Tuesday 22 September 2015

የተናገሩት ከሚጠፋ… (በኤፍሬም ማዴቦ – ከአርበኞች መንደር)


September 22, 2015



ባለፈዉ መጣጥፌ “ቃል የእምነት ዕዳ ነዉ” ብዬ ጀምሬ “ቃላችን አይለወጥ” ብዬ ነበር የተለየኋችሁ። አለምክንያት አልነበረም እንዲህ ያልኳችሁ፤ በአንድ በኩለ ቃል መከበርም መከፈልም ያለበት ዕዳ ስለሆነ በሌላ በኩል ደግሞ ቀትር ላይ የገባዉን ቃል ሳይመሽ እንደ ጴጥሮስ ሦስቴ የሚክድ ብዙ ቃላ አባይ ሰላለ ነዉ። አገሬን ከወያኔ አጸዳለሁ ብሎ ቃል የሚገባ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ዕዳ አለበት። ዕዳዉ ደግሞ ገንዘብ ወይም ንብረት አይደለም። ቃሉን መጠበቅ ወይም ቃሉን ማክበር ነዉ።


Ephrem Madebo with Patriotic Ginbot 7 fighters

ደግሞም አንድ ሰዉ የተናገርዉን ቃል ሰብሮ የእምነት ባለዕዳ ከሚሆን ዕድሜ ልኩን የገንዘብ ባለዕዳ ቢሆን ይሻለዋል። የገንዘብ ዕዳ ቆይቶም ቢሆን ይከፈላል ወይም አበዳሪዉ ሊምረን ይችላል፤ የዕምነት ዕዳ ግን የማይሽር ጠባሳዉ እየቆረቆረን አብሮን ይኖራል እንጂ አይጠፋም። ማንም ሰዉ ለአገሬ ህይወቴን እሰጣለሁ ብሎ ቃል ሲገባ መሃላዉ ከህዝብና ከአገር ጋር ብቻ አይደለም፤ እንዳዉም የሰዉ ልጅ ቃል የሚገባዉ መጀመሪያ ከራሱ ጋር ነዉ። ለራሱ የገባዉን ቃል የማያከብርና ቃሌ ቃል ነዉ ብሎ የገዛ ራሱን የእምነት ዕዳ ያልከፈለ ሰዉ ለህዝብና ለአገር ቃል መግባት አይችልም። ዛሬ ወያኔን እናጥፋ ብሎ ካራ ጨብጦ አብሮኝ የቆመ ሰዉ ነገ ከወያኔ ጋር ሆኖ ካራዉን እኔዉ ላይ አዙሮ ባየዉ እሱ ቀድሞዉንም ካራ የጨበጠዉ ወያኔን ለማጥፋት ሳይሆን ስጋ ሊቆርጥብት ነዉና ብዙ አይገርመኝም። እንዲህ አይነቱን ለቁም ነገር ሲፈልጉት አልሰማ ብሎ ሆዱ ሲሞላለት ግን ሳይጠሩት አቤት የሚል ስጋ ወዳድ ሆዳም ደግሞ ኢትዮጵያ በየዘመኑ አፍርታለችና ብዙ ሊገርመን አይገባም። ከሰሞኑ ከምድረ ኤርትራ የነፈሰዉ ነፋስ ያስተማረን አንድ ትልቅ ቁም ነገር ቢኖር እንዲህ አይነቱን ሞላ ጎደለ የሚባል የካራና የስጋ ጨዋታ ነዉ። አዎ! የካራ ጨወታ – ወዲህ ማዶ ስጋ ሊቆርጡበት ወዲያ ማዶም ስጋ ሊቆርጡበት።

“የተናገሩት ከሚጠፋ የወለዱት ይጥፋ” . . . ገዢዎቻችን በተለይ የዛሬዎቹ ቃል አባዮች እንደቆሻሻ ዕቃ መሬት ላይ ጣሉት እንጂ ቃል የዕምነት ዕዳ መሆኑን ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ዘመን አይሽሬ የአገራችን አባባል ነዉ። አባቶቻችን የተናገሩትን ወይም ቃል ገብተዉ የተማማሉትን ነገር ከሚያጥፉ የወለዱትን ማጣት ይቀላቸዋል። እኛ ልጆቻቸዉ ግን ከዬት የመጣን ጉዶች አንደሆንን አላዉቅም ቃል አባይነታችን እኛን፤ ልጆቻቸንና አገራችንን ሲያጠፋ በአይናችን እያየን ቅር እንኳን አይለንም። “እመጣለሁ ብሎ ሰዉ እንዴት ይዋሻል፤ ማበል እንኳን አንቺን ምድር ያበላሻል” መሬት ላይ ጠብ የማይል ትክክለኛ አባባል ነዉ። አገራችን ኢትዮጵያ ትናንት እንሞትልሻለን ብለዉ ዛሬ በሚገድሏት ቃል አባይ ልጆቿ እየተበላሸች ነዉ። እነዚህ ቃልአባዮች የኢትዮጵያን የምድር ላይና የምድር ዉስጥ ኋብቷን አንጂ የገረጣዉን ፊቷን ማየት አይፈልጉም- አዎ ወያኔ የሚያየዉ ኃብትሽን፤ የሳዑዲዉ ሰዉ ወርቅሽን፤ ባዕድ ከበርቴዉ ለምለም መሬትሽን . . . ወይኔ ኢትዮጵያ ማን ይሆን የሚያየዉ የጠቆረዉ ፊትሽን፤ ማን ይሆን የሚያብሰዉ እምባሽን፤ እኮ ማን ይሆን የሚያቆመዉ መከራሺን . . . ማን ይሆን?. . . ማን ይሆን?

የዛሬዋ ኢትዮጵያ አንድ ትዉልድ ዉሸት ብቻ እየሰማ ያደገባት የዉሸት መዲና ሆናለች። ጳጳሱ፤ ቄሱና ፓስተሩ “እኔ መንገድ፤ አዉነትና ህይወትና ነኝ” ያለዉን የሰማዩን አምላካቸዉን ረስተዉ ለምድር ዉሸታሞች አደሩ። ሂዱና ዋሹ ሲባሉ ሄደዉ ዋሹ፤ እዉነትን በዉሸት አስተባብሉ ሲባሉ አስተባበሉ፤ በሀሰት መስክሩ ሲባሉ አፋቸዉን ሞልተዉ በሀሰት መሰከሩ። “ታላቁ መሪ” እየዋሸን ኖሮ እየዋሸን ሞተ። መታወቂያዉ ዉሸት ነዉና ሞቶም አልሞተም ተብሎ ተዋሸለት። ከአህያ ጋር የዋለች ጊደር ምን ለምዳ ትመጣለች እንዲሉ ሌላ ሁሉ ቢቀር ዉሸትን ይፀየፋል ተብሎ የተነገረለት የዛሬዉ ጠ/ሚኒስቴር ጭራሽ “ታላቁን መሪ” እንደዋቢ እየጠቀሰ ስራዉ ሁሉ ዉሸት፤ ዉሸት፤ ዉሸት ብቻ ሆኖ ቀረ። የኢትዮጵያ ሬድዮ ሲከፈት ዉሸት ይናገራል፤ ሲዘጋ ደግሞ ነገ ስለሚዋሸዉ ዉሸት ያስባል። ጋዜጦች በስህተት አንኳን እዉነት አይጻፍባቸዉም። የኢቲቪ ዜና አንባቢ ተመስገን በየነ ግማሽ ሰዐት የዋሸዉን ዉሸት ለማካካስ ዜናዉን አንብቦ ሲጨርስ ለ15 ደቂቃ ጎንበስ ብሎ ይሰግዳል።

ለረጂም ግዜ ተማምነን ጀርባችንን የሰጠነዉ ሰዉ ለጠላት እጁን ሰጥቶ ጦርነት ሲያዉጅብን አንዳንዴ በትግሉ ዉስጥ ማንን አምነን ጀርባችንን እንደምንሰጠዉ ግራ ሊገባን ይችላል። ከሰሞኑ የሰማነዉ ዜና እንዲህ ግራ የሚያጋባ ዜና ነዉ። ሆኖም ሳንተማመን ትግል ብሎ ነገር የለምና የትግል ጓዶቻችንን ማመን ብርታት እንጂ ደካሞች እንደሚሉት ሞኝነት ወይም የዋህነት አይደለም። በጓዶቻችን ላይ ክህደት ፈጽመን ከምናሰቃያቸዉ እኛ ብንሰቃይ ይሻላል፤ ደግሞም ጓዶቻችንን ማመን አቅቶን በጥርጣሬ ተፋጥጠን ባለንበት ከምንረግጥ አንዳንዴ አዉቀንም ቢሆን ብንታለል ብዙ መንገድ መጓዝ እንችላለን። ትግል በተለይ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ትግል ከሚያስተምረን ትምህርቶች ዉስጥ አንዱና ዋነኛዉ ሌሎች በኛ ላይ እምነት እንዲኖራቸዉ ከፈለግን እኛ አስቀድመን ልናምናቸዉ አንደሚገባን ነዉ። አለዚያ ሁለታችንም አንተማመንም። አለመተማመን ደግሞ ያጠፋፋናል እንጂ አንድ ቤት ዉስጥ አብሮ አያኖረንም። እንደኔ እንደኔ የወያኔን ስርዐት ደምስሰን ኢትዮጵያን የእኩሎች አገር የምናደርጋት እያንዳንዳችን ለትግል ጓዶቻችን የገባነዉን ቃል ሰብረን ረጂም ህይወት ከመኖር ቃላችንን አክብረን ዛሬዉኑ መሞትን ስንመርጥ ብቻ ነዉ። ወያኔ አንደ እሳት የሚፈራዉና በፍጹም የማያሸንፈዉ አንዲህ አይነቱን ከብረት የጠነከረ ጽኑ አቋማችንን ብቻ ነዉ። ለዚህ ነዉ እንዲህ አይነት ጽናት የሌላቸዉን ደካማ ግለሰቦች ፈልጎ እያማለለ ጽናታችንን የሚፈታተነዉ። ከሰሞኑ ለህዝብ ከመታገል ህዝብን መታገል መርጦ ከለየላቸዉ የህዝብ ጠላቶች ጋር የተቀላቀለዉ ሞላ አስገዶም ለዚህ ዉሳኔ የበቃዉ ህዝባዊዉ ትግል የሚፈልገዉ የአለማ ጽናት የሌለዉ ደካማ ግለሰብ ስለሆነ ብቻ ነዉ። ዉድ ኢትዮጵያዉያን ክህደት ትናንት ነበር፤ ዛሬ አለ፤ ነገም ይኖራል። ስለዚህ ክህደት ሊያስተምረን እንጂ በፍጹም ሊያስበረግገንና አንገታችንን ሊያሰደፋን አይገባም። ክህደትና ከሀዲዎችን እያሰላሰልን የምንኖር ከሆነ የበለጠ እንዲጎዱን ተጨማሪ ዕድል እንሰጣቸዋለን እንጂ ሌላ ምንም የምንፈይደዉ ፋይዳ የለም።

ሞላ አስገዶም እሱን የመሰሉ ደካማ ጓደኞቹን ከተቀላቀለ በኋላ መቀሌ፤ አዲስ አበባና አዳማ ዉስጥ ክህደቱን አስመልክቶ እርስ በርሳቸዉ የሚጣረሱ ሦስት ጋዜጣዊ መግለጫዎችን ሰጥቷል። እርግጠኛ ነኝ ይህ ቁርስ ላይ የተናገረዉን ምሳ ላይ የማያስታዉስ ግለሰብ በተያዘለት የጉብኝት ሰሌዳ መሠረት ዘጠኙን ክልሎች የሚዞር ከሆነ ዘጠኝ የተለያዩና እርስ በርሳቸዉ የሚጣረሱ ምክንያቶችን መደርደሩ አይቀርም። የወያኔ የመረጃና የደህንነት መ/ቤት ተብዬዉም ቢሆን ምን ያህል የዉሸትና የጉራ ቤት ለመሆኑ መረጃ ብሎ የለቀቃቸዉን ዉሸቶችና ቱልቱላዎች መጥቀሱ ይበቃል። ለምሳሌ የመረጃና ስለላ ድርጅቱ ከአንድ አመት በላይ ከሞላ አስገዶም ጋር በሚስጢር ይሰራ እንደነበር ተናግሯል። ይህ እዉነት ከሆነ የደምህት ታጋዮች በዚህ አንድ አመት ግዜ ዉስጥ በወያኔ ታጣቂዎችና ወታደራዊ ጣቢያዎች ላይ ለወሰዷቸዉ እርምጃዎች በተለይ እግር ኳስ ጨዋታ በመከታተል ላይ እንዳሉ ለወሬ ነጋሪ ሳይቀር እንዳለ ለተደመሰሱት የኢትዮጵያ ወታደሮች ተጠያቂዉ ከሞላ አስገዶም ጋር ይሰራ የነበረዉ የወያኔ የመረጃና የስለላ ድርጅት ነዉ ማለት ነዉ።

