Friday 27 February 2015

በአዋሳ በደረሰው የእሳት ቃጠሎ የሟቾች ቁጥር ከ20 በላይ ነው ሲሉ የቃጠለው ሰለባ የሆኑ ሰዎች ገለጹ


የካቲት ፳(ሃያ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በደቡብ ክልል ዋና ከተማ በአዋሳ የካቲት 14 ቀን 2007 ዓም በደረሰው ከፍተኛ 
የእሳት ቃጠሎ የሟቾች ቁጥር በመንግስት እንደተገለጸው አንድ ሳይሆን ከ20 በላይ መሆኑን ተገጂዎች ለኢሳት ገልጸዋል።

ከፍተኛ ንብረት ከወደመባቸውና እሳቱ ሲነሳ በስፍራው ከነበሩት መካከል አንዱ ለኢሳት ሲናገር፣ እርሱ የ6 ሰዎችን የተቃጠለ 
አስከሬን ማየቱን፣ በስፍራው የሚገኙ ጓደኞቹ ደግሞ በአጠቃላይ እስካሁን 27 አስከሬን ተፈልጎ መቀበሩን ተናገሩዋል።

አንድ ህጻነት እና አንዲት እናት ከ3 ልጆቿ ጋር ሞታ መመልከቱን፣ በማግስቱ ደግሞ ተጨማሪ ሁለት ሰዎች ሞተው ማየቱን 
የሚናገረው ግለሰቡ፣ የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች አካባቢውን ከነዋሪው በመከለል ማታ ማታ የተቃጠለ አስከሬን እየፈለጉ 
በመቅበር ላይ ናቸው ብሎአል። እናቶች አሁንም ድረስ ልጆቻቸውን እየጠየቁ ቢሆንም፣ በከንቲባው በኩል የሚሰጠው ምላሽ 
አሳዛኝ መሆኑን ግለሰቡ ገልጿል። ነዋሪዎቹ በመንግስት በኩል በቂ እርዳታ እንዳልተደረገላቸው በምሬት ተናግረዋል።

መንግስት የእሳቱን መነሻ እስካሁን ይፋ አላደረገም። ነዋሪዎች እንደሚሉት ግን መስተዳድሩ ቦታውን ለመሸጥ እሳቱን ሆን ብሎ 
አስነስቶታል። 
በጉዳዩ ዙሪያ የአዋሳን ከንቲባ ለማግኘት ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ አልተሳካም።

No comments:

Post a Comment