Monday 2 March 2015

የይቅርታ ጀግናው እምዬ ዐፄ ምኒልክ፡- ቂም ቂምን እንጂ ዕርቀ ሰላምን አይወልድም !

በዲ/ን ተረፈ ወርቁ
ጽሑፌን እዚሁ በአገራችን የነገሥታት ታሪክ ዘመን በተፈጸመ አንድ አስደናቂ የዕርቀ ሰላም/የይቅር ባይነት ተምሳሌት በሆነ ታሪክ ልጀምር፡፡ በንጉሠ ነገሥት ዐፄ ዮሐንስ አራተኛ ሥር የነበሩት የሸዋው ንጉሥ ምኒልክና የጎጃሙ ንጉሥ ተክለ ሃይማኖት በ፲፰፻፸፬ ዓ.ም. ግንቦት ፴ ቀን በእምባቦ ሜዳ ላይ ከባድ ጦርነት እንዳደረጉ የታሪክ ድርሳናት ያወሳሉ፡፡ በንጉሥ ተ/ሃይማኖትና በንጉሥ ምኒልክ መካከል በገብር አልገብርምና ከግዛት ማስፋፋት ጋር ተያይዞ እነዚህ ሁለቱ ነገሥታት በእምባቦ ሜዳ ከሁለቱም በኩል በርካታ ሠራዊት የተሳተፈበትና እጅግ ደም ያፋሰሰ ጦርነት አካኺደው ነበር፡፡
በጦርነቱም የንጉሥ ምኒልክ ኃይል ስላየለ የንጉሥ ተ/ሃይማኖት ጦር የማታ ማታ ተፈታና ተሸነፈ፡፡ በጦርነቱም ንጉሥ ተ/ሃይማኖት ቆስለው ተማረኩ፡፡ ንጉሥ ምኒልክም ለተሸነፈው የጎጃም ሠራዊት ምሕረት አድርገው ዓባይን አሻግረው ሸኙት፡፡ ከንጉሤ አልለይም ያለውን የንጉሥ ተ/ሃይማኖት ሠራዊትን ደግሞ ምኒልክ ተከተለኝ ብለው ወደ መናገሻ ከተማቸው ወደ እንጦጦ ጉዞ ጀመሩ፡፡
ንጉሥ ምኒልክ ንጉሥ ተ/ሃይማኖትን በአልጋ አሸክመው ቀስ እያሉ ጉዞአቸውን ሰኔ ፭ ቀን ፲፰፻፸፬ ዓ.ም. ጀምረው ሰኔ ፲፱ ቀን እንጦጦ ደረሡ፡፡ ምኒልክም ምርኮኛውን ተ/ሃይማኖትን እንደ ወንድም እንጂ እንደ ባለጋራና ጠላት ሳያዩአቸው በወንድማዊ ፍቅር፣ ትሕትና እና ርኅራኄ ቁስላቸውን እያጠቡ፣ ሐኪም አስመጥተው በማሳከም፣ ጠቦት አርደው እየመገቡ እንዲድኑ አደረጉ፡፡
ንጉሥ ተ/ሃይማኖት ከዳኑም በኋላ አንድ ቀን ንጉሥ ምኒልክ ታላቅ ግብር አገቡ፡፡ በዚህ ንጉሥ ተ/ሃይማኖትና ወታደሮቻቸው፣ የሸዋ ታላላቅ መኳንንንትና መሳፍንት በታደሙበት ግብር ላይ ንጉሥ ምኒልክ ለንጉሥ ተ/ሃይማኖት አንድ ጥያቄ በቀልድ እያዋዙ አቀረቡላቸው፡፡ እንዲህ ሲሉ፡-
‹‹እኔ ማርኬ እንደዚህ አንቀባርሬ አስቀመጥኩህ፡፡ እንደው የሆነስ ሆነና አንተ ማርከኸኝ ቢሆን ኖሮ ምን ታደርገኝ ነበር?!›› ብለው ጠየቋቸው፡፡ የጎጃሙ ምርኮኛ ንጉሥ ተ/ሃይማኖትም፣ ‹‹ጌታዬ አያስዋሹኝማ … እኔማ ብሆን ኖሮ የማረኩዎ ቆራርጬ ነበር ለአሞራ የምጥልዎ!›› ብለው ሲመልሱ በግብር አዳራሹ ታላቅ ሳቅ ሆነ፡፡ ምኒልክም በመቀጠል፡- ‹‹ታዲያ የሚሻለው ያንተ ነው ወይስ የእኔ?!›› ቢሏቸው ‹‹ሲያሸነፉ ለተሸነፈ መራራት፣ ይቅርታ ማድረግ አግባብ ነው እንጂ ጌታዬ፡፡›› በማለት ንጉሥ ተ/ሃይማኖት የዐፄ ምኒልክን ርኅራኄና በጎ ተግባር ማወደሳቸው በታሪክ ድርሳናት ተጽፎ ይገኛል፡፡
