Friday 11 September 2015

አዲሱ አመት 2008 ዓ᎐ም የለውጥ አመት ይሆንልን !!!

          ቀን   11 09 2015
   በአብዩ ጌታቸው
 ከስታቫንገር ኖርዌ 
  
                                                                              
      ኢትዮጵያ ለብዙ አመታት ህዝቦቿ በባህል፣ በቋንቋ ፣ እና በእምነት እና በማህበራዊ ኑሮ ተከባብረውና ተስማምተው በአንድነት የሚኖሩባት ሃገር ናት፣ ሆኖም ግን በአሁኑ ወቅት ላለፉት 25 አመታት ስልጣን ላይ ያለው ወያኔ መራሹ የኢህዲግ ስርዓት ህዝቡን በተንኮል በመከፋፈልና አንዱ በአንዱ ላይ በመጥፎ እንዲነሳበት የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም ᎓᎓ በዘር በመከፋፈል በሃሰት ታሪክ በማስተማር ፣መፅሃፍ በማተም ፣አንዱን በዳይ ሌላው ተበዳይ አድርጎ  በሃሰት በመተረክ ፣ ባእዳንና ካድሬውን ባለ መሬት ሌላውን ባለአገሩን አገር አልባ በማድረግ ማፈናቀል፣ በብሔር እኩልነት ስም ዜጎችን በዘር በመከፋፈል መለያየት መግባባትና መመካከር እንዳይኖር ማድረግ፣ በክልል ከፋፍሎ ህዝቡ በመረጠው ክልል ምርታማ እንዳይሆን ማድረግ ፣በእምነቱ ተከባብሮና ተዋዶ  በሚኖረው ህዝብ መሃል ልዩነትና ግጭቶች እንዲኖር በመፍጠር አንድነታችንን እና ጥንካሬያችንን አናግቶ ስላጣንን  በአፈሙዝ ድጋፍ በማድረግ አገዛዙን ለማራዘም ሌት ከቀን ይጥራል᎓᎓

        የሃገራችንን ዋና ችግር  የስርዓት ችግር ነው ᎓᎓ ለዜጎች የሚጨነቅ ስርዓት በማጣታችን ነው የከፋ ችግር ላይ የወደቅነው ᎓᎓  ፍትህና ተጠያቂነት፣ ግልጽነትና የህዝብ የበላይነት የሰፈነበት ስርዓት ስለሌለን ነው ᎓᎓ እንደምናየው  በኢትዮጵያ  ያሉ ፍርድ ቤቶች ለገዢው ስርዓት የፖለቲካ መገልገያ  መሳሪያ ናቸው። መከላኪያው ፣ፖሊሱ፣ ባንኩ፣ ሚዲያው ሁሉ በስልጣን  ላይ ለተቀመጠው ከማጎብደድ ተላቆ በነፃነት፣ በህግና በሙያው አምኖ ለህዝብ ኣገልግሎት መስጠት ሲችል ነው ከገባንበት ችግር የምንወጣው።

       ህዝብ የመረጠው ስርዓት በሃገራችን በኢትዮጵያ እንዳይኖር የይምሰል ምርጫ በደረሰ ቁጥር ለተቀመጥኩበት ስልጣን ያሰጉኟል በማለት ህዝብን ጨቁኖ ለመግዛት በታቀደ በ "ሽብር ህግ " የሚታሰሩ ፣የሚታፈኑት እና የሚገደሉት የፓርቲ አመራር አባሎችና ግለሰቦች፣ እንዲሁም ህይወታቸውን ለማትረፍ የሚሰደዱ ጋዘጠኞችና ፖለቲከኞች ቁጥራቸው ብዙ ነው አገራችን  በጋዘጠኟ፣ በተቋዋሚ የፖለቲካ አመራሮችና እና አባሎች  እንዲሁም በጦማሪያን ማሰር በአለም ከመጀመሪያ ተርታዎች ስር ትገኟለች᎓᎓ በተጨማሪም ነፃ መፅሄቶች በሙሉ በሀገር ውስጥ እንዳይታተሙ እና ህዝቡ ስለሃገሩ በቂ እውቀት እንዳይኖረው ታግደዋል ᎓᎓


