Thursday 19 February 2015

‹‹ታሪክ አጥፍተን ታሪክ አንሠራም››

የቤተክርስቲያን ነዋየ -ቅድሳት ለዓባይ ግድብ ተብሎ መሰጠቱ ተዘገበ

የካቲት ፲፪ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ሪፖርተር ጋዜጣ እንደዘገበው በእንጦጦ ማርያም ሙዚየም የወርቅ መስቀሎች ጠፍተዋል መባሉ በምእመናን ዘንድ  ተቃውሞ አስነስቷል።
ለርዕሰ አድባራት እንጦጦ መንበረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን፣ ከተለያዩ ምዕመናን በስለትና በስጦታ የተሰጡና እስከ አራት ኪሎ ግራም ሊመዝኑ ይችላሉ የተባሉ ሁለት የወርቅ መስቀሎችና አንድ የወርቅ ሐብል፣ በቅርስነት ከተቀመጡበት ሙዚየም ውሰጥ መጥፋታቸውን የደብሩ ካህናትና የአካባቢው ነዋሪዎች ገልጸዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያኗ ካህናት፣ ሠራተኞችና የአካባቢው ነዋሪዎች-በጋራ በመሆን  የደብሩ አስተዳዳሪና ሌሎች ኃላፊዎች ተባብረው ወርቆቹን ማጥፋታቸውን በመግለጽ ተቃውሟቸውን በፊርማ አስደግፈው  ለመንበረ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት፣ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽሕፈት ቤት፣ ለሀገረ ስብከቱ ቅርሳ ቅርስ ክፍል፣ ለአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮና ለጉለሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምርያ በፊርማ  አስገብተዋል፡፡
የደብሩ ካህናት፣ የተለያዩ ሠራተኞችና የአካባቢው ነዋሪዎች እንደገለጹት፣ በቤተ ክርስቲያኗ የቅርስ ማስቀመጫ ሙዚየም ውስጥ፤ የአፄ ምኒልክ የወርቅ ጫማ፣ የእቴጌ ጣይቱ ብጡል የተለያዩ አልባሳት፣ አልጋና  በተለያዩ ምክንያቶች ለቤተ ክርስቲያኗ የገቡ በርካታ  የወርቅ፣ የብር፣ የነሐስ፣ የተለያዩ ቅርፃ ቅርፆችና ቅርሶች ይገኛሉ፡፡
በማንና በምን ሁኔታ እንደተወሰዱ ባይታወቅም፣ በቱሪስቶች በመጎብኘትም ከፍተኛ ገቢ ሲያስገኙ ከቆዩት  ከእነኚህ ቅርሶች መካከል  ጥቂት የማይባሉ ቅርሶች መጥፋታቸውን ካህናቱ ተናግረዋል።
የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳዳሪ መልዓከ ፀሐይ ቆሞስ አባ ገብረኢየሱስ መኮንን ጥቅምት 21 ቀን 2007 ዓ.ም. ለሙዚየሙ ቁልፍ ያዥ ለመምሬ አስፋው ገብረ ማርያም  በጻፉት ደብዳቤ ፦ በቅርሶች መመዝገቢያ (መረካከቢያ) ቁጥር 170 ላይ የሚገኙትን ሁለት የወርቅ መስቀሎችና አንድ የአንገት ወርቅ ሐብል  ወጪ አድርገው ለሊቀ ህሩያን ቃለጽድቅ ኃይሌ እንዲሰጡ  ትእዛዝ ማስተላለፋቸው ተመልክቷል፡፡
ከቅርስ ማስቀመጫ ሙዚየሙ ወጥተዋል የተባሉት ወርቆች የት እንደደረሱ ባለመታወቁ ካህናቱ፣ ሠራተኞቹና ምዕመናን ግራ ተጋብተው ባለበት ሁኔታ፣ አስተዳዳሪው  መልዓከ ጸሀይ ታኅሳስ 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ሠራተኞችን ሰብስበው ለዓባይ ህዳሴ ግድብ ቦንድ ለመግዛት በሙዚየሙ ውስጥ ያሉ ወርቆች መሸጥ እንዳለባቸው ሐሳብ ማቅረባቸውን  ሰራተኞቹ ተናግረዋል፡፡
‹‹ታሪክ አጥፍተን ታሪክ አንሠራም፤›› በማለት  የአስተዳዳሪውን ሐሳብ  በአንድ ድምጽ መቃወማቸውን የገለጹት  ሰራተኞቹ ፣ ደመወዛቸውን በማዋጣት ለህዳሴ ግድብ ቦንድ እንደሚገዙ የተናገሩ ቢሆንም፣ አስተዳዳሪው ግን እንዳስፈራሩዋቸው አስረድተዋል፡፡
ስለጉዳዩ የተጠየቁት የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ መልዓከ ፀሐይ ቆሞስ አባ ገብረ ኢየሱስ መኮንን፣ ‹‹የተባለው ሁሉ በተለይ ቦንድ የተባለው ጉዳይ ውሸትና ሐሰት ነው፤›› በማለት አስተባብለዋል፡፡ ሀገረ ስብከቱ ከወሰነበት ውጪ የተደረገ ነገር እንደሌለም  አስተዳዳሪው አክለዋል፡፡ ጸሐፊው መጋቤ ሐዲስ ዲበኩሉ ገብረዋህድ  ግን፣ “ተሰጠ የሚባለው ወርቅ የአንገት ሐብልና የጣት ቀለበት ከምዕመናኑ በስለት የሚገባና ሀገረ ስብከቱ የወሰነበት መሆኑን ነው የተናገሩት፡፡ ጉዳዩን ያውቀዋል የተባለውን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኮንን  <<ምእመናኑና ካህናቱ ወርቅ ጠፍቷል በሚል ያቀረቡት ተቃውሞ ዝም ተብሎ የሚታይ ሳይሆን መጀመርያ ማጣራት ተገቢ ነው” ብለዋል።
ሀገረ ስብከቱ የካቲት 10 ቀን 2007 ዓ.ም. ጉባዔ አድርጎ አጣሪ ኮሚቴ መሰየሙን የተናገሩት ስራ አስኪያጁ፤ ከቅርስ ጥበቃና ባላደራ ባለሥልጣን፣ ከጉለሌ ክፍለ ከተማ ፍትሕ ጽሕፈት ቤት፣ ከሀገረ ስብከቱ ካህናት አስተዳዳሪ መምርያ፣ ከቅርሳ ቅርስና ከክፍለ ከተማው ሀገረ ስብከት አምስት አባላት ያሉት ኮሚቴ ተሰይሞ የካቲት 11 ቀን 2007 ዓ.ም. በደብሩ በመገኘትና ኃላፊዎቹ ባሉበት እንደሚያጣራም አስታውቀዋል፡፡

No comments:

Post a Comment