ንጉሥ ተ/ሃይማኖት በምኒልክ ደግነትና ርኅራኄ በእጅጉ ተነክተው ነበር፡፡ እንደውም አንድ ቀን ዐፄ ምኒልክ ራሳቸው ምርኮኛውን ተ/ሃይማኖትን ቁስላቸውን ሲያጥቡላቸውና በፍቅር ሲንከባከቧቸው ሳለ ምርኮኛው ተ/ሃይማኖት ልባቸው እጅጉን ተነክቶ ‹‹የወጋዎ እኔን ቁስሌን እንዴት ያጥቡልኛል?! ምን ልበልዎ?!፣ ማን ብዬ ልጥራዎ፣ እንደው እምዬ ልበልዎን?!›› ብለው ማለታቸው ይነግርላቸዋል፡፡
ይህን የታሪክ ሐቅ ይዘን በእኛ ዘመን ትናንትና አገራችንን ባስተዳደሩ ነገሥታቶቻችንና ገዢዎቻችን ዙሪያ በመረጃ አልባ ዕውቀትና ለምን በሚል ድጋፍና በጭፍን ጥላቻ ጎራ ለይተው በታሪክ ላይ ለፍርድ ዳኝነት ለተሰየሙና የትናንትናውን ክፉ ታሪክ በበቀል ለመድገም ለሚፈልጉ ወገኖቻችን ሁሉ ከቂምና ጥላቻ ይልቅ የሚበጀን ፍቅር፣ ዕርቅና ሰላም መሆኑን ልገልጽላቸው እወዳለሁ፡፡
በመግቢያዬ ባነሳሁት እውነተኛ ታሪክ ላይ ተመርኩዤም በዕርቅ፣ ሰላምና መግባባት ጉዳይ ላይ ጥቂት ነገሮችን ለማለት እወዳለኹ፡፡ ዛሬ ዛሬ ስለ ዐፄ ምኒልክም ሆነ ስለ ሌሎች ነገሥታትና ገዢዎች ታሪክ ሲነገር መቶና ሁለት መቶ ዓመት ወደኋላ ተጉዘው ትናንትን ዛሬ ላይ ሆነው ለመዳኘት የሚፈልጉ ሰዎች ከቀን ወደ ቀን መበራከታቸውን እየታዘብን ነው፡፡
ይህ ከገጠር እስከ ከተማ፣ አልፎም በባሕር ማዶ አፍሪካ፣ አሜሪካና አውሮፓ ድረስ የዘለቀው ዘርን፣ ጎሳን፣ ቋንቋንና የትናንትና ታሪካችንን መሠረት ያደረገው የጥላቻና የቂም በቀል ዘመቻ እንደ ሰደድ እሳት እየተስፋፋና ብዙዎችን እያጠመቀ እንዳለም እያየን ነው፡፡ ባለፈው ሰሞንም በዚሁ በዕንቁ መጽሔት ላይ ቴዲ አፍሮ ዐፄ ምኒልክን በተመለከተ በሰጠው ቃለ መጠይቅ የተነሳ በማኅበራዊ ድረ ገጾች ሲነሡና ሲሰጡ የነበሩ የተለያዩ ትንታኔዎችንና አስተያየቶችን ለታዘበ ከሰላም፣ ፍቅርና ከዕርቅ ይልቅ ምን ያህል ክፋት፣ ቂምና ጥላቻ ልባችንን እንደሞላው ያጋለጠ ነው ማለት የሚቻል ይመስለኛል፡፡
እነዚሁ በዘመናችን የዐፄ ምኒልክን ታሪክ አጠልሽተው፣ ሰብእናቸውንም አርክሰው፣ ፍጹም አረመኔ፣ ጨካኝና ጭራቅ አድርገው የሚፈርጁና በተቃራኒው ደግሞ እኚህን ንጉሥ ፍጹም የማይሳሳቱ፣ ቅዱስ መልአክ አድርገው በመሳል ምን ሲደረግ ስለ እምዬ ምኒልክ ክፉነታቸው ይነገራል በሚሉ ጎራዎች መካከል ጽንፍ ይዞ፣ ቁጣንና ቂምን አርግዞ የቀጠለውን ሙግት እና እሰጥ አገባ እየተሳቀቅንና እንደ አገርም ሆነ እንደ ሕዝብ የነገ ዕጣ ፈንታችን እያሳሰብንና እያሰፈራን በነጋ ጠባ እየተከታተልን ነው፡፡