ሞላ አስገዶም ትናንት ከኛ ጋር ሆኖ እኛ ሲል ነበር፤ ዛሬ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጠለቶች ጋር ሆኖ እኛ ይላል። ይህ ሰዉ “እኛ” ሲል የሱ እኛ እነማንን እንደሚያጠቃልል አይታወቅም፤ እሱ እራሱም የሚያዉቀዉ አይመስለኝም። ሞላ አስገዶም ወያኔን እንደተቀላቀለ አፉን ሞልቶ ጥምረቱን የፈጠርነዉ “እኛ” ነን ብሎ ሲናገር በተደጋጋሚ ተደምጧል። ጥምረቱ የኢትዮጵያ ህዝብ ፍላጎትና ህዝባዊ ትግሉ የደረሰበት የዕድገት ደረጃ ዉጤት ነዉ እንጂ ሞላ አስገዶም ስለፈለገዉ የሚፈጠር አለዚያ የሚቀር የሞላ አስገዶም የቤት ዉስጥ ዕቃ አይደለም። ደግሞም እንደ ሞላ አስገዶም ፍላጎት ቢሆን ኖሮ የደምህት ጥምረቱ ዉስጥ መግባት ለግዜዉም ቢሆን ሊዘገይ ይችል ነበር። ደምህት ጥምረቱ ዉስጥ ገብቶ አገር አድን የጋራ ንቅናቄዉ የተፈጠረዉ የደምህት ሠራዊትና ከሞላ አስገዶም ዉጭ ሁሉም የደምህት ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ከሌሎች ኢትዮጳያዉያን ወገኖቻቸዉ ጋር ሆነዉ በጋራ ለመታገል በመወሰናቸዉ ነዉ። የሞላ አስገዶም ፈርጥጦ ወያኔ ጉያ ዉስጥ የመሸጎጡ ዋነኛዉ ምክንያትም የዚህ ዉሳኔ ዉጤት ነዉ እንጂ የወያኔ መረጃና ስለላ ድርጀት ሚስጥራዊ ግንኙነት ዉጤት አይደለም። ሌላዉ እርስ በርሱ የሚጋጭ የወያኔ ዉሸት – በአንድ በኩል ሞላ አስገዶምና የደምህት ሠራዊት ሙሉ ትጥቃቸዉን እንደታጠቁ ጠቅልለዉ ወደ አገራቸዉ ተመለሱ የሚለዉ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ቁጥሩ ወደ 700 የሚጠጋ የደምህት ሠራዊት ወደ አገሩ ተመለሰ የሚለዉ የተምታታ ዘገባ ነዉ። እዚህ ላይ የደምህትን ሠራዊት ብዛት መናገሩ አስፈላጊ ባይሆንም ግንዛቤ ማግኘት የፈለገ ሰዉ ግን ተመድ ያወጣቸዉን ሪፖርቶች መመልከቱ የሚበቃ ይመስለኛል። ደግሞም ሞላ አስገዶም አታልሎ መንገድ ካስጀመረዉ ሠራዊት ዉስጥ ገሚሱ ወደ ትግሉ ሜዳ ተመልሷል፤ የተቀረዉ ደግሞ ወደ ትግሉ ሜዳ ካልተመለስኩ እያለ ከሱዳን ባልስልጣኖች ጋር እየተደራደረ ነዉ። በነገራችን ላይ የዚህ ጽሁፍ ጸሀፊ ሞላ አስገዶም አታልሎ ሀምዳይት ከወሰዳቸዉ በኋላ ትግል ወይም ሞት ብለዉ ተመልሰዉ ከትግል ጓዶቻቸዉ ጋር ከተቀላቀሉ ጀግኖች ኢትዮጵያዉያን ጋር አብሮ ቡና ጠጥቷል።

ጓዜን ጠቅልዬ ትግሎ ሜዳ ከመግባቴ በፊትም ሆነ ከገባሁ በኋላ የደምህት ስም በተነሳ ቁጥር አብረዉ የሚነሱ ሁለት መላምቶች አሉ። አንደኛዉ መላምት ደምህት የኤርትራ መንግስት ሆን ብሎ የፈጠረዉና ጭራሽ ኤርትራ ዉስጥ የመንግስት የጸጥታ ሀይሎችን ተክቶ በመንግስታዊ ተቋሞች ጥበቃና ደህንነት ስራዎች ላይ የተሰማራ ድርጅት ነዉ የሚል መላምት ሲሆን ሁለተኛዉ መላምት ደግሞ ሞላ አስገዶም በኤርትራ መንግስት ድጋፍ ሁለተኛዉ መለስ ዜናዊ ሆኖ ህወሃትን ተክቶ አትዮጵያን ይመራል የሚለዉ መላምት ነዉ። ደግነቱ የነዚህ መላምቶች የማዕዝን ራስ የሆነዉ ሞላ አስገዶም ኮብልሎ ወያኔን መቀላቀሉና ከተቀላቀለ በኋላ የሰጣቸዉ ጋዜጣዊ መግለጫዎች ሁለቱንም መላምቶች እንዳልነበሩ አድርጓቸዋል። እኔን አልገባ ያለኝና በጣም የሚገርመኝ ግን በአንድ በኩል የኤርትራ መንግስት የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ድርጅቶች ትብብር እንዲፈጥሩ አይፈልግም ይባላል፤ በሌላ በኩል ደግሞ ጥምረቱ የተፈጠረዉ በሻዕቢያ ግፊት ነዉ ይባላል። መቼም ገና በልጅነቴ ካልጃጀሁ በቀር ሻዕቢያና የኤርትራ መንግስት መሃል ልዩነት ያለ አይመስለኝም። ሌላዉ የሰሞኑ አስቂኝ ድራማ ደግሞ ሞላ አስገዶም ጥምረቱን የፈጠርነዉ እኛ ነን ሲል የሱን መኮብለል አስመልክቶ የሚሰጠዉ አስተያያት ደግሞ ሞላ አስገዶም ጨርቁን ጠቅልሎ ወያኔን የተቀላቀለዉ ብርሀኑ ነጋ በኤርትራ መንግስት ግፊት የጥምረቱ ሊ/መንበር መሆኑ አልዋጥ ብሎት ነዉ ይባላል።

ሌላዉ አሁን በቅርቡ ወይም ከሞላ አስገዶም መኮብለል በኋላ የተጠነሰሰዉ መላምት ደግሞ ደምህቶች እራሳቸዉ ኤርትራ ዉስጥ የሚገኙ ተቃዋሚ ድርጅቶች በወያኔ ስርዐት ላይ ወታደራዊ እርምጃ መዉሰድ እንዳይችሉ ሆን ተብለዉ በወያኔ የተፈጠሩ እንቅፋቶች ናቸዉ የሚለዉ መላምት ነዉ። በኔ ግምት ይህኛዉ መላምት ከሁሉም መላምቶች የከፋና እጅግ በጣም አደገኛ የሆነ ጽንፈኛ መላምት ነዉ። እንደዚህ መላምት ፈጣሪዎች አባባል የትግራይ ህዝብ በህወሃት አመራር በደል አይደርስበትም ወይም የትግራይ ህዝብ ከሌሎች ኢትዮጵያዉያን ወንድሞቹና እህቶቹ ጋር ሆኖ የህወሃትን ግፈኛ ስርዐት አይታገልም ማለት ነዉ። እንዲህ አይነቱ ጭፍንነትና ጠባብነት የሚመነጨዉ ደግሞ ሞላ አስገዶምንና ደምህትን ወይም ህወሃትንና የትግራይን ህዝብ ለያይቶ ማየት ካለመቻል አባዜ ነዉ። በደርግ ስርዐት ዉስጥ ጭቆናዉና በደሉ በዛብኝ ብሎ ጠመንጃ ያነሳዉ ጀግናዉ የትግራይ ህዝብ ህወሃት ከሌሎች ኢትዮጵያዉያን ወገኖቹ ተነጥሎ እንዲታይ ለማድርግ የሚሸርብበትን ሤራና የሚያደርስበትን ግፍና መከራ አፉን ዘግቶ የሚቀበልበት ምንም ምክንያት የለም። ስለዚህ ደምህት የትግራይ ህዝብ ብሶትና ምሬት አምጦ የወለደዉ ፀረ ህወሃት ንቅናቄ ነዉ እንጂ ወያኔ የፈጠረዉ ድርጅት አይደለም፤ሊሆንም አይችልም። ሞላ አስገዶምም ቢሆን የራሱ የተጠረቃቀመ ድክመት ከንቅናቄዉ ሊ/መንበርነቱ እንደሚያስነሳዉ ሲያዉቅ የፈረጠጠ ፈርጣጭ እንጂ እሱና ወያኔ እንደሚሉት የአንድ አመት ቀርቶ የአንድ ወርም ተከታታይ ግንኙነት አልነበራቸዉም።

ወደ ኢትዮጵያ ፖለቲካ መድረከ ብቅ ብለዉ የጠፉትንም ሆነ ዛሬም ድረስ ያሉትን የፖለቲካ ድርጅቶች ባህልና ድርጅታዊ አሰራር ስንመለከት የድርጅቶች ህልዉና መመዘኛና የማንነታቸዉ መለኪያ ቆምንለት የሚሉት አላማ ሳይሆን የመሪዎቻቸዉ በተለይ የዋናዉ መሪ ተክለሰዉነት ነበር። የድርጅት ወይም የፓርቲ ሊ/መንበር ከድርጅቱ ባለይ ነዉ፤ እሱ ይሁን ያለዉ ይሆናል፤አይሁን ያለዉ አይሆንም። ብዙ ግዜ የድርጅት/ፓርቲ ሊ/መንበር ድርጅቱን የማፍረስ አቅም ጭምር አለዉ። ይህንን ደግሞ በቅርብ ግዜ ታሪካችን በተደጋጋሚ አይተናል። አንድን ድርጅት ወይም ፓርቲ አባላት ሲቀላቀሉ የሚመለከቱት የፓርቲዉን ሊ/መንበር እንጂ የፓርቲዉን የፖለቲካና የኤኮኖሚ ፕሮግራም አይደለም። የፓርቲ ሊ/መንበርም ቢሆን የኔ የሚላቸዉን ሰዎች ነበር እየመረጠ የሚያሰባስበዉ። እንደዚህ አይነቱ የፓርቲ አደረጃጀትና አሰራር አሁን እየተቀየረ የመጣ ቢሆንም ለረጂም ግዜ የፖለቲካ ትግላችን ችግር ሆኖ ቆይቷል። ሞላ አስገዶም በቅርቡ የደምህትን ሠራዊት ከነሙሉ ትጥቁ ይዤ ኢትዮጵያ ገባሁ ብሎ በድፍረት የተናገረዉ ንግግር ይሄዉ የድርጅት ሊ/መንበር ያሰኘዉን ሁሉ ማድረግ ይችላል የሚለዉ የቆየ የፖለቲካ ባህላችን በሽታ ተጠናዉቶት ነዉ። “ዝንጀሮዉን ከጫካ ያዉጡታል እንጂ ጫካዉን ከዝንጀሮዉ ዉስጥ አያወጡትም” የሚል ብህል አለ፤ ትክክለኛ ብህል ነዉ። ሞላ አስገዶም ህወሃት/ወያኔ የኢትዮጵን ህዝብ በአጥር እየለያየ በትናናንሽ ጎጆዎች ዉስጥ ማኖሩ አልዋጥ ብሎት ሁሉንም የሚያቅፍ ሰፊ ቤት ሰርተን ኢትዮጵያን የዲሞክራሲ አገር እናደርጋለን ብሎ ለብዙ አመታት የታገለ ሰዉ ነዉ። ችግሩ ሞላ አስገዶም ነዉ ከነዚያ ትናንሽ የወያኔ ጎጆዎች የወጣዉ እንጂ ትናንሽ ጎጆዎቹ ከሞላ አስገዶም ዉስጥ ስላልወጡ እንደ ማግኔት እየሳቡት ወደነበረበት ቦታ መልሰዉታል። ለሁሉም የሞላ አስገዶም ታሪክ ሲጻፍ – መጣና ሄደ ከሚሉ አምስት ሆሄያት የዘለለ ምንም ቁም ነገር የለዉም። እየመጡ መሄድና እየሄዱ መምጣት ደግሞ ትናንሽ ቤት የሚናፍቃቸዉ ትናንሽ ሰዎች እስካሉ ድረስ ይቀጥላል።

ሁለት ሺ ሰባት ሊጠናቀቅ ሦስት ቀን ሲቀረዉ አንድ የብዙ ኢትዮጵያዉያንን ጆሮ የሳበ ዜና ቴሌቪዥኑን፤ ሬድዮኑን፤ ጋዜጣዉንና ድረገጹን ተቆጣጠረዉ። ዜናዉ የወያኔ/ህወሃትን ስርዐት በመሳሪያ ኃይል የሚታገሉ አራት ድርጅቶች አገር አድን የጋራ ንቅናቄ ፈጠሩ የሚል የአዲስ አመት የምስራች ነበር። የኢትዮጵያ ህዝብ ለረጂም ዘመን የናፈቀዉ የምስራች ነበር። ግን ምን ያደርጋል – በጥባጭ እያለ ንጹህ ዉኃ አይጠጣምና ይሀንን የአዲስ አመት የምስራች ሰምተን ሳናጣጥም ነበር የሞላ አስገዶምን ዜና ክህደት የሰማነዉ። አስደንጋጭ ዜና ነበር። በእርግጥም የአራት ድርጅቶች ጥምረት ተፈጠረ የሚል ዜና በተሰማ ማግስት የጥምረቱ ምክትል ሊ/መንበር ሠራዊት እየመራ ሄዶ ወያኔን ተቀላቀለ የሚል ዜና መስማት የሚያስደነግጥና በመጀመሪያዉ ዜና ላይ ቀዝቃዛ ዉኃ የቸለሰ ልብ ሰባሪ ዜና ነዉ። ደግነቱ ሁሉም ነገር ለበጎ ነዉ። የሞላ አስገዶም መክዳት ተራ ዜና ነዉ ማለቴ አይደለም። ግን ሞላ አስገዶምና የወያኔ መረጃ ድርጅት በትብብር ሠራነዉ ያሉት አዲስ ድራማ ተዉኔቱ ሳይጻፍ አየር በአየር የተከወነ ምናቡ ያልተባ ድራማ በመሆኑ ድራማዉ ከያኒዉን ሳይሆን የኢትዮጵያን ህዝብና ለአንድነቱና ለነጻነቱ የሚታገሉ ልጆቹን በከፍተኛ ደረጃ የጠቀመ መሆኑን ማሳዉቁ አስፈላጊ ይመስለኛል።

