Friday 27 March 2015

የአዋሳ ፖሊስ የሰማያዊ ፓርቲ የቅስቀሳ ቁሳቁሶችን ቀማ

• ‹‹የባጃጅ ሾፌሮችን አድማ የመራው ሰማያዊ ነው›› ባለስልጣናቱ
የአዋሳ ፖሊስ መጋቢት 20/2007 ዓ.ም ለሚደረገው ሰልፍ የተዘጋጁትን የሰማያዊ ፓርቲ የቅስቀሳ ቁሳቁሶች መቀማቱን በአዋሳ ከተማ የሰልፉ አስተባባሪ አቶ ዮናስ ከድር ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጾአል፡፡ ከአዲስ አበባ ሰልፉን ለማስተባበር ወደ አዋሳ ያቀኑት የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች አዋሳ በደረሱበት ወቅት የፀጥታ ኃላፊው እና የከንቲባው አማካሪ አስተባባሪዎቹን አስጠርተው በሚያወያዩበት ወቅት ፖሊስ የቅስቀሳ ቁሳቁሶችን ከተቀመጡበት ቦታ ቀምቶ እንደወሰደ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የአዋሳ ከተማ የፀጥታ ኃላፊ እና የከንቲባው አማካሪ የሰልፉን አስተባባሪዎች በመጥራት ‹‹በከተማችን በሚገኙ አደባባዮች ባዛሮች አሉ፡፡ በተጨማሪም ለህዳሴው ግድብ ከ18-30 የህዝባዊ ስብሰባዊና ህዝባዊ ንቅናቄዎች ይደረጋሉ፡፡ በዚህም ምክንያት የፀጥታ ኃይል ስለሌለን እስከ መጋቢት 30 ድረስ ሰልፍ ማድረግ አትችሉም፡፡›› እንዳሏቸው ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

የሰልፉ አስተባባሪዎች ከከተማው ባለስልጣናት ጋር በሚወያዩበት ወቅት ፖሊስ ቲሸርትና በረሪ ወረቀቶች ቀምቶ የወሰደ ሲሆን ቁሳቁሶቹ አሁንም ድረስ በፖሊስ እጅ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡ ሆኖም ፖሊስ ‹‹እቃ አልወሰድንም፣ የምናውቀን ነገር የለም›› ብሎ እንደካዳቸው አስተባባሪዎቹ ገልጸዋል፡፡

በተመሳሳይ ዜና በሲዳማ ዞን ቡርች ወረዳ የደህኢዴን /ኢህአዴግ ካድሬዎች ህዝቡ እሁድ በሚደረገው ሰላማዊ ሰልፍ እንዳይወጣ በሜጋ ፎን እየቀሰቀሱ መሆኑን የሰልፉ አስተባባሪዎች ገልጸዋል፡፡ ካድሬዎቹ ‹‹በእሁዱ ሰልፍ የወጣ ሰው ይታሰራል›› እያሉ እንደቀሰቀሱም ለማወቅ ተችሏል፡፡

በሌላ ዜና በአዋሳ ከተማ የተከሰተውን የነዳጅ እጥረትና የዋጋ ታሪፍ ተከትሎ ትናንት መጋቢት 17/2007 ዓ.ም የባጃጅ ሾፌሮች የሥራ ማቆም አድማ ያደረጉ ሲሆን የከተማው ባለስልጣናት አድማውን የመራው ሰማያዊ ፓርቲ ነው የሚል ውንጀላ እያቀረቡ መሆኑን የሰልፉ አስተባባሪዎች ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡

‹‹የአዋሳ ፖሊስ ለእሁዱ ሰልፍ የተዘጋጁትን የቅስቀሳ ቁሳቁሶች በመቀማት እና የተለያዩ ወከባዎችን በመፍጠር
ሰልፉን ለማደናቀፍ እየሰራ ቢሆንም እኛ ህጋዊ ግዴታችን ተወጥተናል፡፡ በመሆኑ ሰልፉ በታቀደለት ወቅት
ይካሄዳል›› ሲሉ የሰልፉ አስተባባሪዎች ገልጸዋል፡፡

No comments:

Post a Comment