ስለ ዐፄ ምኒልክ ሲነሳ ክፉ ክፉ ታሪካቸው ብቻ እንዲነገርና በአንጻሩም ደግሞ ስለ ንጉሡ ደግ ደጉ ታሪካቸው ብቻ እንጂ ሌላው ሌላው እንዳይነገርባቸው የሚፈልጉ ሰዎች ቆም ብለው በትናንትና ታሪካችን ላይ ያላቸውን አተያይና አቋም በቅጡ ሊፈትሹ ይገባቸዋል፡፡ በነጋ ጠባ የብሔር ፖለቲካን የሚሰብከውና ለተግባራዊነቱም ተግቶ እየሠራ የሚገኘው የኢሕአዴግ መንግሥትም እጅግ በሚያሳፍር ኹኔታ በዚህ ዓመት በተከበረው የዐድዋ በዓል ላይ የዐፄ ምኒልክ ፎቶ በዐድዋ ተራራ ላይ እንዳይኖር አድርጓል፡፡
ይህ አሳፋሪና ትልቅ የታሪክ ቅሌት ነው፡፡ ከአፍሪካ እስከ አሜሪካ፣ ከሩሲያ እስከ ቻይና፣ ከአውሮፓ እስከ አውስትራሊያ ታላቅ አፍሪካዊ ሰው፣ ጥቁር ጀግና፣ የኢትዮጵያን ዘመናዊ ልደት አብሳሪ በሚል የሚሞካሽቱንና በጠላቶቻቸው በኢጣሊያኖቹ ሳይቀር ቪቫ ምኒልክ ተብሎ የተዘመረላቸውን ዐፄ ምኒልክን አንድ የታሪክ ሰበዝ ብቻ መዞ በማውጣት ግዙፍና ገናና ታሪካቸውን መጠልሸት ራስን ከማዋረድና ከማስነቀፍ የዘለለ ሌላ ምንም ፋይዳ ሊኖረው አይችልም፡፡ እንዲሁም ደግሞ ትናንትናን በዛሬ ላይ ሆኖ መዳኘትና ፍርድ መስጠት በታሪክ ጥናት ሙያ ትልቅ ስህተት ከመሆኑም በላይ ሕሊናን የሚሞግት ትልቅ የሆነ ሞራላዊ ጥያቄ እንደሚያስነሳ ልብ ሊሉት ይገባቸዋል፡፡
እዚህ ጋር የ፳ኛው መቶ ክ/ዘመን ኢትዮጵያዊው ምሁር ፖለቲካል ኢኮኖሚስቱ ነጋድራስ ገ/ሕይወት ባይከዳኝ የታሪክ አጻጻፍንና አተያይን በተመለከተ የተናገረውን ምክር ለእነዚህ ወገኖቻችን ልጠቅስላቸው እወዳለሁ፡- ‹‹ትናንትና የሆነውን ታሪክ ለመጻፍና በአግባቡ ለመረዳት ንጹሕ ልብ፣ ሚዛናዊ የሆነ ከዘረኝነትና ከወገተኝነት የጸዳ በጎ ሕሊና›› እንዲኖረን ግድ ይላል፡፡
አለበለዚያ ግን አሁን በያዝነው ሸካራ መንገድ ዐፄ ምኒልክን ሰይጣን፣ የሰይጣን ቁራጭ በተቃራኒው ደግሞ ንጉሡን ፈጽመው የማይሳሳቱ ቅዱስ መልአክ አድርገው በመሣል ጎራ ለይተው የቃላት ጦርነት እየተወራወሩ ባሉ ሰዎች መካከል መቼም ቢሆን መስማማት ሊኖር እንደማይችል ከመቼውም ጊዜ በላይ ግልጽ እየሆነ እየመጣ ያለ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የትናንትና ታሪካችንን እያየንበት፣ እየፈተሸንበት ያለው መነፅር የተበላሸና የጠራ ያለመሆኑ ጉዳይ ነው፡፡