ደምህት በዚህ የወያኔ ድራማ ዉስጥ በእሳት ተፈትኖ ወርቅነቱን አረጋግጧል። ሞላ አስገዶም የደምህትን ሠራዊት ለወያኔ አስረከብኩ ብሎ በተናገረ ማግስት የደምህት መሪዎች የሰጡት አርቆ አስተዋይነት የታየበት አመራርና ያሳዩት ቆራጥነት የፖለቲካ ድርጅቶቻችን የደረሱበትን የዕድገት ደረጃ በግልጽ አሳይቷል። ደምህት እራሱም እንደ አንድ የትግል ድርጅት የተደቀነበትን አደጋና ፈተና በጣጥሶ በመዉጣት በትናንሾችና በደካሞች ሴራ በፍጹም የማይናጋ ጠንካራ ድርጅት መሆኑን በተግባር አሳይቷል። የዛሬዉ ደምህት ዉስጡን ከአድርባዮች ያፀዳ ሁለትና ሦስት እርምጃዎች ወደፊት የተራመደ ጠንካራ ድርጅት ነዉ። እርግጠኛ ነኝ ይህ የደምህት መሪዎች ያሳዩት አስተዋይነት፤ ጽናትና ቆራጥነት እኔ የምፈልገዉ ነገር ካልሆነ ድርጅቱን በአፍጢሙ እደፋዋለሁ ብለዉ ለሚያስቡ ዕብሪተኛ መሪዎች ጥሩ ትምህርት ነዉ። ሌላዉ የሞላ አስገዶም ክህደት በግልጽ ያሳየን ነገር ቢኖር የኢትዮጵያ ፖለቲካ መድረክ የሀዝብ መብትና ነጻነት ይከበር በሚሉ የነጻነት ሀይሎችና ህዝብን ረግጠን እንገዛለን በሚሉ ፀረ ህዘብ ሀይሎች ለሁለት መከፈሉን ነዉ። ወደድንም ጣላን ካሁን በኋላ ያለን አማራጭ ሁለት ብቻ ነዉ፤ ወይ ወያኔ ሆኖ ከህዝብ ጋራ መዋጋት ወይም ከህዘብ ጋር ሆኖ ወያኔንና ስርዐቱን መዋጋት። ሞላ አስገዶም ጎራዉን ለይቷል፤ እኛም ጎራችንን እንለይ። መኃል ቆሞ መመልከት አብቅቷል።

ጠላቴን አግዝፌ መመልከት አልወድም፤ ትንሽ ነዉ ብዬም ጠላቴን በፍጹም አልንቅም። በቅርቡ የወያኔ የመረጃና ደህንነት መ/ቤትና ሞላ አስገዶም ከአንድ አመት በላይ አብረን ሠራን ያሉትን የጀማሪዎች ስራ ስምለከት ግን ወያኔ/ህወሃት “የምትሰሩትን ብቻ ሳይሆን የምታስቡትን ጭምር የሚያይ አይን አለኝ” እያለ የኢትዮጵያን ህዝብ ከማስፈራራት ዉጭ የረቀቀ የመረጃ ስራ መስራት ቀርቶ አረፍተነገሮችን አገጣጥሞ ለጆሮ የሚጥም ንግግር ማድረግ የሚችል አዋቂ የሌለበት የባዶዎች ድርጅት መሆኑን ነዉ የተረዳሁት። ሞላ አስገዶምም በወዶገባነት ሄዶ የተቀላቀለዉ ይህንኑ አዋቂ የሌለበትን እሱን የመሰለ ድርጅት ነዉ። ይህንን ደግሞ እስከዛሬ በሰጣቸዉ ቃለመጠይቆች በግልጽ አይተናል። ህወሃት/ወያኔን እስከዛሬ በሥልጣን ላይ ያቆዩት ሁለት ነገሮች ቢኖሩ አንዱ ጠመንጃ ሁለተኛዉ የኛ የነጻነት ኃይሎች መበታተን ብቻ ነዉ።

ነገ የምንፈልጋት ኢትዮጵያ እንደ መኪና ተገጣጥማ አትጠብቀንም – የዛሬዉ ጥረታችንና ድካማችን ዉጤት ናት። ኢትዮጵያና ህዝቧ ከወያኔ ሲፀዱ የሚነፍሰዉ የነጻነት አየር ሁላችንንም ቢያስደስትም ደስታዉ የሚገለጸዉ በግለሰብ ደረጃ ነዉ። ዛሬ ከጠላት ጋር ተፋልመን የተቀማነዉን ነፃነት ማስመለስና እንደገና እንዳንቀማ ነቅቶ መጠበቅ ግን የሁላችንም የጋራ ሀላፊነት ነዉ። እንግዲህ ወገን ወገባችንን ጠበቅ የምናደርግበት ግዜ አሁን ነዉና ሁላችንም በየተሰለፍንበት መስክ እንበርታ። ጠላታችን ጠንካራ መስሎ የሚታየዉና ያለ የሌለ ጡንቻዉን የሚያሳርፍብን የማይቀረዉን ድል ማሽተት ስንጀምር ነዉ። የድል መአዛችንን የምናሸትበት ግዜ ደግሞ ሩቅ እንዳይመስለን ነገና ከነገ ወዲያ ነዉ። ከወላዋይና እዚህም እዚያም እየዘለለ ከሚያዘናጋን አጉል ጓደኛ አንዱኑ የለየለት ጠላት ይሻላልና የሞላ አስገዶም ክህደት ትግላችንን ሊያጠራዉና መንገዳችንንም ሊያሳጥረዉ ይገባል እንጂ በፍጹም ግራ ሊያጋባን አይገባም። አይዞን. . . ሞኝ ከዘመዱ ከሚያገኝዉ ጥቅም አዋቂ ከጠላቱ የሚያገኘዉ ጥቅም ይበልጣልና ጠላቶቻችን የፈጠሩልንን አጋጣሚዎች ሁሉ በሚገባ እንጠቀምባቸዉ እንጂ ለጠላት አንመቻች። ጠላታችን እየተሳሳተልን ነዉ፤ ጠላት ሲሳሳት ማቋረጥ ነዉር ነዉ። ቸር ይግጠመን!!!
አፍሬም ነኝ ከአርበኞች መንደር

Friday 11 September 2015

አዲሱ አመት 2008 ዓ᎐ም የለውጥ አመት ይሆንልን !!!

          ቀን   11 09 2015
   በአብዩ ጌታቸው
 ከስታቫንገር ኖርዌ 
  
                                                                              
      ኢትዮጵያ ለብዙ አመታት ህዝቦቿ በባህል፣ በቋንቋ ፣ እና በእምነት እና በማህበራዊ ኑሮ ተከባብረውና ተስማምተው በአንድነት የሚኖሩባት ሃገር ናት፣ ሆኖም ግን በአሁኑ ወቅት ላለፉት 25 አመታት ስልጣን ላይ ያለው ወያኔ መራሹ የኢህዲግ ስርዓት ህዝቡን በተንኮል በመከፋፈልና አንዱ በአንዱ ላይ በመጥፎ እንዲነሳበት የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም ᎓᎓ በዘር በመከፋፈል በሃሰት ታሪክ በማስተማር ፣መፅሃፍ በማተም ፣አንዱን በዳይ ሌላው ተበዳይ አድርጎ  በሃሰት በመተረክ ፣ ባእዳንና ካድሬውን ባለ መሬት ሌላውን ባለአገሩን አገር አልባ በማድረግ ማፈናቀል፣ በብሔር እኩልነት ስም ዜጎችን በዘር በመከፋፈል መለያየት መግባባትና መመካከር እንዳይኖር ማድረግ፣ በክልል ከፋፍሎ ህዝቡ በመረጠው ክልል ምርታማ እንዳይሆን ማድረግ ፣በእምነቱ ተከባብሮና ተዋዶ  በሚኖረው ህዝብ መሃል ልዩነትና ግጭቶች እንዲኖር በመፍጠር አንድነታችንን እና ጥንካሬያችንን አናግቶ ስላጣንን  በአፈሙዝ ድጋፍ በማድረግ አገዛዙን ለማራዘም ሌት ከቀን ይጥራል᎓᎓

        የሃገራችንን ዋና ችግር  የስርዓት ችግር ነው ᎓᎓ ለዜጎች የሚጨነቅ ስርዓት በማጣታችን ነው የከፋ ችግር ላይ የወደቅነው ᎓᎓  ፍትህና ተጠያቂነት፣ ግልጽነትና የህዝብ የበላይነት የሰፈነበት ስርዓት ስለሌለን ነው ᎓᎓ እንደምናየው  በኢትዮጵያ  ያሉ ፍርድ ቤቶች ለገዢው ስርዓት የፖለቲካ መገልገያ  መሳሪያ ናቸው። መከላኪያው ፣ፖሊሱ፣ ባንኩ፣ ሚዲያው ሁሉ በስልጣን  ላይ ለተቀመጠው ከማጎብደድ ተላቆ በነፃነት፣ በህግና በሙያው አምኖ ለህዝብ ኣገልግሎት መስጠት ሲችል ነው ከገባንበት ችግር የምንወጣው።

       ህዝብ የመረጠው ስርዓት በሃገራችን በኢትዮጵያ እንዳይኖር የይምሰል ምርጫ በደረሰ ቁጥር ለተቀመጥኩበት ስልጣን ያሰጉኟል በማለት ህዝብን ጨቁኖ ለመግዛት በታቀደ በ "ሽብር ህግ " የሚታሰሩ ፣የሚታፈኑት እና የሚገደሉት የፓርቲ አመራር አባሎችና ግለሰቦች፣ እንዲሁም ህይወታቸውን ለማትረፍ የሚሰደዱ ጋዘጠኞችና ፖለቲከኞች ቁጥራቸው ብዙ ነው አገራችን  በጋዘጠኟ፣ በተቋዋሚ የፖለቲካ አመራሮችና እና አባሎች  እንዲሁም በጦማሪያን ማሰር በአለም ከመጀመሪያ ተርታዎች ስር ትገኟለች᎓᎓ በተጨማሪም ነፃ መፅሄቶች በሙሉ በሀገር ውስጥ እንዳይታተሙ እና ህዝቡ ስለሃገሩ በቂ እውቀት እንዳይኖረው ታግደዋል ᎓᎓


ስርዓቱ ስልጣኑን ለማረዘሚያ በነደፈው ‘የሽብር ህግ’ መሰረት በእምነት ውስጥ ጣልቃ በመግባት ፍፁም ሰላማዊ የሆኑ የሙስሊም ኢትዮጵያን የእስልምና ሀይማኖት መሪዎች ያለአግባብ ፍርድ  ለብዙ አመታት እስር ቤት አጎሮአል እስከ ሀያ ሁለት ዓመት በሚደርስ ተገቢ ያልሆነ እስራት ፈርዶባቸዋል᎓᎓  ለብዙ አመታት  በእምነት እና በማህበራዊ ኑሮ ተከባብረውና ተስማምተው በአንድነት  የሚኖሩትን  የኢትዮጵያን ክርስቲያንና ሙስሊሙን ህብረተሰብ ለማጋጨት የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም᎓᎓

            ስርዓቱ የሃገሪቱ አንጡራ ሃብት በጥቂት ግለሰቦች ስር እንዲመዘበር እና ፣ ስልጣንን ተገን በማድረግ  በኢትዮጵያ ህዝብ ስም በእርዳታ ስም የሚገኘው ገንዘብም ከሃገር እንዲሸሽ እያደረገ ነው አድርጎአታልም ᎓᎓ ኢትዮጵያ ከአፍካ  ከናይጄሪያ ቀጥላ የሃገርን ገንዘብ በማሸሽ ሁለተኛ ሃገር ናት  ᎓᎓ ሙስናም በሃገሪቷ ላይ ተንሰራፍቶ ምስኪኑ ህዝብ የበይ ተመልካች ሆናል ᎓᎓ የኑሮ ውድነትና ድህነት  የህዝባችንን አንገት አስደፍቶአል᎓᎓

   ስርዓቱ በጋንቤላ፣በቤሻንጉል፣እና በሌሎች በደቡብ ኢትዮጵያ ለህንድ፣ ለቻይ፣ለሳውዲ እና ለስርዓቱ አጎብዳጅ ካድሬዎች በኢንቬስትመንት ስም እና በዘር ፖለቲካ ህዝቡን በማተራመስ  ነዋሪውን እና ገበሬውን ከሚኖርበት እና የዕለት   ኑሮውን ለማሸነፍ ከሚያርስበት ቦታ አፈናቅሎ ለህይወት ማጣት ፣ ለረሃብና ለአገር ውስጥ ስደት በቅተዋል ᎓᎓አሁንም ችግሩ ተባብሶ እየሄደ ነው መጨረሻው ወደማያልቅ ችግር እያመራን ነውና በቃ ማለት አለብን !

