading and appalling white supremacist regime in Apartheid South Africa was an ally of the West, while Nelson Mandela, the giant of human dignity, freedom, and justice, was marked as a “terrorist.” These are just a few; the list is long and full of despots with abhorrent human rights records and bloody legacies.

In South and Central America, paramilitary death squads, mostly trained and supported by the US government, roamed the streets, villages, and towns terrorizing, raping, killing, and maiming innocent civilians. Millions have fallen victim around the world in the raging blaze of the Cold War. In Africa, Asia, South, and Central America, countless mass graves hold the open secrets and bleeding wounds of many nations. In El Salvador, for instance, the pain and suffering of the Salvadorian people was remembered recently at a ceremony of the beatification of the man they called “the voice of the voiceless,” Archbishop Oscar Romero, an ordinary man with an extraordinary dedication and unwavering service to the poor, the marginalized, and neglected.
On February 17, 1980, Archbishop Romero wrote a letter to President Jimmy Carter lamenting the US government’s collaboration with the military junta in El Salvador and its impact on the Salvadorian people: “I am very concerned by the news that the government of the United States is planning to further El Salvador’s arms race by sending military equipment and advisors to ‘train three Salvadoran battalions in logistics, communications and intelligence.’ If this information from the papers is correct, instead of favoring greater justice and peace in El Salvador, your government’s contribution will undoubtedly sharpen the injustice and the repression inflicted on the organized people, whose struggle has often been for respect for their most basic human rights.”
President Carter never responded to Archbishop Romero’s letter. A week later, on March 24, 1980, the humble servant of the people, Monseñor Archbishop Oscar Romero, was assassinated while he was celebrating mass. His dedication to the poor and marginalized was so pure and creative that the Archbishop began to read the names of those who were snatched from their homes by paramilitary forces: the desaparecido – the disappeared, as they became to be known. Such a simple act of weekly reading of the names on the radio reached into every household in El Salvador infuriating the military junta. His legacy and commitment continues to inspire many around the world.
While most countries are still trying to recover from the Cold War trauma, the so called “War on Terror” has emerged as the sequel of this tragic chapter in human history. The US and the West once again have forged an alliance with murderous regimes who do not flinch for a second from terrorizing and murdering their own people. Regimes, who do not have an ounce of legitimacy from the people they proclaim to rule, have been endorsed and applauded by the West for their “outstanding contribution in the fight against terror.” Such utter neglect and cruel brutality endorsed and oiled by the West is nowhere more evident than in Ethiopia. For the last twenty four years, the people of Ethiopia endured the most horrendous and indiscriminate form of brutality.
As many international human rights organizations reported torture, extrajudicial killings, and disappearances under the Tigray People’s Liberation Front (TPLF) ethno-kleptocratic regime are daily occurrences. Civil society and independent media outlets are effectively shut down. Journalists are risking their lives to tell the truth. Elections are held under tight control of the ruling elite where opposition leaders and members are arrested and intimidated. For example, in the most recent election, the regime declared itself 100% “winner” effectively becoming the first in Africa to win 100% of the seats. It is worth noting that the well-established percentage of victory in Africa is often between 94- 99%; the TPLF regime’s 100% election “victory” is unfamiliar to most authoritarian regimes on the continent. And yet, the US and the West continue to call such a regime “democratically elected” ignoring the cries of the people. President Obama’s lavish praise for such brutal regime has left many bewildered and shocked.
Thwarting democracy in the name of fighting terror is not only wrong and misguided, it could have multiple negative implications in the long run. First, it actually submits to the objectives of terror groups, such as Al-Shabab, who are committed to disrupting and blocking the establishment of secular, free, and democratic systems in the region. In this regard, they have effectively stifled the democratic aspirations of the Ethiopian people. Second, US and Western policy of collaborating with the TPLF ethno-kleptocratic regime is already radicalizing different groups in Ethiopia forcing them to give-up on peaceful and non-violent struggle and opt for other forms of resistance. As humiliation, lack of economic and social mobility, and political exclusion escalates, citizens will risk their lives to reclaim their dignity and humanity. This inevitable path, presents dangerous and horrifying scenario with regional and continent wise ramifications.
The twentieth century, in terms of human warfare, was the bloodiest and the most violent century in history. In what Jose Marti called the “hour of the furnaces,” Oscar Romero, Mahatma Gandhi, Nelson Mandela, Desmond Tutu, Martin Luther King Jr., and many others accompanied those who were in the sights of the men with guns. In their unwavering commitment, they made the journey full of hope with anticipation of better future. They made the journey and the struggle stronger as they burned brighter. Who would be the ones who will follow in the path of these giants of the 20th century and shine a light on what already appears to be a violent and tumultuous century. Once again, the call has gone out for a leadership not only to lead, but also to listen to the pain and anguish of those excluded in the current global political and economic order. Those who say “this is not about me” will emerge as true leaders. Those who proclaim the role of “après moi, le deluge” will take citizens into the edge of the abyss – a new century old fight for freedom, justice and democracy.
So, how many more innocent civilians have to die? How many more journalists have to endure imprisonment and torture? How many peaceful pro-democracy activists have to be killed in broad day light? How many children must grow up without parents? How many more mass graves have to be discovered? How many more mothers have to bury their children killed by TPLF security forces? How much blood? How many more lives must we lose before the world wakes up and says enough!
Alem6711@gmail.com