እናም በዚህ አካኼድ ወደ ሌላ የከፋ የጥላቻ፣ የቂም በቀልና የእልቂት ታሪክ ምዕራፍ ከመሻገራችን በፊት እነዚህን ጽንፍ የያዙ ጎራዎችን አቀራርበው ከመጠፋፋትና ከእርስ በርስ እልቂት ሊታደጉ የሚችሉ ለአገርና ለወገን የሚቆረቆሩ እውነተኛ የሰላምና የዕርቅ ሰባኪዎች በእጅጉ ያስፈልጉናል፡፡
በዚህ ረገድም የሃይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ ምሁራን፣ የመገናኛ ብዙኃን ባለ ሙያዎች ከመቼውም ጊዜ በላይ ለዕርቅና ለሰላም ድምፃቸው ከፍ ብሎ እንዲሰማ ያስፈልጋል፡፡ ትውልዱ ከገባበትና እየነጎደበት ካለው የዘረኝነት፣ የትምክህተኝነትና የቂም በቀል አዙሪት ታድገው የነገውን የአገሩን ሰላም፣ አንድነትና የዕድገት ብሩህ ተስፋዋን ባሻገር ወደሚያይበት የፍቅር፣ የሰላምና የዕርቅ ተራራ ይዘውት የሚወጡ እንደ ማንዴላ ያሉ ከልባቸው ሰው የሆኑ የዕርቅና የሰላም ጀግኖች በእጅጉ ያስፈልጉናል፡፡
በመጨረሻም ለዚህ ጽሑፌ በመግቢያነት የተጠቀምኩበት ይህ የትናንትና የታሪካችን አካል የሚነግረን እውነታ ቢኖር ይቅር ባይነት የበቀልን መንፈስ አጥፍቶ ዕርቀ ሰላምን እንደሚያሰፍን ነው፡፡ ዐፄ ምኒልክ ጠላታቸውና ተፋላሚያቸው ለሆኑት ለምርኮኛው ንጉሥ ተ/ሃይማኖት ከልባቸው ይቅርታ በማድረጋቸው በግዛታቸውና በሕዝቦች መካከል ዕርቅና ሰላም እንዲወርድ አድርጓል፡፡ ያም ብቻ ሳይሆን ዐፄ ምኒልክ ወንድማዊ የሆነ ፍቅራቸውንና ይቅርታቸውን ያለ ስስት ባላጋራቸው ለሆኑት ሰው በማካፈል የጥላቻና የቂም በቀል ዐርም እንዲነቀል ታላቅ የሆነ የፍቅር መሥዋዕትነትን ከፍለዋል፡፡
እንዲህ ዓይነቱ የሰላምና የዕርቅ መንፈስ በዘር፣ በቋንቋና እነርሱና እኛ በሚል ፈሊጥ ለተከፋፈለው ሕዝባችን፣ ጽንፈኝነትና ጥላቻ ክፉኛ እየናጠው ባለው የአገራችን የፖለቲካ ትኩሳት ወላፈን ምክንያት በተለያዩት የሃይማኖት አባቶች፣ በመንግሥት፣ በተቃዋሚ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች መካከልም እንዲመጣ ሁላችንም የበኩላችንን ድርሻ መወጣት ያስፈልገናል፡፡
ባለፈው ታሪካችን ላይ በስሜት ሳይሆን በእውቀት፣ በቅንነትና በጨዋነት በመነጋገር/በመወያየት ለመቀራረብና ለመግባባት የሚያስችለንን መንገዱን ማስተካከል እንጂ ቂም በቀልን መስበክ ሌላ ቂምንና ጥላቻን እንጂ ሰላምንና ዕርቅን አያመጣም፡፡ የጋራ አገራችን ለሆነች ኢትዮጵያና ሕዝቧ ሰላም፣ ልማት፣ ዕድገትና ብልጽግናም የሚበጀውና የሚያዋጣውም ይኸው የዕርቅና የሰላም መንገድ ብቻ ነው!!

No comments:

Post a Comment