      አገዛዙ በኢንቬስተምንት ስም የሚቃጠለው ወይም የሚመነጠረው ደን የአየር ማዛባት ማስከተሉን አለማስተዋል እንዲሁም በውስጡ የሚኖሩ የአገሪቷ ብርቅዮ እንስሳቶችን ሁንታን አላማጥናት እና በካድሬነትን የሚገኘውን የግል ጥቅም ከህዝብ እና ከሃገር በላይ ማፍቀር ሃገሪቷ ወደ ከፋ ችግር ውስጥ ከቷል᎓᎓ ችግሩ ለመደባበስ ሃገራችንን ከካሊፎኒያ ጋር ማወዳደር ትልቅም ቅሌት ነው ᎓᎓

      የአገዛዙ የትምህርት አሰጣጥ ፖሊሲው የፖለቲካው ትምህርት መስጫ ከመሆኑም አልፎ ተማሪው ተገቢውን የትምህርት አሰጣጥ ወይም እውቀት አግኝቶ የተሻለ ደረጃ እንዲደርስ ካለማድረጉ በተጨማሪ ተምሮም በተማረበትና በሰለጠነበት የሙያ ዘርፍ እንዳይሰማራ የተመቻቸ መንገድ ካለመኖሩ ለከፋ ችግር ተዳርጎአል᎓᎓ ወጣቱ ስደትን ተስፋው አድርጎ እንዲኖር ተደርጎአል ᎓᎓ ተሰዶም በሚደርስበት መከራና ኢሰብዓዊ ችግር  በአፋጣኝ የሚደርስለት መንግስት የለውም ᎓᎓ በሳውዲም ፣ በሊቢያ ፣ በደቡብ አፍሪካም  አይተነዋልና᎓᎓

     አገዛዙ ታሪካዊ ቦታዎች እና ቅርሶች እንዲጠፋ ዘወትር ይሰራል ለምሳሌ ዋልድባ ገዳም መመልከት ይቻላል  የሃገራችንን እምነት ባህል በክብር ይዘው የቆዩልን አባቶችን አፈናቅለዋል ቦታውንም በልማት ስም ይፈለጋል በማለት ወስደውታል᎓᎓ ዋልድባ ገዳም ታሪካዊ ፣ጥንታዊ ፣ ቅዱስ የፀሎት እና ሰዎች ከእግዚአብሄር ጋር የሚገናኙበት ቦታ ነው ፣ቦታውን ጠብቆ ለትውልድ የማስተላለፍ አላፊነቱ የማን ነው ? 

    ክልልን ለማስፋፋት፣ በጎንደር ፣በወልቃይትና በአፋር ህዝብ ላይ የሚደርሰው ግፍ ፣ በመሬት ጥያቄ የተነሳ በአምቦ ተማሪዎች ላይ የደረሰው ግድያ ፣ በኦጋዴን ህዝብ ላይ የሚደርሰው በደል እንዲሁም አገሪቷን በመቁረስ በሰሜን ምዕራብ፣ በምዕራብና በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ከ1600 ኪሎ ሜትር በላይ እርዝመት እና ከ30-60 ኪ/ሜትር የጎን ስፋት ያለውን ውሃ-ገብ ለም መሬቷ ተቆርሶ ለሱዳን ተሰቶአል፣ የአካባቢው ነዋሪም በኢሰብዓዊ  ሁኔታ እየተገደሉ እና  በጉልበትና በዘዴም እየተፈናቀሉም ነው ᎓᎓ 
ዝምታችን ሃገራችን ምን እስክትሆን ነው ?

       የወያኔ መራሹ አገዛዝ ጥፋቱ ዘርፈ ብዙ ነው ፣ ታዲያ ይህን አምባገነን አገዛዝ አፍርሶ በምትኩ ፍትሃዊ እና ዲሞክራሲያዊ ስርዓት  ለመገንባት ብንቀሳቀስ ምን ይለናል ? የሰላማዊ ስርዓት ለውጥን  በር ለዘጋ አምባገነን ምርጫችን የግድ የሃይል  አማራጭ ነው ᎓᎓

       ሃገራችን ከችግር እንድትወጣ ከተፈለገ የአቋም ቁርጠኝነትን ይጠይቃል። እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብቱ የተከበረበት፣ የኢኮኖሚ ብልፅግናና ማኅባራዊ ፍትህ የሚያገኙበት፣ የዜጎች ህይወት፣ ደህንነትና ጥቅም የተከበረበት ሃገር እንዲኖረው የሁላችንምም ትብብር እና አስተዋፅኦ ይጠይቃል።

       እናም ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በየትኟውም ስፍራ የሚገኝ ሁሉ ለነፃነትና ለዲሞክራሲ የሚደረገውን ትግል እውቀት ያለው በእውቀቱ፤ ጉልበት  ያለው በጉልበቱ፤ ገንዘብ ያለው በገንዘቡ ለመደገፍ ዛሬ ነገ ሳንል አሁኑኑ ከአርበኝነቱ ትግል መቀላቀል ይጠበቅብናል፡፡ ኢትዮጵያዊነታችንን ብቻ ሳይሆን ሰው መሆናችን የሚረጋገጠው ነፃነታችንን አስጠብቀን በነፃነት መኖር ስንችል ብቻ መሆኑ መዘንጋት የለበትም፡፡

     ስለዚህ ዛሬ የአገርን አድን ንቅናቄ  የለኮሰውን የነፃነት እና የአንድነት ቀንዲል ከነጻነት አደባባይ ለመትከል የጀመረውን ጉዞ በሰው ሀይል፤ በገንዘብና በቁሳቁስ በማገዝ አዲሱ አመት 
2008 ዓ᎐ም የለውጥ አመት ይሆንልን ዘንድ ሁላችንም የድርሻችንን እንድንወጣ ለእኛ ኢትዮጵያውያን ከእኛ ኢትዮጵ ያውያን ውጭ ማንም እንደሌለ ከመቼውም ግዜ በበለጠ በመገንዘብ ለተግባራዊ ስራ እንተባበር ፣ እንነሳ !


መልካም አዲስ ዓመት !


ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!!



በኖርዌይ ስታቫንገር ከተማ የተሳካ ህዝባዊ ወይይት ተካሄደ!!!!

12002107_1620630081557713_6304443920125446013_n1898001_1620629378224450_355679714234094641_n11998824_1620630491557672_8308639176961483645_n11960112_1620629534891101_7552772508092671518_n

በዲምክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ  የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ስታቫንገር ቅርንጫፍ አዘጋጅነት መስከረም 5 2015  በኢትዮጵያን ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታ ላይና በሰብዓዊ መብት አያያዝ በተመለከተ ታላቅና የተሳካ ውይይት ተካሄደ::
በሕዝባዊ ስብሰባው ላይ የነፃነት ተምሳሌቱና የጀግናው አንዳርጋቸው ፅጌ ወ/ሮ ብዙሃየው ፅጌ ፣ የአበኞች ግንቦት 7 አመራር ዶ/ር ሙልዋለም አዳምና ፣ የዲምክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ  የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ሊቀመንበር አቶ ዩሀንስ አለሙ በተጋባዥ እንግድነት የተገኙ  ሲሆን
ቁጥራቸው በርካታ የሆኑ ከተለያዩ የኖርዌይ ከተማ የመጡ አገር ወዳድ ታዳሚዎች  በስብሰባው ተገኝተዋል::
በመጀመርያ የዲሞክራሲያዊ ለለውጥ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ስታቫንገር ቅርንጫፍ አቶ አብዩ ጌታቸው በኢትዮጵያ ውስጥ በወያኔ አረመናዊ ስርአት በጭካኔ በግፍ ለተገደሉ እና በተለያዩ አስር ቤቶች በፖለቲካ ኣስተሳስባችው ምክንያት ያለወንጀላችው ለታሰሩ ውድ ኢትዮጵያዊን ወገኖቻችን   የአንድ ደቂቃ የህሊና ጸሎት በማስደረግ ስብሰባውን ያስጀመሩት ሲሆን በመቀጠል የዲምክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ  የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ሊቀመንበር አቶ ዩሀንስ አለሙ ስለ ድርጅቱ እንቅስቃሴና ከዚህ ቀደም ሲደግፋቸው የነበሩት የቀድሞው ለአንድነትና ለዲሞክራሲ ፓርቲ ሰማያዊ ፓርቲ ጋር ባሁን ሰሃት የወያኔ ሥርሃት ባደረገው አፈና ምክንያት መገናኘት እንዳልተቻለና የቀረው አርበኞች ግንቦት 7 በመሆኑ ሙሉ ድጋፋቸውን እያደረጉ እንደሆነ የገለፁበት ንግግር አድርገዋል።
በቀጣይም የነፃነት ተምሳሌቱና የጀግናው አንዳርጋቸው ፅጌ ወ/ሮ ብዙሃየው ፅጌ ስለ ወንድማቸው ያለበት ሁኔታና አንዳርጋቸውን ለማስፈታት በዲያስፖራ ኢትዮጵያን እየተደረገ ያለው ተቃውሞ ፍሬ አፍርቶ ባሁን ጊዜ በተባበሩት መንግስታት፣ በአሜሪካንና በእንግሊዝ መንግስት የነፃነት ታጋዩን አንዳርጋቸው ፅጌ ይፈታ ዘንድ ከፍተኛ ጫና እየተደረገ መሆኑንና ይህም የኢትዮጵያ ህዝብ በተለይም የዲያስፖራው ትልቅ ተጋድሎ መልስ መሆኑንና ትግሉም አንዳርጋቸው ፅጌ ማስፈታት ብቻ ሳይሆን ነፃነት ያጣውን የኢትዮጵያ ህዝብ ከወያኔ ስርሃት እስኪፈቱ ድረስ ትግሉ መቀጠል እንዳለበት አሳስበዋል።
በኖርዌይ ለሚገኙ ኢትዮጵያን ያላሰለሰ ድጋፍ ያደርጉ ለነበሩት የኖርዌይ ስታቫንገር ማህበራዊ ተቃውማት የምስጋና ሰርተክፌት የተሰጠ ሲሆን
ከዚያ በማስከተል መድረኩን የተረከቡት  የአበኞች ግንቦት 7 አመራር ዶ/ር ሙልዋለም አዳም ሲሆኑ ባሁን ሰሃት የአርበኞች ግንቦት 7 አመራሮች በኤርትራ በረሃ ላይ እያደረጉ ያለውን እንቅስቃሴና ወሳኝ ምህራፍ ላይ ስላለው ትግል እንዲሁም አርበኞች ግንቦት 7 ከየትኛውም አይል ጋር አብሮ የሚሰራና ለመስራትም የሚጥር እንደሆነ እንደምሳሌም ከትህዴን/የትግራይ ህዝብ ዴሞክራሲ ንቅናቄ/ ፣ ከአፋርና ከጋምቤላ ነፃ አውጪ ድርጂቶች ጋር ተባብሮ በመስራት ላይ እንደሆነ ገልፀው አሁን የውይይትና የወሬ ጊዜ አይደለም እንቅስቃሴውን ሰምታቹዋል በየቀኑ ከወያኔ ሃይል ጋር ትንቅንቅ እያደረጉ ነው ስለዚህ ይህን ትግል ለመደገፍ የእናንተን ድጋፍ ይፈልጋልና ትግሉን ለመደገፍ እንነሳ ብለዋል።
11998882_1620630568224331_9029763007235433616_n11947586_1620630201557701_1920486985203716960_n
በመጨረሻም ከታዳሚ ለሚሰነዘሩ ጥያቄና አስተያየት መልስ የሚሰጥበት ሆኖ በግልፅነትና በጨዋነት ለተነሱ ጥያቄዎች ከመድረክ መልስ እየተሰጠባቸው የሰከነ ውይይት ተደርጎ በዝግጂት ክፍሉ ሰብሳቢና በዲሞክራሲያዊ ለለውጥ የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ስታቫንገር ቅርንጫፍ አቶ አብዩ ጌታቸው የመዝጊያ ንግግር ተደርጎ በአበኞች ግንቦት 7 መዝሙር በመዘመር የተሳካ ውይይት ተደርጎ ተጠናቅዋል።
ድል ለኢትዮጲያ ሕዝብ!!!!!
በዲምክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ  የድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ ስታቫንገር!!!!

ቴዲ “የፍቅር ነብዩ”ን ተውት ስለ ፍቅር ደግሞ ደጋግሞ ይዘምር … (ፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም)

