Friday 6 February 2015

5 የአየር ሃይል የጥበቃ አባላትና 2 ፓይለቶች ጠፉ

ጥር ፳፱(ሃያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የኢሳት የአየር ሃይል ምንጮች እንደገለጹት ከሁለት ሳምንት በፊት 5 የአየር ሃይል የጥበቃ አባላት እስከነ ሙሉ ትጥቃቸው እንዲሁም 2 ፓይለቶች ከድሬዳዋ አየር ሃይል ጠፍተዋል። የጥበቃ አባላቱም ሆነ ፓይለቶቹ  ያሉበትን ለማወቅ የተደረገው ጥረት እስካሁን አልተሳካም። ይህንን ተከትሎ ጄ/ል ሳሞራ የኑስ ከመቶ አለቃ ማእረግ በላይ ያላቸውን አየር ሃይል አባላት ሰብስበው ግምገማ አካሂደው ነበር።

ጄ/ል ሳሞራ “የአየር ሃይል አባላት ለምን ይከዳሉ? አሁን ያላችሁትስ ምን ታስባላችሁ?” የሚል ጥያቄ ለተሰብሳቢው ያቀረቡ ሲሆን፣  የአየር ሃይል አባላቱም ከፍተኛ የሆነ የአስተዳደር በደል እንደሚደርስባቸው፣ ከእጅ ወደ አፍ የሆነ ክፍያ እንደሚከፈላቸው፣ በመኖሪያ ቤት እጦት እንደሚሰቃዩ ገልጸዋል። መኮንኖቹ በርካታ ችግሮችን ዘርዝረው ያቀረቡ ቢሆንም፣ ጄ/ል ሳሞራ ችግሮችን ከመስማት ውጭ ምንም አይነት ምላሽ ሳይሰጡ ሄደዋል።
የአየር ሃይል አባላት ሞራል ( ስሜት) መዳከም ገዢው ፓርቲ በሩሲያ ቅጥር አብራሪዎች ላይ እምነቱን እንዲጥል አድርጎታል። የትግራይ ተወላጅ የሆኑት  ሻምበል ሳሙኤል ግደይ እና ቴክኒሻን ብርሃን ግደይ ከመቶ አለቃ ቢልልኝ ደሳለኝ ጋር በመሆን ስርአቱን አናገለግልም ብለው ሄሊኮፕተር ይዘው መጥፋታቸው፣ የህወሃትን የዘር ፖለቲካ መሰረት እንዳናጋው ምንጮች ይገልጻሉ። ለወትሮው ይታመኑ የነበሩ የትግራይ ተወላጅ የአየር ሃይል አባላት ሳይቀሩ የሚታመኑ ሆነው ባለመገኘታቸው ፣ ባለስልጣናቱ አይናቸውን የውጭ ቅጥረኞች ላይ እያዞሩ ነው።
ስርዓቱን አናገለግልም ብለው የጠፉት የአየር ሃይል አባላት የተቃዋሚ ድርጅቶችን ተቀላቅለው እየታገሉ ነው።   በሌላ በኩል ደግሞ የአፍሪካ መሪዎችም ሆነ የሌሎች አገራት መንግስታት ለስብሰባ ወደ አዲስ አበባ በሚመጡበት ጊዜ ለደህንነት ስራም ሆነ ለልዩ ጥበቃ የሚመደቡት የአንድ ብሄር ተወላጆች ናቸው በማለት የሌሎች ክልሎች የደህንነት አባላት ቅሬታ ማሰማታቸው ታውቋል። የ24ኛው የአፍሪካ የመሪዎች ጉባኤ ከተካሄደ በሁዋላ ለግምገማ ከተጠሩት ምድብተኛ የደህንነት ሰራተኞችና የጸጥታ አካላት መካከል አንዳንዶች፣  ” ለመሪዎችና ለእንግዶች ደህንነት የሚመደቡት ጠባቂዎች የአንድ አካባቢ ተወላጆች ብቻ መሆናቸው፣ “ስርአቱ የእናንተ አይደለም፣ አናምናችሁም” የሚል መልክት አለው በማለት በድፍረት ለገምጋሚዎች ተናግረዋል።
“በብሄራችን ምክንያት ተበድለናል” ያሉት የደህንነት ሰራተኞችና ጠባቂዎች፣ ደረሱብን ያሉዋቸውን በርካታ ችግሮች ዘርዝረው አቅረበዋል። ” በኢትዮጵያ ውስጥ አሸባሪዎች ራሳቸውን እያደራጁና መረባቸውን እየዘረጉ በመጡበት ሁኔታ የምናምነውን ሰው እንመድባለን” የሚል  መልስ ግምገማውን ከሚመሩ መሪዎች የተሰጠ ሲሆን፣ ተሳታፊዎች  በተሰጠው መልስ ማዘናቸውን በግምገማው የተሳተፉ የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

No comments:

Post a Comment