Wednesday 28 January 2015

የዞን9 የጦማርያን እና ጋዜጠኞች ችሎት ላይ ክሱ ተሻሻሏል ሲል "ፍርድ ቤቱ" ወሰነ


ሰበር ዜና -----ክሱ ተሻሻሏል ሲል "ፍርድ ቤቱ" ወሰነ 


ለስድስት ወራት የክሱን ፎርማት ይዘትና ህጋዊ መሰረት ሲያጠና የከረመው "ፍርድ ቤት" ክሱ ተሻሽሏል የሚል ብያኔውን ዛሬ በተደረገው 16ተኛ የዞን9 የጦማርያን እና ጋዜጠኞች ችሎት ላይ በንባብ አሰምቷል ፡፡

አንዲሻሻሉ ከታዘዙት አራት ነጥቦች መካከል ሶስቱ መሻሻላቸውን አይቻለሁ ያለው "ፍርድ ቤቱ "

1. ቡድን በሚል የተጠቀሰው ተከሳሾቹ ያቋቋሙት የህቡህ ቡድን አንደሆነ ፍርድ ቤቱ ተረድቷል ቡድኑ ዝርዝር ሁኔታ በማስረጃ መስማት ወቅት ተቀባይነት ሊኖረው ወይም ደግሞ ውድቅ ሊሆን የሚችል ስለሆነ ክሱ ውስጥ መካተት አለበት ሲል ወስኗል ፡፡

2. ስልጠናን አስመልክቶ ‹‹ተከሳሾች ከ2004 ጀምሮ እጃቸው እስከተያዘበት ጊዜ ድረስ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት በግንቦት 7 አመቻችነት ስልጠና መውሰዳቸውን የተሻሻለው ክስ አስፍሯል፡፡ ስለሆነም ጊዜውና በማን የሚለው ስለተጠቀሰ ክሱ መሻሻሉን ፍርድ ቤቱ ተቀብያለው ብሏል፡፡

3. ለሽብር ተግባር ዋለ የተባለውን 48.000 ብር አስመልክቶ ክሱ ውጨ አገር የሚገኙ የቡድኑ አባላት ናቸው በሚል ስለሚያብራራው ተቀባይነት አግኝቷል ያለ ሲሆን ስራ ክፍፍልን አስመልክቶ በቂ ዝርዝር ባለመቀረቡ ከስራ ክፍፍል ፍሬ ነገር ውጪ ያሉት የክሱ ፍሬ ነገሮች ተካተው ተከሳሾች የእምነት ክህደት ቃላቸውን ለመስጠት ዝግጁ መሆን አለመሆናቸውን ፍርድ ቤቱ ጠይቋል፡፡


በተከሳሾች ጠበቃ የፍርድ ቤቱ የሶስቱን ፍሬ ነገሮችን መቀበል ያልተጠበቀ መሆኑን ገልጸው ከደንበኞቻቸው ጋር ለመመካከር ጊዜ ጠይቀዋል ፡፡ በዚህም መሰረት ችሎቱ ለከሰአት 8.00 በድጋሚ ተቀጥሮ የጠዋቱ ችሎት ተጠናቋል፡፡

በፍርድ ቤቱ ውሳኔ ብዙም ያልተገረሙት ተከሳሾች ወንዶቹ የምሳ እረፍታቸውን በልደታ ፍርድ ቤት ውስጥ ሲያሳልፉ፣ ሴቶቹ ወደ ቃሊቲ ተመልሰዋል፡። በጠንካራ መንፈስ ላይ የነበሩት እስረኞች ብይኑ በችሎት ሲሰማ ከፈገግታ እና ሳቅ ባለፈ ምንም አይነት መደናገጥ አልታየባቸውም ፡። በቆይታቸውም እርስ በርሳቸው ሲያወሩ ሲወያዬ እና ወዳጅ ዘመዶችን ሰላም ሲሉ ተስተውለዋል፡፡

በከሰአቱ ችሎት በቂ የመወያያ ግዜ ለማግኘት ስላልተቻለ ጠበቃ አምሃ አጭር ቀጠሮ በመጠየቃቸው ችሎቱ ለሚቀጥለው ማክሰኞ ለጥር 28 ተቀጥሮ ተጠናቋል፡፡

ማስታወሻ

የዞን9 ጦማርያን ፍርድ ቤቱ እድሉን ተጠቅሞ የፍትህ ስርአቱን ነጻነት የሚያረጋግጥበትን ወርቃማ እድል አንዲጠቀም ደጋግመን መጠየቃችን ይታወሳል፡፡ ከማስረጃው 90 በመቶው ጦማራችን ላይ የወጡ ጽሁፎች በመሆናቸው ክሱ ሃሳባቸንን በነጻነት በመግለጻችን ብቻ የተቀናበረ ፓለቲካዊ ክስ መሆኑን ግልጽ ያደርገዋል ፡፡ አሁንም አልረፈደምና ዞን9 ጦማርያንን እና ጋዜጠኞችን በነጻ በማሰናበት የፍትህ ስርአቱ ራሱን እንደቁምነገር የሚያስቆጥርበትን እድል አንዲጠቀም ደግመን እናሳስባለን፡፡ የፍትህ ስርአቱ መስተካከል ከጦማርያኑ እና ጋዜጠኛ ወዳጆቻችን ከታሰሩለት አገራዊ አጀንዳ አንዱ ነውና !

No comments:

Post a Comment