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

እረ ተዉኝ ባትነኩኝ ምናለበት
አባካችሁ ሰዎች ስራዬን ልስራበት።
ታላቁ ጥላሁን ገሠሠ

ፍቅር ሁሉንም ድል ያደርጋል !
ሸክስፒር “አስራሁለተኛው ሌሊት“ በሚለው የትያትር ፁሁፋቸው ላይ የኦርሲኖ መስፍን በአዳራሹ ተሰባስበው ለነበሩት ድምጻውያንና ሙዚቀኞች  እንዲህ በማለት ተናግረው ነበር፣ “ሙዚቃ የፍቅር ምግብ እስከሆነ ድረስ አሁንም ዘምሩ፣ በርካታ ሙዚቃዎችን ደግማችሁ ደጋግማችሁ ዘምሩልኝ…“
Teddy Afro, Ethiopian popular singer
እራሱን ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ (ህወሀት) እያለ የሚጠራው የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በቅጽል ስሙ ቴዲ አፍሮ እየተባለ የሚጠራውን ቴዎድሮስ ካሳሁንን በሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ከብዙ ጊዜ በፊት ጀምሮ ለመንፈሳቸው እርካታ ምግብ የሆነውን የህዝቦች የፍቅር ሙዚቃ እንዳይጫወት እገዳ ሲጥልበት ቆይቷል፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ የቴዲን ህይወት እንደ እነርሱ በመከራ የታጀበ እንዲሆን አጥብቀው ይሰራሉ፡፡ እንደ እነርሱ “የመከራ ፍቅር ኩባንያ“ እንዲሆን ይፈለጋል፡፡
ቴዲ ግን ስለሰው ልጆች ፍቅር ደስታ እንጅ በምንም ዓይነት መልኩ ስለመከራ አይዘምርም፡፡
ቴዲ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብን ለማገልገል የተፈጠረ ድምጻዊ ከያኒ አይደለም፡፡ ስለመከራ እና ስቃይም አይዘምርም፡ መዘመርም አይችልም።
ቴዲ መቸውንም ጊዜ ቢሆን ለወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ባዶ ፕሮፓጋንዳ ማድመቂያ የሆኑትን የጥላቻ፣ የበቀል፣ ኢፍትሀዊ እና ጥልቅ ጥላቻዎችን የሚያነግሱ ሙዚቃዎችን በምንም ዓይነት መልኩ አያቀነቅንም፡፡
እርሱ የሚያቀነቅናቸው ስለደስታ፣ ስለሰላም፣ ስለአንድነት፣ ስለሀገር እና አህጉራዊ ፍቅር፣ ስለኢትዮጵያዊነት፣ ስለአፍሪካዊነት እና በአጠቃላይ ስለሰው ልጆች ፍቅር ነው፡፡ እንደ ሙዚቀኛ ሊዘምር የሚፈልገው እና በተግባር እያሳየ ያለው ስለዚያ ብቻ ነው፡፡ ስለፍቅር ብቻ ነው፡፡
ጥቂት ሰዎች ጥላቻን ለማራገብ የተፈጠሩ ናቸው፣ ሌሎቹ ደግሞ የዕድል ዕጣ ፈንታቸው ስለፍቅር መኖር ነው የሚል አባባል አለ፡፡
ቴዲ የተፈጠረው እና የዕድሉ ዕጣ ፈንታም የፍቅርን ድል አድራጊነት ወንጌል በዓለም ላይ ለሚገኙ ህዝቦች ሁሉ ለመስበክ ነው፡፡ ይኸው ነው ሌላ ተክዕኮ የለውም፡፡
ቴዲን ከሚወዳት ኢትዮጵያ ለማለያየት እና ጥሏት እንዲሰደድ ሌት ከቀን ጥረት የሚያደርጉት ለምንድን ነው?
አሁን በቅርቡ በአማርኛ ቋንቋ ተዘጋጅቶ በድረ ገጽ የግንኙነት መስመር በተለቀቀ ዘገባ መሰረት ይፋ እንደተደረገው የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ቴዲን ከሀገር ለማስወጣት እና በግዞት ወይም ደግሞ ከዚያ በከፋ መልኩ እንዲኖር ለማድረግ የወሰነ መሆኑን በግልጽ አመላክቷል፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ የሚወዳትን ሀገሩን ጥሎ እንዲሰደድ ለበርካታ ዓመታት በቴዲ አፍሮ ላይ የስነ ልቦና፣ የሕግ እና የኢኮኖሚ ጦርነቶችን እና ጫናዎችን ሲያካሂድበት እና ሲፈጽምበት ቆይቷል፡፡
እነዚህ የጥላቻ እና የበቀል ጎተራዎች ታዋቂውን ድምጻዊ ከያኒ አሳንሶ የማየት፣ ስብዕናውን በማንኳሰስ ዝቅ አድርጎ እንዲያስብ እና የማዋረድ ዕኩይ ድርጊቶችን ሲፈጽሙበት ቆይተዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ2008 የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በቴዲ አፍሮ ላይ ሰውን በመኪና ገጭቶ በማምለጥ የሚል የፈጠራ ክስ በመክሰስ በቁጥጥር ስር እንዲውል አድርገዋል፡፡
ይህንን የፍብረካ ወንጀል በመጎንጎን ለይስሙላው የዝንጀሮ/የጦጣ ፍርድ ፍቤት እንዲቀርብ በማድረግ ለ6 ዓመታት ያህል በእስር ቤት እንዲማቅቅ ውሳኔ ተላልፎበት ነበር፡፡
ሆኖም ግን ድምጻዊው በእስር ቤት ቆይታው ወቅት ባሳየው ጥሩ ስነምግባር በሚል በአመክሮ 6 ዓመታት የነበረው የእስራት ጊዜ ወደ 2 ዓመታት ዝቅ እንዲል ተደርጓል፡፡
በድምጻዊው ላይ የሀሰት ውንጀለቀ ተፈብርኮ የተቀነባበረውን የፈጠራ ክስ በማስመልከት “ጀግናው ከያኒ፡ የቴዲ አፍሮ የሙዚቃ ግጥም ስንኞች“ በሚል ርዕስ ትችት አቅርቤ የነበረ ሲሆን በዚያ ትችት ላይ ሰውን ገጭቶ በመግደል እና በማምለጥ በሚል የፈጠራ የውንጀላ ክስ ላይ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አቀረብኳቸው ያላቸውን ማስረጃዎች በመመርመር ከሕግ አንጻር ምንም ዓይነት ውኃ የማይቋጥር እና በተራ በቀልተኝነት ላይ የተመሰረተ እና በደፈናው ከያኒውን ለማጥቃት በማሰብ የእስራት ቅጣት የተወሰነበት መሆኑን አጋልጨ ነበር፡፡
ቴዲ እ.ኤ.አ በ2012 “ጥቁር ሰው“ የሚለውን አልበሙን በለቀቀበት ጊዜ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በቴዲ አፍሮ ላይ በማህበራዊ የግንኙነት ዘዴዎች አማካይነት ከፍተኛ በሆነ የማዋረድ እና ስም የማጥፋት ዕኩይ ዘመቻ ከፈተ፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ማንነታቸውን በደበቁ አጥቂ ተዋጊ ሰው አልባ ስም አጥፊ ተዋጊዎች በማህበራዊ ድረ ገጾች እና ሌሎች የመገናኛ ዘዴዎችን በመጠቀም ቴዲን ጥላሸት የመቀባት ዘመቻ ላይ ተጠመደ፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስቦች በ19ኛው ክፍለ ዘመን ዳግማዊ አጼ ምኒልክ የአፍሪካዊ ክብር መገለጫ እና የነጻነት ታጋይ በማለት በሀሰት በመኮፈስ ይልቁንም ጨካኝ እና ጨፍጫፊ የነበረ ንጉስ ነው በማለት የሀሰት የውንጀላ ክስ በማሰማት ቴዲ በሙዚቃው ንጉሱን የገነነ እና ታዋቂ ለማድረግ ጥረት አድርጓል በማለት የባጥ የቆጡን ቀባጥረዋል፡፡
ይህንን የወያኔውን ክህደት እና ቅጥፈት፣ እንዲሁም ተራ ውሸት እና የደንቆሮ የበታችነት ስሜት የበቀል ቅጥፈት በቴዲ አፍሮ የሙዚቃ የግጥም ስንኞች እና ቃና ባለው ዜማው የተዜመ ብቻ ሳይሆን መላው የአፍሪካ ህዝብ እና ዓለም ያደነቀው እና የመሰከረለት ታላቅ ገድል ነው፡፡ ምኒልክን አክብሯቸው፣ አድንቋቸው ታላቁ እና እውነተኛው ሀገር እና ህዝብ አፍቃሪ ንጉሳችሁ የነበሩ እንጅ አሁን እናንተ ሌት ቀን እንደበቀቀን እንደምትለፈልፉለት ከሀዲ እና የባንዳ ዝርያ፣ ሀገር ሻጭ እና በጎሳ ከፋፋይ የሀገር እና የህዝብ ጠላት አልነበሩም፡፡
በእርግጥ ቴዲ በሙዚቃ አልበሙ ለሀገራቸው ሉዓላዊነት እና ክብር ሲሉ ሁሉም ጎሳዎች እና ቡድኖች ሲዋደቁ እና የህይወት መስዋዕትነትን ከፍለው ይህችን ሀገር ያስረከቡንን ጀግኖች እና ታዋቂ ሰዎችን አንበሳ አድርጎ በመሳሉ እና በመዘከሩ ምክንያት ይህ ለወያኔው ታላቅ ሸክም እና ጥላቻ ነው፡፡
እ.ኤ.አ ታህሳስ 2013 የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በቴዲ ላይ የማጠልሸት፣ ጥለሸት የመቀባት፣ የማዋረድ እና ዝቅ አድርጎ የማየት ሌላ ዘመቻ ከፈተ፡፡
ቴዲ “ለእኔ የምኒልክ የአንድነት ዘመቻ ቅዱስ ጦርነት ነበር“ ብሎ ቃለ መጠይቅ ላይ ተነግሯል ብለው የሐሰት ወሬ በመንዛት የውንጀላ ውርጅብኝ ክስ በመመስረት አደንቋሪ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻቸውን ቀጠሉ፡፡
ለመሆኑ ህዝብን ሰውን ሁሉ አንድ ማድረግን እና በፍቅር እንዲተሳሰሩ ከማድረግ በላይ ምን ቅዱስነት ነገር አለ!?
በጎሳ መለያየት፣ እርስ በእርስ ማባላት፣ በህዝብ መካከል የጥላቻ መርዝ መዝራት፣ ጎጠኝነትን ማስፋፋት፣ የኃይማኖት ጽንፈኝነትን በማራገብ ልዩነትን መፍጠር፣ ህዝብን በረሀብ እና በችጋር እየለበለቡ ኢኮኖሚው በሁለት አሀዝ አድጓል፣ ተመንድጓል እያሉ መቀባጠር፣ ትውልድ ገዳይ የትምህርት ፖሊሲ ነድፎ ለምንም ለማንም የማይጠቅም ትውልድን እየፈጠሩ የጫት እና የሌሎች አደንዛዥ ዕጽ ሰለባ እያደረጉ ብሎኬቶች በመቆለል ብቻ እድገት እና ልማት ይመጣ ይመስል ህዝብ ግብር እየከፈለ በሚያስተዳድራቸው በብዙሀን መገናኛ ዘዴዎች ሌት ቀን ፕሮፓጋንዳ መስራት????
ለእናንተ ዕድገት ማለት ይኸ ነው፡፡
በህዝባቸው ዘንድ እምዬ ምኒልክ የሚል ተቀጽላ ስም የተሰጣቸው እናንተ በፈጠራ ውሸት ተክናችሁ ሁሌ እውነትን ሀሰት፣ ሀሰትን እውነት፣ ቀዩን ጥቁር፣ ጥቁሩን ነጭ እያላችሁ እንደምታቀርቡት የበሬ ወለደ ዓይነት አስተሳሰብ ላይ ተመስርቶ የተሰጠ ስያሜ ሳይሆን በእርግጥም ምኒልክ ለአንድ ጎሳ፣ ቡድን፣ ብሄረሰብ፣ ዘር፣ ኃይማኖት፣ ማንነት ሳይሆን ለሁሉም ኢትዮጵያዊ ወገኖቻቸው ሁሉ የእናትነትን ባህሪ የተላበሱ፣ እንደ እናት ፍቅርን የሚለግሱ እውነተኛ አፍሪካዊ መሪ በመሆናቸው ብቻ ነው፡፡
ይህ ታሪካው እውነት የማይካድ ነው።
ከዚህ አንጻር በቴዲ አፍሮ “ቅዱስ ጦርነት” ብሏል የተባልዌ ሐሰት ኢትዮጵያን አንድ ለማድረግ የተደረገውን ተጋድሎ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ጠምዝዞ እና በሚያውቅበት ሸፍጥ የመስራት ተንኮሉ በማጣመም “ዘር ማጥፋት” ብሎ ፈረጀው፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በቴዲ አፍሮ ላይ የከፈተው ዋና ስም የማጠልሸት ተልዕኮ ማጠንጠኛው የዳግማዊ ምኒልክን ስም የማጠልሸት ዘመቻ ነው፡፡
በእርግጥ  ያ ሁሉ ድንፋታ በመንግስትነት ደረጃ ስልጣንን ተቆጣጥሪያለሁ ከሚል ድርጅት የማይጠበቅ የወረደ እና ተራ ወሮበልነት ነው፡፡ የሀገሩ መሪ በህዝቡ፣ በአህጉር እና በዓለም አቀፋዊ መድረኮች ሁሉ ስለደግነቱ እና ስለጀግንነቱ ሲወደስ ደስ ሊለው እና ሊኮራ ይገባዋል እንጂ መሰሪ ቀናተኛ ጠላት ሆኖ መቅረብ ከአስተሳሰብ ዝቅጠት የመነጨ ነው ከማለት ሌላ ምን ሊባል ይችላል!
ይልቁንም የወያኔው ድብቁ እና እውነተኛው አጀንዳ አሁን በህይወት የሌለውን እና በጨፍጫፊነቱ እና በአምባገነንነቱ እውቅና ያለውን እ.ኤ.አ በ2005 የተካሄደውን ሀገር አቀፍ ምርጫ ተከትሎ ተከስቶ በነበረው ውዝግብ በእራሱ ትዕዛዝ በመቶዎች የሚቆጠሩ ንጹሀን ሰላማዊ ዜጎች ምርጫው መጭበርበሩን በማስመልከት ተቃውሟቸውን ሰላማዊ በሆነ መልኩ የገለጹትን ወገኖቻችንን በአደባባይ እንዲጨፈጨፉ ያደረገውን የመለስ ዜናዊን የዘር ማጥፋት ወንጀል ለመሸፋፈን እና ለመደበቅ ሲባል የሚደረግ ሸፍጥ ነው፡፡
ይህ ብቻ አይደለም ከዚያ ቀደም ሲልም ሆነ ከዚያ ወዲህ በበደኖ፣ በአሰበ ተፈሪ፣ በጎንደር በእየሱስ ቤተክርስቲያን ቅጥር ግቢ፣ በአርሲ፣ በጋምቤላ፣ በኦጋዴን እና በሌሎች በተለያዩ ቦታዎች እና አካባቢዎች ዘርን መሰረት ያደረገ የዘር ማጥፋት ፍጅት መፈጸሙን ልብ ይሏል! የአቦን ቅጠል የቀመሰች ፍየል ያስለፈልፋታል ይባል የለ! ነገሩ እንደዚያ ነው፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በፈጠረው ውዝግብ ምክንያት ቴዲ አፍሮ በአሁኑ ጊዜ የደች/ሆላንድ ንብረት በሆነው በሄይከን ኩባንያ እየተዳደረ ከሚገኘው ከበደሌ ቢራ ፋብሪካ ጋር ስምምነት በማድረግ ሊያቀርብ የነበረውን ኮንሰርት እንዲሰረዝ ተደርጓል፡፡
