Tuesday 6 January 2015

የአንደርጋቸው ፅጌ አስገራሚ መልዕክት ከማይታወቀው እስር ቤት

Image
በኢትዮጲያ ቴሌቪዥን በፖሊስ ፕሮግራም ላይ viewtopic.php?f=2&t=91626 ተቆርጦ ተቀጥሎ የተላለፈው የአንዳርጋቸው ፅጌ ድንቅ የትግል ጥሪ መልዕክት ለሊቱን ሙሉ ሲደንቀኝ ነው ያደረው፡፡ ኢቲቪ በነካካ እጇ ያልተቆራረጠውን ሙሉ ቪዲዮ ደግሞ ብትለቅልን እንዴት ሸጋ ነበር፡፡
አንዳርጋቸው ፅጌ በተቆራረጠው ቪዲዮም ውስጥ እንኳን ያስተላለፋቸው 3 መልዕክቶች ድንቅ ናቸው፡፡ ሙሉውን ንግግሩን ፅፌ እለጥፈዋለሁ፡፡ እስከዛው ግን መልዕክቶቹ እነኚህ ናቸው፡-
1ኛ፡- ለወጣቱ የተላለፈ የትግል ጥሪ፡- ወጣቱ የሴት ጓደኛውን ቀጥሮ ሸሚዙን ሲያስተካክል መዋል ሆኗል ስራው፡፡ እንዴት አድርጎ ከኢትዮጲያ እንደሚወጣ እና ደቡብ አፍሪካ ወይም አሜሪካ እንደሚገባ ብቻ ነው የሚያስበው፡፡ ወደ ፖለቲካው የሚመጣው ወጣት ቁጥር እጅግ አናሳ ነው፡፡ ተፒለፍ እና ኢህአፓ ጊዜ የነበረው ፖለቲካ በትምህርታቸው ጎበዝ የነበሩ ተማሪዎችን ሳይቀር ነበር የሚስበው፡፡ አሁን ግን የፊልም አክተር እና ዘፋኞች የሚኖሩበትን ቤት በፊልም እያየ በምኞት ብቻ የሚኖር ወይም እንዲህ አይነት ቤቶች ወዳሉበት አካባቢ ለመሰደድ የሚፈልግ ወጣት ነው ያለው፡፡ በሚል አንዳርጋቸው ወጣቱ ካረፈበት የእንቅልፍ አዚም እንዲላቀቅ እና ለትግል እና ለመደራጀት እንዲዘጋጅ ያስተላለፈው መልዕክት ነው፡፡
2ኛ፡- የተባበረ ትግል ጥሪ፡- አንዳርጋቸው ይህንን ጥሪ ያስተላለፈው ለሶስት አካላቶች ነው፡፡ አንደኛ የኦሮሞ የአማራ እና የደቡብ ኤሊቶች ልዩነታቸውን አጥብበው በህብረት እንዲሰሩ የጠየቀበት፡፡ ሁለተኛ በውጭ ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶች 5 እና 20 እየሆኑ ለየብቻቸው የሚያደርጉትንና እንደ አንዳርጋቸው አገላለፅ ‹‹ዩኒቲ ኦፍ ፐርፐዝ›› የሌለበትን ትግል እንዲተው የተናገረበት እና ሶስተኛ ደግሞ በሀገር ውስጥ የሚገኙ ዘጠና ፓርቲዎች 1500 ፊርማ ብቻ እያሰባሰቡ እዚህ እና እዚያ የፈሉበትን ሁናቴ የተቃወመበት ነው፡፡
3ኛ፡- ምርጫ ቀልድ መሆኑን ያጋለጠበት መልዕክት፡- መንግስት ግልፅነት ያለው አሰራር ሳይከተል ተቃዋሚዎች እንዴት ብለው ነው የምርጫ ማኒፌስቷቸውን ማዘጋጀት የሚችሉት የሚል ጥያቄ በቪዲዮው ላይ ሲጠይቅ የሚሰማው አንዳርጋቸው ፅጌ ቃል በቃል ‹‹ምርጫው ቀልድ ነው›› ሲልም ይደመጣል፡፡
ሌላው በዚህ ቪዲዮ ላይ ያስተዋልኩት ነገር ከ 6 ደቂቃ ከ 55 ሰከንድ እስከ 7ኛው ደቂቃ ከ 4 ሰከንድ ድረስ እጅግ በጣም ሳግ በተናነቀው እና በተጎዳ ድምፅ ‹‹ከዚህ በኋላ ያለው ነገር የበለጠ ቀውስ እና የበለጠ ኪሳራ በሀገሪቷ እና በህዝቧ ላይ የሚያደርስ ነገር ነው የሚል ዕምነት ነው ያለን›› የሚለው ንግግሩ ነው፡፡ ምኑ ነው የበለጠ ቀውስ እና ኪሳራ ያመጣል ያለው ነገር; ምናልባት ኢቲቪ ትጥቅ ትግሉ የበለጠ ኪሳራ ያመጣል እያለ ነው የሚል ምስል በተመልካች ዘንድ ለመፍጠር አሳባ ነው; ያም ቢሆን ደግሞ ትጥቅ ትግሉ የበለጠ ቀውስ እና ኪሳራ ያመጣል ሲል ማሰማት ነበረባት፡፡ እኔ ግን ሲመስለኝ የበለጠ ቀውስ እና ኪሳራ የሚያመጣ ያለው ምርጫውን እና አሁን ያለውን ስርአት ነው፡፡ ይህን ያልኩበት ምክንያትም በንግግሩ መጨረሻ ላይ የበለጠ ቀውስ እና ኪሳራ የሚያደርስ ነው የሚል እምነት ነው ‹‹ያለኝ›› ሳይሆን የሚለው ‹‹ያለን›› ነው የሚለው፡፡ ይህ ማለት የአንድን ቡድን አቋም እየገለፀ እንዳለ ግልፅ ነው፡፡ በቡድን ደረጃ ያውም አንዳርጋቸው ‹‹እኛ›› እያለ የሚያወራለት ቡድን ደግሞ ስለ ትጥቅ ትግሉ እንዲህ አይነት አቋም እንደሌለው ግልፅ ነው፡፡
በመጨረሻም ቪዲዮውን ደግሜ ደጋግሜ ካየሁት በኋላ የገባኝ ነገር ቢኖር አንዳርጋቸው ባገኛት ትንሽ ቀዳዳም ቢሆን መልዕክቱን ማስተላለፉን እና ምናልባትም ይህ መልዕክት በቴሌቪዥን እንዲሰራጭ ያደረጉት ሰዎች የውስጥ አርበኛ ሊሆኑ እንደሚችሉ ነው፡፡

No comments:

Post a Comment