ስርዓቱ ስልጣኑን ለማረዘሚያ በነደፈው ‘የሽብር ህግ’ መሰረት በእምነት ውስጥ ጣልቃ በመግባት ፍፁም ሰላማዊ የሆኑ የሙስሊም ኢትዮጵያን የእስልምና ሀይማኖት መሪዎች ያለአግባብ ፍርድ  ለብዙ አመታት እስር ቤት አጎሮአል እስከ ሀያ ሁለት ዓመት በሚደርስ ተገቢ ያልሆነ እስራት ፈርዶባቸዋል᎓᎓  ለብዙ አመታት  በእምነት እና በማህበራዊ ኑሮ ተከባብረውና ተስማምተው በአንድነት  የሚኖሩትን  የኢትዮጵያን ክርስቲያንና ሙስሊሙን ህብረተሰብ ለማጋጨት የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም᎓᎓

            ስርዓቱ የሃገሪቱ አንጡራ ሃብት በጥቂት ግለሰቦች ስር እንዲመዘበር እና ፣ ስልጣንን ተገን በማድረግ  በኢትዮጵያ ህዝብ ስም በእርዳታ ስም የሚገኘው ገንዘብም ከሃገር እንዲሸሽ እያደረገ ነው አድርጎአታልም ᎓᎓ ኢትዮጵያ ከአፍካ  ከናይጄሪያ ቀጥላ የሃገርን ገንዘብ በማሸሽ ሁለተኛ ሃገር ናት  ᎓᎓ ሙስናም በሃገሪቷ ላይ ተንሰራፍቶ ምስኪኑ ህዝብ የበይ ተመልካች ሆናል ᎓᎓ የኑሮ ውድነትና ድህነት  የህዝባችንን አንገት አስደፍቶአል᎓᎓

   ስርዓቱ በጋንቤላ፣በቤሻንጉል፣እና በሌሎች በደቡብ ኢትዮጵያ ለህንድ፣ ለቻይ፣ለሳውዲ እና ለስርዓቱ አጎብዳጅ ካድሬዎች በኢንቬስትመንት ስም እና በዘር ፖለቲካ ህዝቡን በማተራመስ  ነዋሪውን እና ገበሬውን ከሚኖርበት እና የዕለት   ኑሮውን ለማሸነፍ ከሚያርስበት ቦታ አፈናቅሎ ለህይወት ማጣት ፣ ለረሃብና ለአገር ውስጥ ስደት በቅተዋል ᎓᎓አሁንም ችግሩ ተባብሶ እየሄደ ነው መጨረሻው ወደማያልቅ ችግር እያመራን ነውና በቃ ማለት አለብን !

      አገዛዙ በኢንቬስተምንት ስም የሚቃጠለው ወይም የሚመነጠረው ደን የአየር ማዛባት ማስከተሉን አለማስተዋል እንዲሁም በውስጡ የሚኖሩ የአገሪቷ ብርቅዮ እንስሳቶችን ሁንታን አላማጥናት እና በካድሬነትን የሚገኘውን የግል ጥቅም ከህዝብ እና ከሃገር በላይ ማፍቀር ሃገሪቷ ወደ ከፋ ችግር ውስጥ ከቷል᎓᎓ ችግሩ ለመደባበስ ሃገራችንን ከካሊፎኒያ ጋር ማወዳደር ትልቅም ቅሌት ነው ᎓᎓

      የአገዛዙ የትምህርት አሰጣጥ ፖሊሲው የፖለቲካው ትምህርት መስጫ ከመሆኑም አልፎ ተማሪው ተገቢውን የትምህርት አሰጣጥ ወይም እውቀት አግኝቶ የተሻለ ደረጃ እንዲደርስ ካለማድረጉ በተጨማሪ ተምሮም በተማረበትና በሰለጠነበት የሙያ ዘርፍ እንዳይሰማራ የተመቻቸ መንገድ ካለመኖሩ ለከፋ ችግር ተዳርጎአል᎓᎓ ወጣቱ ስደትን ተስፋው አድርጎ እንዲኖር ተደርጎአል ᎓᎓ ተሰዶም በሚደርስበት መከራና ኢሰብዓዊ ችግር  በአፋጣኝ የሚደርስለት መንግስት የለውም ᎓᎓ በሳውዲም ፣ በሊቢያ ፣ በደቡብ አፍሪካም  አይተነዋልና᎓᎓