እ.ኤ.አ በ2014 የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ”ግብር ማጭበርበር” የሚል ሌላ የፍብረካ ውንጀላ በማቀነባበር ቴዲ አፍሮን እንደገና በእስር ቤት ለማማቀቅ ሙከራ አደረገ፡፡ የውንጀላ ክሱ የቀረበው ከ7 ወይም ደግሞ ከ8 ዓመታት በፊት ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ ላስገባው ተሽከርካሪ ግብር አልከፈለም የሚል ነበር፡፡
ሊገመት ከሚችለው በላይ ድፍረትን በተላበሰ መልኩ ፍርድ ቤቱ የግብር ማጭበርበሩን ጉዳይ ለማጣራት ተጨማሪ ቀናትን ለፖሊስ ለመስጠት እና ቴዲ አፍሮም በእስር ቤት ይቆያል የሚለው አስፈላጊ አይደለም ይህንንም አልቀበልም አለ፡፡ (ደፋር ዳኛው ከወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ፊት ለፊት በመቆም! አይታመንም!!)
እ.ኤ.አ በ2015 የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ጆሮ ጠቢዎች ቴዲ በሚሄድበት ቦታ ሁሉ እንደጥላ ይከታተሉት ጀመር፡፡
ቴዲ እናቱን ለመጎብኘት በሚሄድበት ጊዜ አነፍናፊ አዳኝ ውሾችን ያስከተሉ ጆሮ ጠቢ ወሮበሎች ተከትለውት ሄዱ፡፡
ወደ ከተማ በሚሄድበት ጊዜ ሞተር ብስክሌት በሚይዙ ወሮበሎች አማካይነት መሰናክል እንዲፈጠርበት ይደረጋል፡፡
የሲቪል ልብስ የለበሱ ወሮበሎች አንገቱን እንቅ አድርገው ይይዙታል፡፡ በመንገድ ላይ በመጓዝ ላይ እያለ ድንገት ያስቆሙት እና ያስፈራሩታል፡፡
የስልክ መስመሮቹ ይጠለፋሉ፡፡
ቤቱ ቀጣይነት ባለው ሁኔታ በፖሊስ ምርመራ ስር ነው፡፡
በየጊዜው በወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ የይስሙላ የዝንጀሮ ፍርድ ቤቶቸ እየቀረበ የማስፈራሪያ ድርጊት ይፈጸምበታል፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በኤፍ ኤም የሬዲዮ ጣቢያው በመጠቀም ቴዲን በገንዘብ ኪሳራ ውስጥ እንዲወድቅ እና የገነባውን ታላቅ ስሙን ለማጥፋት ሌት ቀን የፕሮፓጋንዳ ስራውን ይቀጥላል፡፡ ስሙን በማብጠልጠል ላይ ይገኛሉ፡፡ ያለምንም የሕግ ተጠያቂነት እያወገዙት እና ስም የማጥፋት ዘመቻቸውን ቀጥለውበት ይገኛሉ፡፡
በሀገር ውስጥም ሆነ ወደ ውጭ ሀገር በመሄድ ህይወቱን መምራት እንደማይችል ከፍተኛ የሆነ ችግር እየፈጠሩ ከህዝብ ለመለየት ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡
አሁን በቅርቡ የቴዲ አፍሮ ባለቤት ለህክምና ጉዳይ ወደ ኬንያ ሄዳ በነበረችበት ጊዜ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አውሮፕላኑን በማስቆም ቴዲን ምንም ዓይነት ክፍያ ሳይከፍል ተደብቆ ለመሄድ ሲሞክር እንደተያዘ ሕገ ወጥ ሰው እየገፉ እና እየጎተቱ በአደባባይ ሲያንገላቱት በህዝብ ተስተውሏል፡፡
እንደዚሁም በሌላ ጊዜ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ  ቴዲን በማዋረድ እና የሞራል ስብዕናውን ዝቅ በማድረግ እነርሱ የእርሱ ጌቶች እንደሆኑ የማሳየት ስራ ሰርተዋል፡፡
ቴዲ ያለው ትልቁ ጌታው ወያኔ ሳይሆን ታላቁ የፍቅር ኃይል ነው!
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ተከታታይነት ባለው ሁኔታ ቴዲ አፍሮን ያስፈራሩታል ምክንያቱም ቴዲ የእነርሱን ሙዚቃ አይዘምርም፣ የእነርሱን ዳንስ አይደንስም፣ እንደዚሁም የእነርሱን የጥላቻ ከበሮ አይደልቅም፡፡
ለዚህም ነው እትብቱ ከተቀበረችባት እና ከሚወዳት ሀገሩ እንዲሰደድ ጥረት በማድረግ ላይ ያሉት፡፡
ሆኖም ግን ቴዲ እስከ አሁን ድረስ በሚወዳት ሀገሩ ቆይቷል፡፡ የእራሱን ሀገር ትቶ በማንም ወሮበላ አስገዳጅነት የትም ቦታ ቢሆን አይሄድም፡፡
በውጭ ሀገር ተሰድዶ ነጻ ሆኖ ከመኖር ይልቅ በሀገሩ ውስጥ ሆኖ እጆቹ በካቴና ታስረው በግፈኛ አምባገነኖች እየተሰቃዬ እና ሰብአዊ መብቱ እየተደፈጠጠ መኖርን ይመርጣል፡፡
የእውነተኛ አርበኝነት ባህሪ እንደዚህ ነው!
ጥላቻ የበለጠ እየከረረ እና እየመረረ በሄደ መጠን ጥቂቶች ሀገር ለቀው ይሰደዳሉ፣ ሌሎች ጥቂቶች ደግሞ መከራውን እና ስቃዩንም አሳቱንም ችለው በሀገራቸው ይቆያሉ ይባላሉ፡፡
ቴዲ ግን የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብን እሳት ፊት ለፊት ተቋቁሞ በሀገሩ በመኖር ላይ ይገኛል፡፡
ቴዲ የኢትዮጵያ ነገስታት የነበሩትን ዳግማዊ ምኒልክን እና ቀዳማዊ አጼ ኃይለ ስላሴን በማወደሱ እና ጀግንነታቸውን በመመስከሩ ብቻ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ከልቡ ምርር አድርጎ ጠልቶታል፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አመራሮች እና አባላት “የኢትዮጵያን ታሪክ ጥላሸት መቀባት“ በሚል ርዕስ አዘጋጅቸው በነበረው ትችቴ ላይ ከዳግማዊ አጼ ምኒልክ እና ከቀዳማዊ አጼ ኃይለስላሴ ይልቅ አሁን በህይወት የሌለው አምባገነኑ መለስ ዜናዊ የፈጸማቸው ትግባራት የበለጡ ናቸው የሚለውን ቅጥፈታቸውን ለማጋለጥ ሞክሪያለሁ፡፡
ቴዲ አሁን በህይወት ለሌለው ለአምባገነኑ መለስ ዜናዊ እና ለእርሱ ታዛዥ ሎሌዎቹ የሚዘምር ቢሆን ኖሮ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በዚህ ከያኒ ላይ እንደዚህ ያለ ማቋረጫ የሌለው ጦርነት እና የማሰቃዬት እኩይ ድርጊት ሊፈጽሙበት ይችሉ ነበርን?
ቴዲ በእውነታው ዓለም ላይ ያሉትን ጅቦች አንበሳ አድርጎ ቢያቀርባቸው ኖሮ ጆቦቹ ለምን እንደ አንበሳ ተደርገን ተፈረጅን ብለው ቅሬታዎቻቸውን ያቀርቡ ነበርን?
አሁን በህይወት ስሌለው አምባገነኑ መለስ ዜናዊ የሌለውን ስብዕና እንዳለው በማስመሰል “የአፍሪካ አባት” የሚል የሙገሳ መዝሙር ቢያሰማ ኖሮ በቴዲ ላይ እንደዚያ ያለ ጥላሸት የመቀባት እና የማዋረድ ድርጊት ይፈጸምበት ነበርን?
ቴዲን መዘለፍ አልፈልግም ሆኖም ግን የመለስ ዜናዊ ምስል ያለበትን ቲ ሸርት (ካናቴራ) በመልበስ በኮንሰርቱ ላይ ቢታደም ኖሮ በወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ የማስፈራራት ድርጊት ይፈጸምበት ነበርን?
በቴዲ ላይ ማቋረጫ የሌለው ስቅይት እና ማስፈራራት ቢፈጸምበትም ቅሉ ምንም ዓይነት ቅሬታ አላሰማም፡፡ ሌላ ምንም ነገር ትንፍሽ አላለም፣ እንዲህ ነበር ያለው፣ “ፍቅር ሁሉንም ነገር ያሸንፋል፡፡“
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ለ25 ዓመታት ያህል በስልጣን ኮርቻ ላይ ተፈናጥጦ “ጥላቻ ሁሉንም ነገር ያሸንፋል“ በማለት የእራሱን ደስታ በመግለጽ ላይ ይገኛል፡፡
ጥላቻ ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን አሸናፊ ሆኖ ሊታይ ይችላል፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ የሚወዱት ብቸኛው ነገር ቢኖር ጥላቻን እራሱን ነው፡፡
ሆኖም ግን ቴዲ የማይበገር ጀግና ነው፡፡ እንዲህ እንደሚሉትን የዶ/ር ማርቲን ሉተር መርሆዎች እያስተጋባ የሚኖር ይመስላል፣ “ጥላቻን ጥላቻ አያስወግደውም፣ ይህንን ማድረግ የሚችለው ፍቅር ብቻ ነው፡፡“ በሌላ አባባል “ፍቅር ሁሉን ነገር ያሸንፋል፡፡”
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ቴዲ አፍሮን የሚፈራው ለምንድን ነውቴዲን እንደዚህ ጥቁር ጥምድአድርገው የሚጠሉት ለምንድን ነው!?
እስቲ ስለቴዲ የማያወዛግቡ ጥሬ ሀቆችን ይፋ እናድርግ፡
እንደ ድምጻዊ አቀንቃኝ ቴዲ አፍሮ አቻ የማይገኝለት ድምጻዊ ነው! ምንም ዓይነት ተወዳዳሪ የለውም!
ቴዲ እንዲህ የሚሉትን ባህሪት የተላበሰ ምጡቅ ድምጻዊ ነው፡  በስብዕናው አንድ ዓይነት ወጥ ነው፣ የግጥም ስንኞቹ ምትሀታዊ ኃይልን የተላበሱ ናቸው፣ የዜማ ቅላጼዎቹ ማራኪ፣ መንፈስን በደስታ ስሜት ውስጥ የማስጋለብ እና የሰውን ቀልብ የመቆጣጠር ኃይል ያላቸው ናቸው፣
ቴዲ አፍሮ ልዩ ተሰጥኦ ያለው የሙዚቃ ሰው ነው! ምንም ዓይነት ጥያቄዎች ሊነሱበት የሚገባ ጉዳይ አይደለም! ምንም ዓይነት!
እንደዚሁም ሁሉ ቴዲ አፍሮ ነገሮችን በጥልቀት የማየት ችሎታ ያለው የጥልቅ ሀሳብ ባለቤት ሰው ነው፣ ለሁሉም ነገር ጥንቃቄን የሚያደርግ፣ በፍቅር የተሞላ እና ብሩህ አዕምሮ ያለው ሰብአዊ ፍጡር ነው፡፡
በሚያቀርባቸው በሁሉም ሙዚቃዎቹ ስለህይወት ፍልስፍናው ያስተምረናል፡፡ ይህ ፍልስፍናው በሶስት ቃላት እንደሚከተለው ተጠቃሎ ሊቀርብ ይችላል፡ “ፍቅር ሁሉንም ያሸንፋል”፣ ይኸው ነው! ሌላ ምንም ነገር የለም!
ቴዲ ስለይቅርታ ማድረግ እና ዕርቀ ሰላም ስለማውረድ ይዘምራል፡፡
ስለሀገሩ እና አህጉሩ ፍቅር ይዘምራል፡፡
ስለብሄሮች እና ስለኃይማኖቶች ተቻችሎ መኖር ይዘምራል፡፡
ስለኢትዮጵያ ዝና አጥብቆ ይዘምራል፡፡
ኢትዮጵያ ነጻነቷን እንድትቀዳጅ፣ ከቅኝ ገዥነት ነጻ እንድትወጣ፣ ከውጭ የበላይነት ነጻ እንድትሆን ሉዓላዊነቷን አስጠብቃ እንድትኖር መተኪያ የሌላት ህይወታቸውን ገብረው ላቁዩአት ጀገኖች ልጆቿ ይዘምራል፣ ያቀነቅናል፡፡
የነጻነት መዝሙሮችን ይዘምራል፡፡
ቴዲ እንደ ቦብ ማርሌይ ሁሉ እንዲህ የሚሉ የሙገሳ ሙዚቃዎችን ይዘምራል፡
እነዚህን የትንሣኤ ሙዚቃዎች ለመዘመር እገዛ አታደርጉምን/እነዚህን የነጻነት ሙዚቃዎች?/እስከ አሁን ያሉኝን ሁሉ ዘምሩ፡/የትንሣኤ ሙዚቃዎች/እስከ አሁን ያሉኝን በሙሉ፡/የትንሣኤ ሙዚቃዎች፡/እነዚህን የነጻነት ሙዚቃዎች፡፡/የነጻነት ሙዚቃዎች አብራችሁኝ አትዘምሩም።
ሁሉም የትንሣኤሙገሳ ሙዚቃዎች የቴዲ አፍሮም ናቸው፡፡
ቴዲ እንዲህ በማለት ይጠራዋል፣ “የኢትዮጵያ ትንሳኤ” (የኢትዮጵያ የሙገሳ/ትነሳኤ)፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በአሁኑ ጊዜ ቴዲ አፍሮን ማቋረጫ በሌለው መንገድ ለምን እያሰቃዬው እንዳለ ምንም ሀሳብ የሌኝም ፈፅሞ  አይገባኝም፡፡
ቴዲ እውነታውን በመዘመሩ ምክንያት ሊሆን ይችላልን?
እውነትን በሚጠሏት መካከል ጠላቶችን እንዴት እንደሚያፈራ ልገንዘብ እችላለሁ፡፡
ቴዲ ስለፍቅር በመዘመሩ ምክንያት ሊሆን ይችላልን?
ጥላቻ በደም ስሮቻቸው በተዋሀዱት መካከል የማይሞቱ ጠላቶች እንደሚያፈራ እገነዘባለሁ፡፡
ቴዲ ስለይቅርታ አድራጊነት በመዘመሩ ምክንያት ሊሆን ይችላልን?
በበቀል እና በጥላቻ በተዘፈቁት መካከል ጠላቶችን እንዴት እንደሚያፈራ ልገነዘብ እችላለሁ፡፡
ቴዲ ስለዕርቀ  ሰላም በመዘመሩ ምክንያት ሊሆን ይችላልን?
የህይወት ተልዕኳቸው ከፋፍሎ መግዛት በሚሉት መካከል ጠላቶች እንዴት እንደሚያፈራ ልገነዘብ እችላለሁ፡፡
ቴዲ ስለ ኢትዮጵያ ትንሳኤ በመዘመሩ ምክንያት ሊሆን ይችላልን?
በኢትዮጵያ ገዳዮች መካከል ጠላቶች እንዴት እንደሚያፈራ ልገነዘብ እችላለሁ፡፡
ቴዲ ስለኢትዮጵያ አንድነት በመዘመሩ ምክንያት ሊሆን ይችላልን?
ኢትዮጵያን በመክተፊያ ቢላዋ በመተሯት እና እንዴት የጎሳ፣ የብሄረሰብ ቡድኖች፣ የኃይማኖት እና የክልል ጎጠኛ ደሴት ባደረጓት መካከል ጠላቶች እንዴት እንደሚያፈራ ልገነዘብ እችላለሁ፡፡
ቴዲ ስለለሁሉም ኢትዮጵያውያን የወደፊት የተሻለ ህይወት በመዘመሩ ምክንያት  ሊሆን ይችላልን?
በዕኩይ ምግባራቸው ምክንያት ዕጣ ፈንታቸው ወደ ታሪክ ቆሻሻ ማጠራቀሚያ መጣል ባለባቸው መካከል ጠላቶች እንዴት እንደሚያፈራ ልገነዘብ እችላለሁ፡፡
ቴዲ ስለኢትዮጵያ ጥንታዊ ዝና በመዘመሩ ምክንያት ሊሆን ይችላልን?
በጥላቻ በተሞሉ ሰይጣኖች፣ በቀልተኞች፣ እምነተቢስ መርህ አልባ ፍጡሮች እና በጫካ ወሮበሎች መካከል ጠላቶች እንዴት እንደሚያፈራ ልገነዘብ እችላለሁ፡፡
ቴዲ ስለኢትዮጵያ ተፈጥሯዊ ውበት እና ስለህዝቧ በመዘመሩ ምክንያት ሊሆን ይችላልን?
በሀሳብ የለሽ ጋጠወጦች እና በጭካኔ በተሞሉት ድድብና በተጠናወታቸው ወሮበሎች መካከል ጠላት እንዴት እንደሚያፈራ ልገነዘብ እችላለሁ፡፡
ሆኖም ግን ቴዲን ለመጥላት ወይም ደግሞ ለመፍራት ጥሩ ምክንያቶች አይደሉም፡፡
ሙሉ ህይወቱ ስለፍቅር፣ መልካም ጉርብትና፣ ስለሀገር ፍቅር እና ክብር፣ ስለአህጉር ፍቅር፣ ስለታሪክ ፍቅር እና ክብር፣ ስለሀገሩ ብዝሀነት እና ስለህዝብ ፍቅር እና ክብር መርሁ እና ተሞክሮው አድርጎ የሚንቀሳቀስን ሰው እንዴት መጥላት ይቻላል?
የሰው ልጆች ፍቅር የሆነ ሐዋርያትን እንዴት መጥላት ይቻላል?
ፍቅርን እራሱን የሚጠሉትን ምንነት የሚገልጽ እራሱን የቻለ ቃል/ሀረግ አለ፡፡ ይህም ቃል/ሀረግ “በሰዎች መጥፎ ዕድል ላይ የሚረካ“ እየተባለ የሚጠራ ሲሆን ቃሉም የተገኘው ከጀርመን ሆኖ አንድ ሰው በተፈጥሮው በሰዎች መጥፎ ዕድል፣ ስቃይ እና መከራ እጅግ የበዛን ደስታ የሚያደርግ እኩይ ሰይጣናዊ አስተሳሰብ ያለው የሚል የእንግሊዝኛ ትርጉም ያለው ሆኖ ይገኛል፡፡ በጥላቻ የተሞሉ ሰው መሳይ ሰይጣኖች ብቻ በሌሎች መከራ፣ ስቃይ እና ውርደት ሀሴትን ይጎናጸፋሉ፡፡
በሰዎች መጥፎ ዕድል ላይ የሚረካ ግብዝ ሸፍጠኛ/sadist በሌሎች ሰዎች ላይ በሚደርሰው ስቃይ፣ መከራ እና መጥፎ ዕድል እጅግ በጣም ደስተኛ እና ሀሴትን የሚያደርጉ፣ ለዚህ እኩይ ምግባርም ለእራሳቸው አዎንታዊ ምላሽ የሚሰጡ ሰው መሳይ በሸንጎዎች የሆኑ ሰይጣኖች ናቸው፡፡
በእንደዚህ ያለ በሰዎች ስቃይ እና መከራ ከፍተኛ የሆነ ሀሴት ባህሪያትን በተጎናጸፉ ሰዎች ሰይጣናዊ አስተሳሰብ ውስጥ ስቃይ፣ ሀዘን፣ እና የሌሎች ሰዎች መጥፎ ዕድል ማግኘት ማለት ለእነርሱ ደስታ፣ የሌሎች ስቃይ የእነርሱ ሀሴት፣ የሌሎች መከራን መቀበል ለእነርሱ ፍጹም የሆነ እርካታ ማለት ነው፡፡
በሌላ አባባል ከጥላቻ የመጨረሻ የሆነውን ደስታ ያገኛሉ፡፡ ይኸ ልዩ የሆነ ሰይጣናዊ ድርጊት ዋነኛ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አመራር እና አባላት መገለጫ ባህሪ ነው!
ለፍቅር ፍቅር ያላቸውን እና ፍቅርን እራሱን የሚጠሉ የፍቅር ጠላቶች ናቸው፡፡
ከተቃዋሚዎች ጋር ህብረት ፈጥሯል በሚል እሳቤ ነውን?
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ቴዲ አፍሮ ተቃዋሚዎችን ይደግፋል የሚል ውንጀላ ያሰማል፡፡ ይህ እራሱ ምን ማለት ነው?
በእርግጥ እነዚህ የጥላቻ ዕኩይ ምግባር አራጋቢዎች ቴዲ አፍሮን ፖለቲከኛ እንጅ ሙዘቀኛ አይደለም የሚል ሀሳብ ለማራመድ ይሞክራሉ፡፡
ቴዲ ፖለቲከኛ የሚሆንባት ዕለት የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ከሸፍጥ ነጻ የሆነ (ለዝንጀሮው/ጦጣ ፓርላማው ከ547 መቀመጫዎች ውስጥ 547ቱንም አሸንፊያለሁ ብሎ የሚያውጅ ሳይሆን) እውነተኛ ዴሞክራሲ እና የሰብአዊ መብት ጥበቃን እውን በሚያደርግባት ዕለት ነው፡፡
ያም የማይሆን ነገር ነው፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ተቃዋሚ ቡድኖችን ማገዝ ወንጀል ነው በማለት በዝንጀሮው/ጦጣው የይስሙላ ፍርድ ቤት ክስ መስርቶ ንጹሀን ዜጎችን ያሰቃያል!
አንድ ሰው የፈለገውን የፖለቲካ ፓርቲ ለመደገፍ ሕገ መንግስታዊ እና የሰብአዊ መብት ምርጫው አይደለምን?
ሆኖም ግን ቴዲ የፖለቲካ ሰው አይደለም፡፡ እርሱ የሙዚቃ ሰው ነው፡፡
በተጻራሪ መልክ አስገራሚው ነገር ደግሞ የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ቴዲ ገንዘብ በመስጠት፣ በሙዚቃ ኮንሰርት በማዘጋጀት እንዲያቀነቅንላቸው፣ እነርሱ እንዲዘምርላቸው የሚፈልጉትን ሙዚቃ በመስጠት በአደባባይ እንዲዘምርላቸው እና በፖለቲካ እንዲደግፋቸው ይፈልጋሉ፡፡
የቴዲ አጭር መልስ ግን አመሰግናለሁ ሆኖም ግን ይቅርታ አላደርግም የሚል ነው፡፡
እውነታው ፍርጥርጥ ተደርጎ ሲታይ ግን የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ቴዲ እንዲያደርግለት የሚፈልጋቸውን ነገሮች ሁሉ ለሌሎች የፖለቲካ ድርጅቶችም በተመሳሳይ መልኩ አንድም ነገር አላደረገም፡፡ ለምንድነው ለወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ እንዲህ ዓይነቱን ድርጊት የሚጀምረው?
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አለቆች ከተራ ሀሳብ ይልቅ የበለጠ ገንዘብ አላቸው፡፡
እንዲህ የሚለውን አባባል መዳመጥ እና መተግበር ይኖርባቸዋል፣ “ገንዘብ ፍቅር ሊገዛልኝ አይችልም፡፡“
“ገንዘብ ፍቅር ሊገዛልኝ አይችልም/ፍቅርን ሊገዛልኝ አይችልም፣ እያንዳንዱ ሰው ይህንን ነገር ይነግረኛል/ፍቅርን ሊገዛልኝ አይችልም፣ በፍጹም፣ በፍጹም፣ በፍጹም፣ በፍጹም…“
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ በማንኛውም መንገድ የኢትዮጵያን ህዝብ ፍቅር ወይም ደግሞ የፈለገውን ያህል ገንዘብ እንደጎርፍ ቢያወርድ የኢትዮጵያን ህዝብ ድምጽ ፍቅር ቴድን በምንም ዓይነት መልኩ አያገኝም! ሊገዛ አይችልም።
እኔ የቴዲ አፍሮ ቁጥረ 1 አድናቂ ነኝ!
ለበርካታ ዓመታት የቴዲ አፍሮ ቁጥር 1 አድናቂ ነኝ፡፡
በእርሱ ሙዚቃ ስዘምር እና ስደንስ ቆይቻለሁ፡፡ የሮጌን የሙዚቃ ምቶች እንዴት አድርጎ ወደ ኢትዮጵያ ባህላዊ የሙዚቃ ቅላጼ እንደሚቀይራቸው አደንቃለሁ፡፡
በአንድ በተወሰነ ቦታ ወይም አካባቢ የሙዚቃ ኮንሰርት በሚያዘጋጅበት ጊዜ ከሁሉም ወጣቶች ህዝቦች ጋር በመቀላቀል መልካም ጊዜን አሳልፋለሁ፡፡
በተለያዩ አጋጣሚዎች ስለቴዲ አፍሮ ጽፊያለሁ፡፡
እ.ኤ.አ በ2010 በሁሚንግ ፖስት ትችት ቴዲ በአካል በሚተላለፍ ትዕይንት ባቀረበው ስራው ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ በመገኘት ከተመለከትኩ በኋላ እንዲህ የሚል ጽሁፍ አቅርቤ ነበር፡
ቴዲን በአካል በሚተላለፍ ስራው ላይ በመገኘት ያቀረበውን ኮንሰርት ከዚያ በፊት ያልተመለከትን እና በአዳራሹ ከአፍ እስከ ገደቡ ጢም ብሎ ሞልቶ የነበረውን የተመልካች ብዛት በማየት ምስክርነቱን ለምንሰጥ ሰዎች ሁሉ በሀሳብ አውሮፕላን ወደ ኋላ ጭው ብሎ በመብረር በትዝታ ማዕበል ውስጥ እንድንዋኝ ያደርገናል፡፡ እንደዚህ ያለ በህዝቡ እና በከያኒው መካከል ጥልቅ የሆነ ትስስር በህይወቴ የተመለከትኩት ከብዙ አስርት ዓመታት በፊት እ.ኤ.አ ግንቦት 30/1978 በሜኖሶታ ዩኒቨርስቲ እየተማርኩ በነበርኩበት ቦታ ቦብ ማርሌይ በመምጣት አቅርቦት በነበረው (ካያ ቱር/Kaya Tour) እና እ.ኤ.አ ህዳር 15/1979 (ሰርቫይቫል ቱር/Survival Tour) የተሰኙትን ኮንሰርቶች ያቀረበባቸው ጊዚያት ትዝ አሉኝ፡፡ በእነዚያ ቦብ ማርሌይ ባቀረባቸው ኮንሰርቶች ላይ የመገኘት አጋጣሚ ዕድሉን ያገኛችሁ በእርግጠኝነት ምን ለማለት እንደፈለግሁ በትክክል ትገነዘባላችሁ የሚል እምነት አለኝ፡፡
እ.ኤ.አ ሰኔ 2014 ኮካኮላ የተባለው ድርጅት ቴዲ አፍሮን የማግለል ድርጊት ፈጽሞ ስለነበር ማንም ቢሆን ይህን ለውፍረት የሚዳርገውን እና በስኳር የተሞላውን ኮካኮላ የሚባለውን እርባናየለሽ መጠጥ ባለበት ድርሽ እንዳትሉ የሚል ትችት አቅርቤ ነበር፡፡
ኮካኮላ የተባለው ድርጅት ለ2014 በብራዚል ተደርጎ በነበረው የዓለም እግር ኳስ ጨዋታ ሻምፒዮን 32 የአካባቢ ድምጻውያን ስራዎቻቸውን እንዲያቀርቡ እና እንዲወዳደሩ ጋብዞ ነበር፡፡
ኮካኮላ ይፋ በሆነ መልኩ ከቴዲ አፍሮ በስተቀር የሁሉንም ተወዳዳሪዎች ስራዎች ለቅቆ ነበር፡፡ በእርግጥ ኮካኮላ በወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አለቆች ትዕዛዝ መሰረት የቴዲ አፍሮን ስራ ውድቅ እንዲያደርግ ትዕዛዝ ተሰጥቶት ነበር፡፡
ይህ ድርጊት ሁይትነይ እንደዘመረው ሁሉ ትክክል አይደለም ሆኖም ግን እሽ ከሚለው ጋር ተመሳሳይ እንደምታ አለው፡፡
(በዚያ እኩይ ድርጊቱ እስከ አሁንም ድረስ የኮካኮላ ምርት ውጤት የሆኑት ባሉበት ቦታ ድርሽ አልልም! ከዚህ አንጻር የኮካኮላ ምርትን ከምጠቀም ይልቅ የምጠጣው አጥቼ በውኃ ጥም ድርቅ ማለትን እመርጣለሁ፡፡ ይህ ለእኔ ሌላ ለምንም ነገር ሳይሆን ቀላል የመርህ ጉዳይ ነው፡፡ እንደዚህ ያለ ምርመራን እና አድልኦን የሚፈጽም ዓለም አቀፋዊ የንግድ ድርጅትን ልደግፍ የምችልበት ሞራሉ የለኝም፡፡ በዚያን ጊዜ ባቀረብኩት ትችቴ ላይ “ኮካኮላ ገሀነም ይግባ” በማለት ተናግሬ ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜ ኮካ ኮላ ገሀነም እንደደረሰ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡)
ቴዲ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ብዙም የሙዚቃ ኮንሰርት አያቀርብም፣ ሆኖም ግን በዓለም እንደ የአፍሪካ የሬጌው ንጉስ እየተባለ ሲወደስ እንደነበረው እንደ ቦምብ ማርሌይ በፍቅር መንፈስ የህዝብን ልብ ያስተሳሰረ ከያኒ መሆኑ ይነገርለታል፡፡ እንግዲህ ቴዲ አፍሮ በሙዚቃ ጥበቡ፣ በፍቅር ዘማሪነቱ እና በአጠቃላይ የዘርፉ ልቅናው የዚህን ያህል ክብር እና ሞገስ ያለው ከያኒ ነው፡፡
(“ሬጌ” የሚለው ቃል ከላቲን “ሬጊ” ከሚለው እና ንጉስ የሚል ትርጉም ካለው ቃል የመጣ ስለመሆኑ ስንቶቻችን እንደምናውቅ ብገነዘብ የሚገርመኝ ይሆናል፡፡ የሬጌ ሙዚቃ “የንጉስ ሙዚቃ” ነው፡፡)
እራሱን ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ እያለ የሚጠራው ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ደናቁርት ቴዲ የንጉሱን ሙዚቃ በማቀንቀኑ እና በሙዚቃ ሰራ ቅላጼዎቹ የዳግማዊ አጼ ምኒልክን እና የቀዳማዊ አጼ ኃይለ ስላሴን ስም እያነሳ በማወደሱ ምክንያት ወንጀል ተደርጎ በይስሙላው የዝንጀሮ/ጦጣው ፍርድ ቤት አንዳያንገላታው ተስፋ አረጋለሁ፡፡ (ሬጌ ሙዚቃ “የንጉስ ሙዚቃ” ነው ለጃማይካ ራስ ተፈሪያውያን፡፡)
እኔ ቴዲ አፍሮን የማውቀው በሰራቸው ቪዲዮ፣ በሚያዘጋጃቸው የሙዚቃ ኮንሰርቶች፣ በድረ ገጽ የግንኙነት መስመር በሚሰጣቸው ቃለ መጠይቆች እና ከሁሉም በላይ ደግሞ በሚያስተላልፋቸው የፍቅር፣ የመግባባት፣ የይቅርታ አድራጊነት እና ዕርቀ ሰላም ናፋቂነት ነው፡፡
ለዚህም ነው አንግዲህ የእርሱ ቁጥር 1 አድናቂው ለመሆን የበቃሁት፡፡
በእኔ የግል የግምገማ መስፈርት መሰረት ቴዲ አፍሮ እንደሙዚቃ ባለሞያነቱ ከፖፕ ሰታር (pop star) በላይ የመጠቀ እና የላቀ ድምጻዊ ከያኒ ነው፡፡ በእኔ አመለካከት ለዶ/ር ኪንግ፣ ለማንዴላ እና ለማህተመ ጋንዲ እሴቶች እና መርሆዎች ተግባራዊነት የቆመ የሙዚቃ ሐዋርያ ነው፡፡
ቴዲ ከፍተኛ የሆነ ክብር፣ ምስጋና እና አድናቆት ያለው ከያኒ ነው፡፡ በእርግጠኝነት ቴዲ ከእርሱ ትውልድ የተስፋ፣ የእምነት፣ የብሩህ አመለካከት እና የጽናት ተምሳሌት ቀንዲል ነው፡፡
(ለእኔ እውን ሆኖ የሚታይ ጉዳይ ነው!!! ቴዲ አፍሮ ከእርሱ የተስፋ፣ እምነት፣ የብሩህ አመለካከት እና የጽናት ተምሳሌት ቀንዲል ሆኖ በመገኘቱ ምክንያት በወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ መሰቃየት ሊኖርበት ይችላልን?)
በቅርቡ ኢትዮጵያዊው ገጣሚ ሄኖክ የሽጥላ  ስለቴዲ ክብር በአማርኛ ጥቂት የግጥም ስንኞችን ቋጥሮ ነበር፡፡
እርሱ የቋጠራቸው ሶስት የስንኝ ግጥሞች ወደ እንግሊዝኛ እንዲመለሱ በማድረግ ያቀረብኩ ሲሆን እንደገና የአማርኛ ትርጉማቸው በግጥም ስንኝ መልክ እንዲመለሱ በማድረግ ሁሉንም መተርጎም እችል ነበር፣ ሆኖም ግን የግጥሙ አንኳር የሆኑት ሶስቱ ስንኞች እንደሚከተለው ቀርበዋል፡
ቴዲ እንደ ዳዊትዘይት በቀንድ ዋንጫ
ቀብቶታል አምላክ ፣ ለብርሃን መውጫ !