     አገዛዙ ታሪካዊ ቦታዎች እና ቅርሶች እንዲጠፋ ዘወትር ይሰራል ለምሳሌ ዋልድባ ገዳም መመልከት ይቻላል  የሃገራችንን እምነት ባህል በክብር ይዘው የቆዩልን አባቶችን አፈናቅለዋል ቦታውንም በልማት ስም ይፈለጋል በማለት ወስደውታል᎓᎓ ዋልድባ ገዳም ታሪካዊ ፣ጥንታዊ ፣ ቅዱስ የፀሎት እና ሰዎች ከእግዚአብሄር ጋር የሚገናኙበት ቦታ ነው ፣ቦታውን ጠብቆ ለትውልድ የማስተላለፍ አላፊነቱ የማን ነው ? 

    ክልልን ለማስፋፋት፣ በጎንደር ፣በወልቃይትና በአፋር ህዝብ ላይ የሚደርሰው ግፍ ፣ በመሬት ጥያቄ የተነሳ በአምቦ ተማሪዎች ላይ የደረሰው ግድያ ፣ በኦጋዴን ህዝብ ላይ የሚደርሰው በደል እንዲሁም አገሪቷን በመቁረስ በሰሜን ምዕራብ፣ በምዕራብና በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ከ1600 ኪሎ ሜትር በላይ እርዝመት እና ከ30-60 ኪ/ሜትር የጎን ስፋት ያለውን ውሃ-ገብ ለም መሬቷ ተቆርሶ ለሱዳን ተሰቶአል፣ የአካባቢው ነዋሪም በኢሰብዓዊ  ሁኔታ እየተገደሉ እና  በጉልበትና በዘዴም እየተፈናቀሉም ነው ᎓᎓ 
ዝምታችን ሃገራችን ምን እስክትሆን ነው ?

       የወያኔ መራሹ አገዛዝ ጥፋቱ ዘርፈ ብዙ ነው ፣ ታዲያ ይህን አምባገነን አገዛዝ አፍርሶ በምትኩ ፍትሃዊ እና ዲሞክራሲያዊ ስርዓት  ለመገንባት ብንቀሳቀስ ምን ይለናል ? የሰላማዊ ስርዓት ለውጥን  በር ለዘጋ አምባገነን ምርጫችን የግድ የሃይል  አማራጭ ነው ᎓᎓

       ሃገራችን ከችግር እንድትወጣ ከተፈለገ የአቋም ቁርጠኝነትን ይጠይቃል። እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብቱ የተከበረበት፣ የኢኮኖሚ ብልፅግናና ማኅባራዊ ፍትህ የሚያገኙበት፣ የዜጎች ህይወት፣ ደህንነትና ጥቅም የተከበረበት ሃገር እንዲኖረው የሁላችንምም ትብብር እና አስተዋፅኦ ይጠይቃል።

       እናም ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በየትኟውም ስፍራ የሚገኝ ሁሉ ለነፃነትና ለዲሞክራሲ የሚደረገውን ትግል እውቀት ያለው በእውቀቱ፤ ጉልበት  ያለው በጉልበቱ፤ ገንዘብ ያለው በገንዘቡ ለመደገፍ ዛሬ ነገ ሳንል አሁኑኑ ከአርበኝነቱ ትግል መቀላቀል ይጠበቅብናል፡፡ ኢትዮጵያዊነታችንን ብቻ ሳይሆን ሰው መሆናችን የሚረጋገጠው ነፃነታችንን አስጠብቀን በነፃነት መኖር ስንችል ብቻ መሆኑ መዘንጋት የለበትም፡፡

     ስለዚህ ዛሬ የአገርን አድን ንቅናቄ  የለኮሰውን የነፃነት እና የአንድነት ቀንዲል ከነጻነት አደባባይ ለመትከል የጀመረውን ጉዞ በሰው ሀይል፤ በገንዘብና በቁሳቁስ በማገዝ አዲሱ አመት 
2008 ዓ᎐ም የለውጥ አመት ይሆንልን ዘንድ ሁላችንም የድርሻችንን እንድንወጣ ለእኛ ኢትዮጵያውያን ከእኛ ኢትዮጵ ያውያን ውጭ ማንም እንደሌለ ከመቼውም ግዜ በበለጠ በመገንዘብ ለተግባራዊ ስራ እንተባበር ፣ እንነሳ !


መልካም አዲስ ዓመት !


ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!!



No comments:

Post a Comment