ነፃነት ለሀገሬ ደግሞ አንዲህ ይለዋል:
ቴዲ እንደ ንጉስ ዳዊት ለብሶ ካባ፤
ከቀንዱ ቅዱሱን ቅባት የተቀባ፣
ጨለማን ሊያስወግድ የመጣ ያምላክ መባ፡፡

ለቴዲ አፍሮ ሰላማዊት አበባየሁ የፃፈችዉን ተደናቂ ግጥም ለመስማት እዚህ ይጫኑ
አሜን!
ሰይጣኖች እባካችሁን ቴዲን ለቀቅ አድርጉትአባካችሁ ተዉት ስራዉን ይስራበት !!!
ታላቁ የኢትዮጵያ የሙዚቃ ንጉስ ጥላሁን ገሠሠ አንደዚህ ብል ዘፍኖ ነበር “እረ ተዉኝ ባትነኩኝ ምናለበት” ሙዚቃዉን ለመስማት  እዝህ ይጫኑ
(ይህን የጥላሁንን ሙዚቃ ለቴዲ በክብርና በወንድምነት አቀርብለታለሁ።) 
እረ ተዉኝ ባትነኩኝ ምናለበት
አባካችሁ ሰዎች ስራዬን ልስራበት።

የሰው ሃሳብ አመረረ በተንኮል እየከረረ
ሰው ካልኖረ ስራ ሰርቶ
ባለው አቅሙ ዘር አምረቶ
በችሎታው በያለበት
ሰርቶ ቢኖር ምናለበት
ነገር ሲጭር ስራ አይሰራም
ሌላዉንም አያሰራም።

እረ ተዉኝ ባትነኩኝ ምናለበት
አባካችሁ ሰዎች ስራዬን ልስራበት ።

አምሮ በነገር ሰግዶ
በወሬ ከሆነ ኑሮ
ምን ሊሆን ነው ምን ሊጠቅም
በስራ ካልሆነ ጥቅም
ባቅሜ ሰርቼ ስራ
ለሀገር ጥቅም ላፈራ
ነው አንጂ የባከንኩኝ
ምን አለበት ባትነኩኝ።

እረ ተዉኝ ባትነኩኝ ምናለበት
አባካችሁ ሰዎች ስራዬን ልስራበት።

የተንኮል ምንጩ ይደፈን
ስራ ሰርተን መኖር አርፈን
ይሻለናል ስራ ስሩ
ምን ይገኛል ካፈሩ
ፍቅር  ሰላም ከኛ ጋራ
አስወጥተው ባላጋራ
አንደየአቅማችን ሰርተን
መኖሩ ነው የሚበጀን።

እረ ተዉኝ ባትነኩኝ ምናለበት
አባካችሁ ሰዎች ስራዬን ልስራበት።

የሕግ የበላይነትን ለወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ማስተማር እና መስበክ ማለት ለአሕዛብ መጽሐፍ ቅዱስን ማሰትማር መሞከር አንደማለት ነው። አለዝያም  በጥቁሩ ባልጩት ድንጋይ ላይ ውኃ እንደማፍሰስ ነው፡፡
አሁን ደግሞ ስለፍቅር፣ ስለይቅርታ አድራጊነት እና ስለዕርቀ ሰላም ለወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ማስተማር እና መስበክ ማለት ለጀርመን ብሄራዊ የሰራተኞች ሶሻሊስት ፓርቲ (ናዚዎች) አባላት ስለፍቅር፣ ስለይቅርታ አድራጊነት እና ስለዕርቀ ሰላም ማስተማር እና መስበክ እንደማለት ነው፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ እንዲያዳምጠኝ ጥያቄ ማቅረቤ አይደለም፡፡ ለዚህማ የሚያዳምጡበት ልቦና የላቸውም እንጅ ሁልጊዜ በየሳምንቱ ትምህርት እያቀረብሁ አይደለምን?
ለወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ጥያቄ የማቀርብላቸው ግን የቴዲ አፍሮን ሙዚቃ በጥሞና እንዲያዳምጡ ነው፡፡ በእውነት የእርሱን እውነተኛ ሙዚቃ፣ መሳጭ የሆኑ የግጥም ስንኞቹን እና መንፈስን የሚያድሰውን የድምጹን ቅላጼ ብያዳምጡ የመቀራረብን እና የፍቅር ስሜትን በተላበሱ ነበር፡፡
ከቴዲ ሙዚቃ በሚወጣው ፍቅር፣ እያንዳንዱ ቃሉ በክፋት የተሞላውን የግፈኞች አዕምሮ ወደ ስምምነት እና ፍቅር በመለወጥ፣ የእርሱ የሙዚቃ ምት የእነርሱን የልብ ምት በመምታት በፍቅር እንዲሸነፉ እና እጃቸውን እንዲሰጡ ያደርጋል፡፡
የእንግሊዝ የተውኔት ጸሐፊ እና ገጣሚ የነበሩት ዊሊያም ኮንግሬቭ እንዲህ በማለት ጽፈው ነበር፣ “ሙዚቃ ጨካኙን አውሬ ሩህሩህ የማድረግ፣ ጠንካራ አለቶችን የማለስለስ ወይም ደግሞ የተቋጠረ ጠንካራ የዋርካ ዛፍ ግንድን እንዲለነበጥ የማድረግ ኃይል አለው፡፡“
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ የቴዲ አፍሮን ሙዚቃ የሚያዳምጡ ከሆነ ሩህሩህ መንፈስን እንደሚላበሱ፣ የተዘጉ ልቦቻቸው ለስላሳ እንደሚሆኑ፣ አውሬያዊው ኋላቀር መንፈሳቸው የተረጋጋ እንደሚሆን እና የተቋጠሩት ልቦቻቸው ሊፈቱ እንደሚችሉ ምንም ዓይነት ጥርጣሬ የለኝም፡፡
የወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ የቴዲን ጣፋጭ የሙዚቃ ምግቦች በመመገብ እና በመሳተፍ ከእኛ ጋር ተቀላቀሉ፣ መንፈስ ይቀርባችኋል ከእኛ ጋር ሁኑ፡፡
በፖለቲካ፣ በሕግ ወይም ደግሞ በሰብአዊ መብት ጥበቃ ቋንቋ ከወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ጋር ለመነጋገር የሚታሰብ ነገር አይደለም፡፡
ሆኖም ግን ሙዚቃ የዓለም ህዝብ የመግባቢያ ቋንቋ ነው የሚለው እውነት ከሆነ በመጨረሻው ሰዓት በቴዲ አፍሮ ሙዚቃ አማካይነት ከወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ጋር መነጋገር እንችላለን ማለት ነው፡፡
በቴዴ  ያስተሰርያል በሚለው ፈዋሽ ድምጹ መሰረት ከወያኔ ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ ጋር መነጋገር እችላለሁ ብዬ አስባለሁ!
የወያኔ ወንድሞች! የቴዲን የፍቅር ሙዚቃዎች ለማዳመጥ ሞክሩ፣ በእርግጠኝነት አዳምጡ!
ከጥላቻችሁ በስተቀር የምታጡት ምንም ነገር የለም!
ሙዚቃ የፍቅር ምግብ ከሆነ ቴዲ እባክህን ዘምር፡፡ ደግመህ ደጋግመህ ተጫወት፣ ዘምር፡፡
ፍቅር ሁሉንም ያሸንፋል፡፡ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ)
አሜን!   
ቴዲ፣ እንወድሀለን፡፡ እናከብርሀለን፡፡ እናደንቅሀለን!!!
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!
ጳጉሜ 2 ቀን 2007 ዓ.ም